RSS

Monthly Archives: November 2012

የተዘነጋ ገፅ . . .

እ – ህ – ህ… ወ – ፍ – ዬ . . . ኡ – ሁ – ሁ… ወ – ፊ – ቱ . . .
ከሚለው የአበበ ተካ ዘፈን ጋር ለአመታት የከረመው ፍቅሬ ሰሞኑን አገርሽቶ (ምን እንደቀሰቀሰው ባይታወቅም) እንደገና እንደ አዲስ ከወፍዬ ጋር እየዘመርኩ፣ እያፏጨሁ… አብሬያት አለሜን እየቀጨሁ… የግጥሙን ርቀት… የጥበቡን ጥልቀት ሳብሰለስል… ፍቅርና ወፍ፣ ወፍና ጎጆ፣ ጎጆና ሰው፣ ሰውና እምነት፣ እምነትና ተፈጥሮ፣ ተፈጥሮና ህይወት ምናምን እያልኩ ማደበላለቅ ሲያምረኝ… ሲያመራምረኝና ሲመረምረኝ… ገጣሚው ባይኔ ላይ ይዋልል ገባ… ስምም፣ ክብርም፣ ብርም ተነፍጎት ያለፈው ሙሉጌታ ተስፋዬ… ሰላማዊ እረፍት ሙሌዋዋዋ… በዚሁ ዋዋዋ ልበል እንጂ !

ድምጻዊ አበበ ተካ በአንድ ወቅት የሙዚቃውን ገበያ የተቆጣጠረ… በቅንጣት ዝና የከበረ… ዘፈኖቹ እንደጣፋጭ ቡና እየተደጋገሙ የተጣጣሙለት ምርጥ ዘፋኝ እንደነበር የ1988ቱን የኪነ ጥበብ ፌስቲቫል እና የአቤን ሽልማት (እንዲሁም ለቅሶውን…) ማስታወስ ብቻውን በቂ ነው፡፡ ቆይ ግን አቤ የት ገባ? በቃ እልምምም?!… “ያ ሱዳን ፈናኒ” እያለ ቼቺኒያን እንዳላቀናት እንዲህ ድምጹ ጥፍት?…. ኧረ አቤ አንተ ያቀናሃት ቼቺኒያ ዛሬ ራሷን የቻለች አገር ሆና ምግብም፣ ጥበብም፣ ህይወትም፣ ሞትም እየተቸበቸበባት ነውና እንዳቀናሃት ካለህበት መጥተህ አቃናት ብያለሁ እግረመንገዴን . . .

እና እንደዚያ አቧራ ያጨሰ የነ ወፍዬ ዘፈን አልበም መላው ግጥሞቹ (ከአንድ ዘፈን በስተቀር) የሙሌ እንደሆኑ ሳስብ ያለዋዛ እንዳልተወደዱ ገባኝ… አበበ ተካ ከዚህ አልበሙ በፊት የቀደመ አልበም ነበረው እምብዛም አይታወቅም… እናም ለአበበ ዝና ሌሎች በርካታ ተጨማሪ ተዛማጅ ጥበቦች ቢኖሩም ቅሉ የሙሌ ጣፋጭ ግጥም የአንበሳውን ድርሻ እንደሚወስድ ማንም አይክድም!
*
ማነው ደግሞ ያ ድሮ ጥርሰ ወርቅ የነበረው አሁን ግን ጥርሱ ሃጫ በረዶ የሚመስለው ዘፋኝ?… ያ ነዋ የጥቁር ውሃው ልጅ?… ታምራት ደስታ አትሉኝም!… ታምራት ደስታ የቱ?… ብንባል ብዙዎቻችን ታምራት “ሃኪሜ ነሽ” ነዋ ብለን እንደምንመልስ ጥርጥር የለኝም… ለምን ቢባል ታምራትን ካለመታወቅ ወደ መታወቅ ከከተፋ ቤት ወደ አደባባይ ይዛ የወጣች ዘፈን ሃኪሜ ነሽ ናትና !

♫ . . . ሐኪሜ ነሽ መድሃኒቴ
ፈዋሼ ነሽ እመ እምነቴ
ሐኪሜ ነሽ መዳኒቴ
እኔ አዳም
ብሞት አንቺንስ አልከዳም . . . ♫

♫ . . . አንቺን የመሰለ ሌላ ሰው ቢኖርም
ላይን ይሞላል እንጂ ለነፍስ አይዘምርም
ጠረንሽን ለምጄ እንደ ናርዶስ ሽቶ
ሌሊቱ እንዴት ይንጋ ቀኑስ እንዴት መሽቶ . . . ♫

የዚህም ግጥም ጌታ የታሜ ባለውለታ አሁንም ሙሌ ነውና ክብር ለሙሌ . . .

*
♫ . . . አደራ ልጄን አደራ
ሆዴን ልጄን አደራ . . . ♫

የሚለውን የብጽአት ስዩም ዘፈን ያደመጠ፣ የወለደና እና የከበደ ዘፈኑን ሲሰማ ወይም የብጽአትን በእንባ የተሞላ አዘፋፈን ሲያይ ልጁን ብሎም እናቱን እያሰበ በፍቅር እንደሚቃጠል ዘፈኑን ያደመጠ ቢፈርድ ይሻለኛል. . .

♫ . . . ወልደህ እየው ብሎ ወላጅ የመረቀው
ለልጅ ሲንሰፈሰፍ ያኔ ነው የሚያውቀው
እርብትብት ከንፈሩ ያንገቱ ስር ሽታ
ከሞትም ያድናል እንኳን ከበሽታ . . . ♫

♫ . . . ባልማዝና በእንቁ በከበረ ድንጋይ
አሽቆጥቁጬ አኑሬሽ በሆንኩሽ አገልጋይ
ምናለ ለእምዬ ውሃ ሸጬስ ባድር
ማን ውጪ እንዳይለኝ ካገርና ከእድር . . . ♫

ይህን የመሰለ መቼም ሊደመጥ የሚችል ዘፈን እንዲሁም ሌሎች የአንድ ሙሉ አልበም የብጽአት ዘፈኖች የሙሌ ናቸውና አሁንም ክብር ለሙሌ!… የፀደኒያ ገብረማርቆስ፣ የሃና ሸንቁጤ፣ የመሰረት ሌላም ሌላም… እያሉ መዘርዘር ይቻላል…

እንደው ወፍዬ ኮርኩሮኝ አነሳሁት እንጂ እጅግ የበዙትን የባለቅኔውን የዘፈን ግጥሞች እዚህ ዘርዝሬ አልዘልቀውም… ምናልባት እየቆራረጥን በተለያየ ግዜ መነካካት የቻልን እንደሆን እንጂ!… ግና የዚህ ሁሉ ጥበብ ባለቤት የሆነ ታላቅ ሰው እንደምንምና እንደማንም ተዘንግቶ ሲቀር ማየት በ’ርግጥ ያማል፡፡ ስንዱ አበበ እጅግ የበዛ ክብርና ምስጋና ይግባትና የተወሰኑትን ስራዎቹን ሰብስባ “የባለቅኔ ምህላ”ን አሳትማልናለች… “ጉኖዬ” አክብሮታዊ ምስጋናዬ ባለሽበት ይድረስሽ… ላሁኑ የዘፈን ስራዎቹ ላይ ብቻ ነኝና ስንዱ በመጽሐፉ − ደብዳቤ ለ“ሲኦል”− ስትል ስለ ሙሌ ከጻፈችው ትንሽ ልቆንጥር…

“. . . ይህንን ይሁን ብዬ ጓዶቼን ፈትቼ፣ ህዝቤን አምኜ፣ ችሎታዬን ለዘፋኞች ልስጥ አልኩና ተነሳሁ፡፡ ገበያው እጅግ የደራ ከመሆኑ የተነሳ እንኳን ሌላ ነገርሽን ከዓይንሽ ላይ ኩልሽን ሊሰርቁሽ የሚችሉ ሰዎች የበዙበት ሆነ፡፡ ይህን ትልቅ የገበያ ስፍራ ለመቀላቀል ስንት አሳር እንደቆጠርኩ ዛሬም ሳስበው ይዘገንነኛል፡፡ በቃ የስልጣናቸው የመጨረሻ ዳር ድንበር አሁን ትዝ አለኝ! “የኢኮኖሚው ባለቤት የፖለቲካውም ዋና ባለቤት” እንደሆነ ሁሉ የስራው ባለቤቶች ነጋዴዎች ብቻ ሆኑ፡፡

. . . “እኔ እበላ − እኔ እበላ” እያሉ ከሚሻሙት ጋር ለጨው ለበርበሬ፣ ለውሎ ላዳሩ እንኳ ብዬ አብሬያቸው ለመቆየት አቃተኝ፡፡ ይልቅ ጠጋ ያሉኝ ጋር በማርያም መንገድ፣ በማተብ በክርስትና ለየግል ተነጋግረን፣ ቀኑን አሳምረን፣ ዱአ አድርገን፣ ተፈጥሮንና ፈጣሪን ሳይቀር እያፋጠጥን አብረን ጎጆ ልንወጣ ሰርተን ፈረንካው ሲገኝ አይኔን ለማየት እንኳ ይፀየፋሉ፡፡ አልፈው ተርፈው ብኩርናዬን ሳይቀር እንድሸጥላቸው ሁሉ ጠየቁኝ፡፡

. . . ስሚ ʻንጂ አንድ ቀን “ያንተን የተለያዩ ዘፈኖች መደዳውን ዛሬ አራት በኤፍ ኤም ሰማሁ ብለሽ” በልብሽ ያጨበጨብሽልኝን ዕለት አስታውሼ ምን ትዝ አለኝ መሰለሽ! ያወጣሁላቸው ስሞች! ታምራት ሃኪሜ ነሽ፣ መሰረት ጉምጉም፣ ፀደኒያ ገዴ፣ ብፅአት ገዳዬ፣ ሸህ አብዱ ሃዋብስል ኧረ ስንቱን አድምቄዋለሁ አያ! ምንስ ቢሆን ሙሉጌታ ተስፋዬ ወዲ ሀለቃይ! ተጋዳላይ ነኝ’ኮ! … ” (የባለቅኔ ምህላ፣ ገፅ 133)

እስቲ ደጋግመን እናንብበውና ከባለቅኔ ምህላ ጋር ደግሞ እንመለሳለን… የቻላችሁ አንብቡትማ!… ዛሬም በርካታ ሙሌዎች በዙሪያችን ይኖራሉና ክብር ለጥበበኞች. . . ነጃ ይበለን እያልን በሃና ሸንቁጤ ዘፈን (በሙሌ ግጥም) እንሰነባበት . . .

“ነጃ በለኝ ወሎ ነጃ በለኝ ነጃ
ነጃ በለኝ የጁ ነጃ በለኝ ነጃ
ታውቀዋለህና የፍቅርን ደረጃ . . .

አንዴ በንጉርጉሮ አንዴ በመንዙማ
ሲያወድስ ይውላል የፍቅርን ከራማ !
አጠገቡ ሆኘ እሱን እየካደምኩ
ከራማው ገብቼ ሳጫጭሰው ባደርኩ !
እናቱ ዱበርቲ አባቱ ሼህ ናቸው
አድርገው ያሉትን የሚያደርግላቸው . . . ”

ሰላም!
አብዲ ሰዒድ

ፎቶ: ከስንዱ አበበ ፌስ ቡክ ገጽ የተገኘ!

 
2 Comments

Posted by on November 27, 2012 in ስብጥርጥር

 

“. . . ነፃ አውጪ . . . ”

ከግፍና ከመከራ
__ አገር ነፃ ልታወጣ፣
ፍትህና እኩልነት 
__ በወገን ደጅ ልታሰጣ፣
ድንቁርናን ልታጠፋ፣
የ’ውቀት ብርሃን ልታሰፋ . . . 

ሌት ተቀን የምትዳክር 

__ አንተ ቆራጥ ወገኔ፤
ለውለታህ ቃልም የለኝ 
__ ብርታት ይብዛልህ ወኔ . . . 

*
እቅድ ውጥንህ ተሳክቶ
የልፋትህ ጥግ ፍሬ አፍርቶ
ጨለማችን ለብሶ ትቢያ
ብርሃን ፀዳል ነግሶ ግልቢያ

እንድናየው ባገር ሸንጎ
በደላችን ተጠራርጎ
ጭንቃችንን ተሸክመህ አደባባይ ስትወጣ
ቅንጣት ተስፋችንን ባንደበትህ እንዳናጣ
ከኛ ነፃነት በፊት ነፍስያህን ነፃ አውጣ !!!

(© አብዲ ሰዒድ፣ ሐምሌ 2004 E.C)

 
Leave a comment

Posted by on November 18, 2012 in ግጥም

 

ጥ – ሬ. . . !

“ዶሮ ብታልም ያው ጥሬዋን”

_ ብለህ ያልከኝ ጓዴ

በል እንካ ጥሬ ቃል

_ ከጥሬ ልቦና፣ ለጥሬው ዘመዴ . . .

*

ዶሮስ ጥሬ አለመች፣ ጥሬ ነው አለሟ ፣

ጥሬ ነው ህይወቷ፣ ጥሬ ነው ሰላሟ . . .

 

‘ምትከርመው በጥሬ

‘ምትኖረው ለጥሬ 

አኗኗሯ ጥሬ

አሟሟቷም ጥሬ

ጥሬ… ጥሬ… ጥሬ…

እሷን መች ጠርጥሬ?! …

*

ይብላኝ እንጂ ለኔ፣ ይብላኝ እንጂ ላንተ !

በጥሬ ህልም ዓለም፣ ቀንህና ቀኔ ለተንከራተተ . . .

 

ተቃውሟችን ጥሬ

ድጋፋችን ጥሬ

ሽብራችን ጥሬ

ህዳሴያችን ጥሬ

ሃዘናችን ጥሬ

ደስታችንም ጥሬ

ጥሬ… ጥሬ… ጥሬ…

ብዙ ቀባጥሬ

“ልማት አሸብሬ” . . .

ሐይሌን አስደንብሬ . . .

 

እኔና አገሬን አጉል ከማጠፋ

ጥሬ እየጠረጠርኩ እስቲ ላንቀላፋ

አንተም ከጥሬህ ጋር ጥሬ ቀንህን ግፋ . . .

 

(© አብዲ ሰዒድ፣ ነሐሴ 2004)

 
Leave a comment

Posted by on November 17, 2012 in ግጥም

 

የፊደል ገበታ . . . !

__ ሀ፣ ለ፣ ሐ፣ መ . . . 
ያየሽ አይኔ ታመመ
ልቤም ሲያስብሽ ደከመ
እግሬም ወዳንቺ አዘገመ . . . !

__ ሠ፣ ረ፣ ሰ፣ ሸ . . .
ህልሜ በህልምሽ ታሸ
አቅሜና ልኬ ተፈተሸ

ወኔዬም ጥሎኝ ሸሸ . . . !

__ ቀ፣ በ፣ ተ፣ ቸ . . .
ሩሕሽ ሩሔ ላይ ተምቧቸ
ኑሮዬ በስምሽ ተመቸ 
ህይወት ያላንቺ ሰለቸ . . . !

__ ኅ፣ ነ፣ አ፣ ኘ . . . *
ከቃልሽ ፍስሃ ተገኘ
ከገፅሽ ብርሃን ናኘ
የመውደድ ቅኔ ተቀኘ . . . !

__ ኸ፣ ወ፣ ዐ፣ ከ . . . **
ኑሮና ፍቅር ተቦተለከ 
ድርና ግብር ተሰከሰከ
ነፍሴም ስላንቺ ተብሰከሰከ . . . !

__ ዘ፣ ዠ፣ የ፣ ደ . . .
ብልሃት ከመብላት ተዛመደ
ልኬት ከስኬት ተዋሃደ
ጥፋት ወ ክፋት ተማገደ . . . ! 

__ ጀ፣ ገ፣ ጠ፣ ጨ . . .
ደሜና ደምሽ ካንድ መነጨ
የሕላዌን ቃል በጋራ ረጨ
በዘልዓለም ጥግ ኪዳን ተቋጨ . . . ! 

__ ጰ፣ ጸ፣ ፐ፣ ፈ . . . *** 
ዘመን በዘመን ተተካ አለፈ
ውበትና ጉልበት እያደር ረገፈ

ፍቅሬ ፍቅርሽ ግን
__ ከሰማየ ሰማይ ከአፅናፍ አለፈ::

__________ / © አብዲ ሰዒድ / _________

ትክክለኛው የፊደል አቀማመጥ
* ኅ፣ ነ፣ ኘ፣ አ
** ከ፣ ኸ፣ ወ፣ ዐ
*** ጰ፣ ጸ፣ ፀ፣ ፈ፣ ፐ እና ቨ
 
Leave a comment

Posted by on November 10, 2012 in ግጥም

 

ገርሞ… ገርሞ… ደግሞ ገረመኝ…!

ከየት እንዳመጣችው ባላውቅም እናቴ ደስታዋ አልያም ትዝብትዋ ከመገረም በላይ ሲሆንባት ሁሌም የምትላት ነገር አለቻት… “ገርሞ…ገርሞ…ደግሞገረመኝ!”… ʻየምር ለአፍሪካ ዋንጫ አልፈናል አይደል?ʼ… እውን ከነ ናይጄሪያ፣ ከነዛምቢያና ቡርኪናፋሶ ጋር ተደልድለን ልንፋለም ነው አይደል?… እውን እምዬ ጦቢያም ወግ ደርሷት ከእግር ኳስ ተፋላሚ አገሮች ተርታ ተሰልፋ ላያት ነው አይደል?… እያልኩ ደግሜ ደጋግሜ ሳሰላስል፣ የኳስ ደስታንና ያገር ደስታን ሳብሰለስል፣… ምክንያቱን የማላውቀው እምባ አይኔን ሲሞላው ዝም ብሎ ይገርመኛል (ጅል ነኝ አይደል?…) ይገርም ይገርምና ይወስደኛል… ጭልጥ አድርጎ  ይወስደኛል ወደ ዘመነ ቼልፊኮ… ወደ ዘመነ መንግስቱ… ወደ ዘመነ አዋድ… ወደ ዘመነ ሉችያኖ… ወደ ዘመነ ተስፋዬ… ወደ ዘመነ ስኬት… ወደ ዘመነ ዝና… ወደ ዘመነ ክብር… ከዚያም ቼልፊኮና እግር… እግርና አገር… አገርና ፍቅር… ፍቅርና ክብር…. ይደበላለቁብኛልና እንዲህ እላለሁ . . .

በቼልፊኮ ጫማ እግር እየደማ

በ’ናት አገር ፍቅር ልብ እየተጠማ

ስንት ታሪክ ታየ ስንት ጉድ ተሰማ . . .!

ቼልፊኮ የድሮ የኢትዮጵያ ተጫዋቾች የእግር ኳስ መጫወቻ ጫማ ነው… ይህ ጫማ የሚሰራው እያንዳንዱ ተጫዋች ባዶ እግሩን ወረቀት ላይ ከተለካ በኋላ ሲሆን፣ ሁሉም በየልኩ ሶሉ በሚስማር እየተመታ ይዘጋጅለታል… በጨዋታ መሃል ሶሉ ሊገነጠል ስለሚችልም የዛን ጊዜ ወጌሻዎች መዶሻ ይዘው ወደ ሜዳ ይገቡ ነበር ይባላል… ʻአጃኢበ ረቢ!ʼ አትሉም!?… aha… እንደውም ባንድ ወቅት መንግስቱ ወርቁ ገጠመኞቹን ሲያወራ “ያፍሪካ ዋንጫን በወሰድንበት ጨዋታ ጎል ካገባሁ በኋላ የቸኮልኩት ዋንጫውን ለመውሰድ ሳይሆን ጫማው እግሬን የወጋኝን ቶሎ ፈትቼ ለመገላገል ነው” ሲል በማስፈገግ የጫማውን አስቸጋሪነት ጠቁሞ ነበር…

የጎንደር ልጅ ነው ያውም የቋራ

መንግስቱ ወርቁ ልበ ተራራ …!
(ያዝማሪ ዘፈን)
ግን መንግስቱ ወርቁን የሚገባውን ክብር ለግሰነው ይሆን?!… አይመስለኒ!… ብለን ትንሽ ብናስታውሰውስ?!… መቼም የሚዘከሩት ሌሎች ሲሆኑ ገረመንና “የነሱ ፈቃድ ይሁን ብለን ዝም አልን!”… aha… መንጌ ፊት አውራሪው… መንጌ ጎንደሬው… መንጌ አድባሩ… መንጌ 8 ቁጥሩ… መንጌ የእምዬ ባለውለታ… ደግሞ እኔ ያወጣኋቸው ስሞች እንዳይመስሏችሁ… ሲሞገስበት የነበረ እንጂ!እኛ እንኳን ባቅማችን ድሮ ቢንጎ ስንጫወት B8 ሲወጣ “B መንግስቱ ወርቁ!” ብለን በመጥራት የማስታወስ ሙከራ አድርገንለት ነበር… ብሔራዊ ሎተሪ ሰምቶ ቢንጎ ሎተሪን ሲያዘጋጅ በማጽደቅ አልተባበረንም እንጂ! … aha
በሰባት የአፍሪካ ዋንጫ ጨዋታዎች አገርን ወክሎ መሰለፍ፣ ባፍሪካ ዋንጫ ታሪክ ከሰባት ምርጥ ጎል አግቢዎች አንዱ መሆን (10 ጎል በማግባት)፣ ብሔራዊ ቡድንን በማሰልጠን ላፍሪካ ዋንጫ ውድድር ይዞ መቅረብ፣ ከ115 በላይ አለም አቀፍ ጨዋታዎች በላይ መሳተፍ፣ ከ 65 በላይ ጎሎችን ማስቆጠር፣ በዘመኑ ምርጥ በመሆኑ በጣልያን፣ በግሪክ፣ በስፔይን፣ በፈረንሳይ እና መሰል ሃገሮች እንዲጫወት ተጠይቆ የነበረ መሆኑ እና ሌሎች ብቃቶቹ… ክብር የማይገባው ተራ ነገር ይሆን?!.. ያው የኳስ እውቀቱ ስለሌለኝ የሚመለከታቸው እነ ጋዜጠኛ አበበ ግደይ ወይም ሌሎች እንዲተነትኑት ትቼ ዝም ብዬ መገረሜን ልቀጥል… (የምር ግን ሁሉም ነገር በባለሞያ ሲተነተን አሊያም ሲሰራ ደስ ይላል… ሙዚቃውንም ፖለቲካውንም… ምኑንም ምኑንም ደግሞ ከኔ ወዲያ ብሎ መፈትፈት ሼ ነው እኮ!…. ኧረ ሼሼሼሼሼ…. aha…)
አዋድ ሞሃመድስ ቢሆን በአምስት የአፍሪካ ዋንጫዎች ከመሳተፉም በላይ ኢትዮጵያችን እስካሁን ጉራዋን የምትቸረችርበትን ብቸኛ ዋንጫ ስታነሳ ከነሉችያኖ፣ ከነኢታሎ፣ ከነጌታቸው፣ ከነአስመላሽ፣ ከነክፍሎም፣ ከነበርሔ፣ ከነመንግስቱ፣ ከነተስፋዬ፣ ከነግርማ እንዲሁም ከግብ ጠባቂው ጊላሚካኤል ጋር አብሮ የጨፈረ ተጫዋች አይደለምን?… ግና ምን ተሸለመ? አሊያም ምን ተደረገለት? ብለን ስንጠይቅ…“ምንም የተደረገልኝ ነገር የለም… በርግጥ የፌዴሬሽኑ ፕሬዝዳንት ሲያገኙኝ በክብር ያናግሩኛል… ሌላው ቀርቶ ባበረከትነው አስተዋፅኦ አማካኝነት የተሰጠንን የእድሜ ልክ የነፃ መግቢያ ትኬት ሰረዙት::”… ሲል ባንድ ወቅት የተናገረው መልስ ይሆነንና እንገረማለን… ግን የነሱ የነፃ መግቢያ ትኬት ቢሰረዝና ከፍለው እንዲገቡ ቢደረግ ለአገሪቷ የኢኮኖሚ እድገት አስተዋፅኦ ያደርጋል ተብሎ ታስቦ ይሁን?… aha… ብሽቅ አለ ጋስ ስብሃት!…
አዋድ ግን ይቀጥላል “እኔ ባበረከትኩት ውለታ ደስ እንዲለኝ… ወጣቶቹ እኛን እያዩ መበረታቻ እንዲሆናቸው እንጂ እኔ የምከፍለው እስካለኝ ድረስ ከፍዬ ‘ገባለሁ… ደግሞም ይመስገን በኑሮዬ ደስተኛ ነኝ” ይሄን ሲናገር ያየሁበት የፊት ገፅታ ውል ሲለኝና የነሰለሃዲን የአሸናፊነት ድል መታሰቢያነቱ ለድሮው ጠቅላይ ሚኒስትራችን ሆነ መባሉን ስሰማ… የምር ገረመኝ!… ገርሞ… ገርሞ… ደግሞ ገረመኝ!
በበኩሌ ያለፉት ጠቅላይ ሚኒስትራችን ቢዘከሩ ቅንጣት አይከፋኝም!… ግን ደግሞ እንደ መንግስቱ ወርቁ ያሉ ብርቅዬ የኢትዮጵያ ልጆች አሊያም የዛኔው ቡድን ቢዘከርበት (መዘከሩ ካስፈለገ) የበለጠ ትርጉም አይኖረው ይሆን?!… እነ አዳነ፣ እነ ሳላሃዲን፣ እነ ደጉ እና መላው የቡድኑ አባላትስ ቢሆኑ ታሪክ ቀያሪ ከመሆናቸውም በላይ የበለጠ ታሪክ እንዲሰሩ፣ ነገ እነሱም የሚዘከሩበት ስም እንዲተክሉ የተሻለ የሞራል ብርታት አይሆናቸው ይሆን?… በደስታ ጊዜ የሚደረጉ ማናቸውም ነገሮች ነገ የበለጠ ደስታ የሚያስገኙ፣ ለተሻለ ፍሬ የሚያበቁ ቢሆኑ ደስ ይላል… በርግጥም የተሻለ ነገር ያመጣሉና!… ቱ!… ድንቄም ምክር እቴ!…
ደግሞ ይሄን ስላልን አንዳንድ የዋህ ደጋፊዎች ተነስታችሁ “ፀረ ልማት፣ ፀረ እድገት” ምናምን የሚል የሽብር ታርጋችሁን ለመለጠፍ ብትሯሯጡ… እንዲሁም አንዳንድ ከንቱ ተቃዋሚዎች መንገድ አገኘን በሚል የዘለፋ ውርጅብኛችሁን ለማውረድ ብትውተረተሩ አሁንም ገርሞ… ገርሞ… ደግሞ ገረመኝ!… ከማለት ሌላ የምንለው አይኖረንም!… aha… እስቲ ኳስን በኳስነቱ ብቻ ወደ ተሻለ ደረጃ ከፍ እንዲያደርጉት እነዚህን ምርጥ ልጆች እናበረታታቻው… ያ ሲሆን ብዙ ምርጥ ምርጥ ተተኪ ታዳጊዎችን ማፍራት ይቻላልና. . .
እዚህ ጋር Tessema Simachew የተባለ የፌስ ቡክ ወዳጃችን ከድል በኋላ የለጠፈውን ብዋሰው ውስጤ ያለውን የበለጠ ይገልፅልኝ ይመስለኛል…  “እንዲህ አይነት ቀኖች ያለፈው ጊዜ ማብቅያ ብቻ አይደሉም፣ የመጭው ጊዜም መጀመሪያ ናቸው። ነገ ኳስ ይዘው ወደ ሜዳ የሚሄዱ ህጻናት ሳልሃዲን ሰይድን ወይም አዳነ ግርማን መሆን ስለሚፈልጉ በደስታ ይጫወታሉ። ከዚህ በኋላ ለሌላ አስርት አመታት የበይ ተመልካች በእርግጠኝነት አንሆንም። የሽንፈት ታሪካችንን ስለሰበራችሁልን፣ ጀግኖቻችን ናችሁ።” ክበርልኝ ተሰማ! . . .
ከጨዋታው በፊት ቡድናችንን ይቅናችሁ ስል እንዲህ የሚል ዱዓ የፌስ ቡክ ግድግዳዬ ላይ ለጥፌ ነበር
አዳነ ሳላሃዲን፣ ሳላሃዲን አዳነ
የእምዬ ክብር በናንተ ተጫነ
እንግዲህ አደራችሁን ብርታት አይራቃችሁ
እምዬ እናት ዓለም ዛሬ ትኩራባችሁ . . .ዱዓና ጸሎታችን ተሰማና በስም የተጠሩት ተጫዋቾች እምዬን ታደጓት (እንደ አባባ ታምራት መጠንቆል አማረኝ እንዴ ?!… aha)… ብቻ  የሆነ  ሆኖ በጭፈራ ውስጥ ሆነን ደግሞ እንዲህ አልን…
አዳነ፣ ሳላሃዲን፣ ሰላሃዲን፣ አዳነ
አገር ከህመሙ በናንተ እግር ዳነ
ስኬት ብልፅግና ይብዛላችሁ
ደስታ ዛሬ ለሰራችሁት ለህያው ውለታ . . . !
እልል በይ ሃገሬ በይ ኩሪ ጨፍሪ
ነገ ደግሞ ሌላ ፈርጦች ልታፈሪ . . . !ክብርና ምስጋና ለመላው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አባላት…
ሁሌም ሰላም እና ዘላለማዊ ፍቅር ለኢትዮጵያችን…
ነገ ደሞ የተሻለ ይሆናል . . . ኢንሻአላህ!
 
Leave a comment

Posted by on November 3, 2012 in ስብጥርጥር

 

የነጽዬ ፍቅር … !

የልጅነት ህልሜ

የሌት ተቀን ትልሜ

ነጺዬ እመቤቴ ፍቅሬ አበባዬ

ምነው ድምፅሽ ጠፋ ብቅ በይ ሽታዬ …

*

እኔ ባንቺ ፍቅር . . .

ምስልሽን ስስል፣ ሳሳምር ስቀባ

እልፍ ዘመን ነጉዶ፣ እልፍ ዘመን ጠባ …

አብረን አላሳለፍን፣ ወይ ትዝታሽ የለኝ

በሩቁ እያየሁሽ፣ ናፍቆትሽ ገደለኝ …

ነፂዬ ምኞቴ፣ ነፂዬ ስጋቴ

ነፂዬ ስስቴ፣ ነፂዬ ብሶቴ

አንቺው ነሽ ውበቴ፣ ባንቺው ነው ማማሬ

ከሰው ሰልፍ የምገኝ በወግ ተቆጥሬ …

አንቺ የሌለሽበት . . .

እንጀራው አይወርደኝ ይተናነቀኛል

ውሃ እንኳን ወግ ደርሶት ጀግኖ ያንቀኛል

አንሶላ ትራሱ ይኮሰኩሰኛል

ጨዋታው አይጥመኝ ይጎረብጠኛል …

*

እኔ አንቺን ፍለጋ . . .

ውሃ እንደ አቧራ ባይኔ እየቦነነ

እልፍ እፍኝ በረዶ ጉንጬ እየዘገነ

እጅ እግሬ ደንዝዞ በቆፈን ተይዞ

በቀጩ፣ በውርጩ ወዜ ተመዝምዞ

በድን አካል ይዤ አገር አስሳለሁ

ባገኝሽ እያልኩኝ እንከላወሳለሁ …

 ወዴት ነው ያለሽው አለሁ በይኝ ውዴ

የት ነው የማገኝሽ እስቲ ጥሪኝ ግዴ

አንችን በመፈለግ በዛ መማገዴ …

*

እኔ አንቺን ፍለጋ . . .

ሃሩሩ በአናቴ ነግሶ እየነደደ

ህይወት በበረሃው እየተማገደ

በአሸዋው ቃጠሎ

ጅስሜ ተብሰልስሎ

የኮዳዬን ውሃ ጨልጬ አንጠፍጥፌ

በፍቅርሽ ለመለም ተስፋዬን ሸክፌ

ይኸው ካገር አገር እንከራተታለሁ

አለሁ በይኝ ውዴ እጎዳብሻለሁ …

ኧረ ተይ ዝም አትበይ አንቺ ነፃነቴ

ሲገባሽ ስታውቂው ባንቺ መጎዳቴ

እስቲ ተለመኚኝ ብቅ በይ በሞቴ …

ነጺዬ ነጺዬ

ነጺዬ ነጺዬ

ባንቺው ተቃጥዬ

ላንቺው ተብሰልስዬ

አለሁ ሁሉን ችዬ … …!

(አብዲ ሰዒድ)

 
Leave a comment

Posted by on November 3, 2012 in ግጥም

 

ሸ – ገ – ሬ – ዋ . . . (2)

አንቺ የሸገር ልጅ እቴ ሸገሬዋ

ፍቅርሽ አሸፈተኝ ተረታሁ ማሬዋ . . .

*

መቼም ባንቺ መንደር . . .

ሳዱላ፣ ኮኮባው

ውሃ ከርል፣ እሳት ከርል፣

ፓይስትራ፣ ስትሮው ተብሎ ቢሞሸር፤

ዘርፋፋ ሽንሽኑ፣

ትፍትፍ መቀነቱ፣

በዘመን ጅንሶችሽ ቢልቅ ቢሽቀረቀር፤

አደስ ከርቤሽ ላንቺ ቢሆን ዲዮዶራንቱ፤

ንቅሳት፣ ውቅራት ቢተኩም በታቱ፤

ውበትሽ ሙሉ ነው ቅንጣት ያልጎደለ፤

የአፍዝ አደንግዝ ሃይልን የታደለ . . .

*

እናም አንቺን አልኩኝ አንቺን ሸገሬዋ

እንዳሻሽ አድርጊኝ ተረታሁ ማሬዋ . . .

*

ሸ ገ ሬ ዋ . . .

መቼም ባንቺ ዓለም. . .

ፉጨቴን በሚስ ኮል፣ ሎሚዬን በቴክስት፤

በኢሜል፣ በፌስ ቡክ፣

በSkype በምናምን

ቢሆንም ‘ማወጋሽ የናፍቆቴን ስስት፤

ለክብርሽ መታያ

ባይቆምም ገበያ

ቲያትር ሲኒማው

ካፌው መስክሽ ቢሆን ለዉበት ማዋያ

*

ይሁን አንቺን አልኩኝ አንቺን ሸገሬዋ

በያ ተቀበይኝ አንድ በይ ማሬዋ . . .

*

ሸ ገ ሬ ዋ!…

እንደው ቅር እያለኝ…

ጅም እገባ ብለሽ፣

ትጥቆችሽን አዝለሽ፣ ማልደሽ ብትነሽም፤

ሳውና፣ ውሃ ዋና፣

ስቲም፣ ጠጉር ስራ፣

ጥፍር ከተረገዝ ውበትን ድርደራ፣

ሄደሽ ብታመሽም፤

በፋሽን ላይ ፋሽን መግዛት ብትወጅም፤

ለፍቅርሽ መድመቂያ፣

መንፈስ ማነቃቂያ፣ ሰርፕራይዝ ብትለምጅም. . .

*

ይሁን ችለዋለሁ አንቺን ሸገሬዋ

የከተማዋን ፈርጥ ውዲቷን ማሬዋ

አንቺን ሸገሬዋ፣ አንቺን ሸገሬዋ

አቤት አቤት ልበል ለፍቅርሽ ማሬዋ᎓᎓

(አብዲ ሰዒድ
ካዛንቺስ – አዲስ አበባ
ታህሳስ – 2001 E.C)

 
Leave a comment

Posted by on November 3, 2012 in ግጥም

 

ሸ- ገ – ሬ – ዋ . . . (1)

አንቺ የሸገር ልጅ እቴ ሸገሬዋ
ፍቅርሽ አሸፈተኝ ተረታሁ ማሬዋ . . .
*
እንደ ወንዜ ጉብል …
ዘርፋፋ ባትለብሺ፣ ሽንሽን ባታሰፊ፤
ሳዱላ ተላጭተሽ፣
ጠጉርሽን ጎንጉነሽ፣ በመስኩ ባታልፊ፤ …

እንሶስላ ሙቀሽ፣
በአልቦ፣ በድሪ፣ በክታብሽ ደምቀሽ፣
ዘንቢልሽን አንቀሽ፣
__ ገበያ ባትሄጂ፤
በአደስ፣ በከርቤ፣
በብርጉዱ ታጥነሽ፣
በጥላሽ ስር ሁነሽ
ጀግናም ባታፋጂ . . . !
*
እኔስ አንቺን አልኩኝ አንቺን ሸገሬዋ
የጣይቱን ሚሞሳ እንቡጧን ማሬዋ . . .*
ሸ- ገ – ሬ – ዋ!
እኔ እንደማውቃት እንደዚያች ኮረዳ…
ውሃ እቀዳ ብለሽ፣
እንስራሽን አዝለሽ፣ ማልደሽ ባትነሺ፤
ባንገትሽ ዝንጉርጉር፣
ጉራማይሌ ጥርስሽ፣ ቀልቤን ባትነሺ፤
ናፍቆቴን ላጋራሽ፣
በምስጢር ባልጠራሽ፣ ፉጨቴን ባትሰሚ፤
ፍቅርሽን ለማግኘት፥
ልብሽን ለማግኘት፣ ባልወረውር ሎሚ . . . !*
በ’ርግጥ አንቺን አልኩኝ አንቺን ሸገሬዋ
የከተማዋን ፈርጥ እንቡጧን ማሬዋ . . .
*
ሸ- ገ – ሬ – ዋ
እንደዚያች ባተሌ …
አቀበቱን ወጥተሽ፣
ቁልቁለቱን ወርደሽ፣
ማገዶ ባትለቅሚ፣ ከጉድባው ባትፈልጪ፤
ኬሻሽን ዘርግተሽ፣ እህል ባታሰጪ፤
እንክርዳድ ባትለቅሚ፣
ባትከኪ፣ ባትወቅጪ፤
ወገብሽን ጠፍረሽ፣
ወፍጮ ላይ አቀርቅረሽ፣ መጅሽን ባትገፊ፤
ራስሽን ሸብ አ’ርገሽ፣
ጥሬ ባታነፍሺ፣ በወንፊት ባትነፊ፤
ላባወራሽ ክብር
በጭስ ተጨናብሰሽ ቤት ለቤት ባትለፊ::*
መቼም አንቺን አልኩኝ ሁኚኝ እማወራ
አቤት አቤት ልበል ያዘዝሽን ልስራ . . .(አብዲ ሰዒድ
ካዛንቺስ – አዲስ አበባ
ታህሳስ – 2001 E.C)
 
Leave a comment

Posted by on November 3, 2012 in ግጥም

 

ሰላም !

የተሰማንን እንተነፍሰው ዘንድ ሰዋዊ ተፈጥሯችን ግድ ይለናል!… አረረም መረረም እንዳሰብነው እንፅፋለን!… እንደፃፍነውም እናስባለን!… ሁሌም ሰላም!…. ሁሌም ፍቅር ለሁላችን!… ሰላምና ፍቅር እስካለን ድረስ ብዙ ገር ነገሮችን በገር ልቦና እንጋራለን…  ኢንሻአላህ!…

 
2 Comments

Posted by on November 2, 2012 in ስብጥርጥር