RSS

Monthly Archives: March 2013

እትዬ አዛለች . . .

lie
የአድባሯ እመቤት እትዬ አዛሉ
አራት ክብሪት ጭረው አገር አቃጠሉ። 

ይኸው ሲያር ይስቃል ያገሬ ማሽላ 
ነበልባል ሲልፈው አካሉ ሲቆላ፤ 

አዛለች እንደሆን ከቶ ምን ገዷቸው
ወገን እያነባ ስድስት ነው ቀልዳቸው፤ 

አራትና ስድስት፣ ስድስትና አራት
ለደሃ ቤተሰብ መች ይሆናል ለ’ራት?!

መለስ ያለ እንደሆን የያዛቸው ጋኔል
ጸበሉ ካልሆነ ይወሰዱ አማኑኤል።

_________ / አብዲ ሰዒድ / _________

 
Leave a comment

Posted by on March 31, 2013 in ግጥም

 

ኮኤ ፉሺ ! . . . ሃኮ ፉሺ ! . . .

Image Picture source: google search!

በሲዳማ ዞን አርቤጎና ውስጥ በአገር ሽማግሌዎች የተከወነ የፍትሃዊ ምርጫ ሂደት ተመክሮ እንካችሁ…

ምርጫው ሊካሄድ ሁሉም ነገር ተዘጋጅቷል… አስመራጮች… ታዛቢዎች… ጸጥታ አስከባሪዎች… ሽማግሌዎችና ሌሎች የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ ቦታ ቦታቸውን ይዘዋል…. መራጩ ህዝብም የምርጫ ካርዱን እንደያዘ ተሰልፎ ይጠባበቃል… ምርጫው ይጭበረበራል፣ ኮሮጆው ሊቀየር ይችላል ብለው የሰጉት የአገር ሽማግሌዎች የራሳቸውን የፍትሃዊ ምርጫ መላ ዘይደዋል… ሁሉም ነገር መጠናቀቁን ሲያረጋግጡም ተነሱ…

ለጸጥታ አስከባሪዎችም አሏቸው: ”ቴኔ ኮሮጆ ሃዺ !” … በደምሳሳው ሲተረጎም ”ይህን ኮሮጆ ወዲያ አንሱት!”… ”ኮሮጆውን ውሰዱት!” እንደማለት ሊሆን ይችላል…

በመቀጠልም የለበሷቸውን ረጃጅም ቡሉኮዎች (ጋቢዎች) ለሁሉም ግልጽ በሆነ መሃል ቦታ ላይ አነጠፏቸው… ለፍትህና ለሃቅ ቆሙ… ለመራጩ ህዝብም አሉት…

”ኮኤ ፉሺ !…”
”ሃኮ ፉሺ !…”

በግርድፉ ሲተረጎምም :

” እዚህ አድርግ! … እዚችው ጣል !”
” እዚህ አስቀምጥ! … እዚችው ቁጭ አድርግ !” … እንደማለት ሊሆን ይችላል …

ሕዝቡ በሽማግሌዎቹ እምነት አለውና አላንገራገረም!… የፓርቲዎች አርማ ያለበትን ወረቀት ወስዶ… ሚስጥራዊ ክፍሏ ውስጥ ገብቶ… የሚመርጠው ምልክት ላይ የ X ምልክቱን አኑሮ… ወረቀቱን እያጣጠፈ ወደ ውጭ ይወጣል… ወደ ተዘረጋው ቡልኮ ላይ ሁሉም እያዩት ወርውሮ ይሄዳል… ሽማግሌዎቹም በንቃት ይጠባበቃሉ… ድንገት የሚያንገራግር… ከሂደቱ የሚያፈነግጥ ሲገኝም ሽማግሌዎቹ ይገስጹታል…

”ኮኤ ፉሺ !…”
”ሃኮ ፉሺ !…” … ይሉታል… ”እዚህ አድርግ! … እዚችው ጣል!” … ወይ ፍንክች!… እያሉ ይመልሱታል…

እንዲሁ ቀኑን ሙሉ ”ኮኤ ፉሺ !… ”ሃኮ ፉሺ !…” እንዳሉ ይውሉና ምርጫው ይጠናቀቃል… የድምጽ ቆጠራውም በሽማግሌዎቹ ዳኝነት ይከወናል… ኮሮጆ የሚባል ነገር ለምርጫው ቅንጣት አስተዋጽኦ ሳያደርግ ይውላል… ለማጭበርበር የተዘጋጁ ኮሮጆዎች ከነበሩም ውሃ በላቸው… በውጤቱም ባለ ዶሮ ምልክቱ የተቃዋሚ ፓርቲ ሲአን (ሲዳማ አርነት ንቅናቄ) አሸነፈ… ባለ ንብ ምልክቱ ተፎካካሪም ሽንፈቱን አምኖ ተቀበለ… ምንም መፈናፈኛ የለማ!…

መራጩ ሕዝብም አለ:

”ቢኒቾ ኢሽ !…”
”ሉኪቾ ሊሽ !…”

ሲተረጎምም…

”ንቧን ወደዚያ !…
ዶሮዋን ወደዚህ !…

እንደማለት ይሆናል… ንብ በሲዳምኛ ቢኒቾ ሲሆን ዶሮ ደግሞ ሉኪቾ ነው… ቋንቋውን በደንብ የምታውቁ ትርጓሜውን ብታርሙኝ ደስታዬ ነው …

”ኮኤ ፉሺ !…”
”ሃኮ ፉሺ !…” የሚሉ ሃቀኛ ዳኞች አያሳጣን አቦ!…

ሽማግሌዎቻችንን እድሜያቸውን ያርዝምልን !!!

”ቢኒቾ ኢሽ !…”
”ሉኪቾ ሊሽ !…”

በሰላም የተሞላ የሳምንት መጨረሻ ይሁንላችሁ!

አብዲ ሰዒድ 

 
Leave a comment

Posted by on March 30, 2013 in ስብጥርጥር

 

*** የጸጥታ ያለህ ?! ***

Image
ባለፈው ”በዣንዣድ ሰላም ሲናድ” ስል የዴርቶጋዳው ደራሲ በሐዋሳ ከተማ ስለከፈተው ”ዣንዣድ ባርና ሬስቶራንት” የቸከቸኳት ሚጢጢዬ ትዝብት ብዙ ሙገሳዎች እንዲሁም ድቆሳዎች አስነስታለች… እሰይ እንኳን አስነሳች!… ሙገሳውም ትንኮሳውም በቀና ልቦና እስከተንሸራሸረ ድረስ ለሚፈለገው ለውጥ የበኩሉን አስተዋጽኦ ያበረክታልና! 

በበኩሌ ይስማዕከ ደራሲ ነውና አይነግድ!… ደራሲ የሆነ ሰው ከወረቀትና ከእስክሪብቶ በቀር ሃብት ሊኖረው አይገባም!… የህዝብ ልጅ ነውና ሲታመም በልመና ይታከም!… ሲሞትም ለቀብሩ ማስፈጸሚያ እርዳታ ይሰብሰብለት!… ደራሲ ነውና በድህነት ይፎክት!… ስለምን ይነግዳል?!… ስለምንስ ራሱን በሃብት ያበለጽጋል?!… አላልኩም!… አልወጣኝም!… ይቺው ሚጢጢዬ የሰውነት ልኬም እንደሱ እንድል አትፈቅድልኝም!… በፍጹም!

የጥበብ ሰው ሲነግድና ሲያስነግድ… ወደ ተሻለ የኑሮ ደረጃ ሲሸጋገር… ጸሃፊያንን ያበረታል፣ ለዘርፉ መበልጸግም አዎንታዊ አስተዋጽኦ ያበረክታልና ወደ ንግድ ስራ ጎራ በማለቱ ልባዊ የሆነ ድጋፍ እንጂ ተቃውሞ የለኝም!… ነገር ግን ምንድነው የሚነግደው?… እንዴት ነው የሚነግደው?… የት ነው የሚነግደው?… የሚሉትን ጥያቄዎች ከሌላው ሰው በተለየ በትኩረት እጠይቃለሁ!… ምክኒያቱም ጥፋቱንም ልማቱንም የሚከተሉ ብዙ ተከታዮች አሉትና!… 

”ዣንዣድ ባርና ሬስቶራንት” የተከፈተው ፍጹም ሰላማዊ የሆነ መኖሪያ መንደር ውስጥ ነው… የአካባቢውን ሰው ሰላም እየረበሸ ነውና ተገቢ አይደለም!… ይህ አይነቱ ሰላምን የመንሳት ተግባር ደራሲ በሆነ ግለሰብ ሲፈጸም ደግሞ የበለጠ ያማል!… እናም የእርምት እርምጃ ሊወሰድበት ይገባል… ለዚህ ጉዳይ ቦታውን የሚፈቅዱ የስራ አስፈጻሚዎችም ሊያስቡበት መንግስትም ለድምጽ ብክለት ችግር አበክሮ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል ነው የኔ ሃሳብ!… አራት ነጥብ!

”ምነው መኖሪያ መንደር ውስጥ ጭፈራ ቤት ሲከፈት ብርቅ ነው እንዴ?… እኛ ያደግነውስ ከግድግዳችን ጎን እየተጨፈረብን አይደለም እንዴ?… ምነው እስከዛሬ አላንገበገበህም?… ምነው በሌሎቹ ላይ አልተነሳህም?… ምን ደርሶ ለአካባቢ ሰላም ተቆርቋሪ ይመስል የግል ጥላቻህን ትቀባጥርብናለህ?!”… ጃስ ገለመሌ ላላችሁኝ ሁሉ… … 

“እኛ የምንፈልገው የተዛመተን እኩይ ተግባር የሚቀንስ፣ ለተሻለ ለውጥ የሚያተጋን እንጂ የሚያባብስ አውቆ አጥፊን አይደለም ነው መልሴ!… እንደ ወረርሽኝ የተዛመተ አጉል ተግባር ሁሉ ሃይ የሚል እስካልተገኘ ድረስ ልክ ነው ማለትም አይደለም!… ኧረ በህግ ልንላቸው ይገባል (ህጉ ባይኖርም!… ህጉ ባይተገበርም!…)” 

በየሰፈሩ የነዋሪን ሰላም የሚነሱ ተግባሮች ሞልተዋል… በሃይማኖታዊ ትምህርት… በንግድ እንቅስቃሴ… በፖለቲካ ቅስቀሳ እና በሌሎች በተለያዩ አጋጣሚዎች እየተሳበቡ የሚካሄዱ ረብሻዎች ልክ የላቸውም!… ለድምጽ ብክለት ያለን ምልከታ እጅግ አናሳ ከመሆኑ የተነሳ የየእለት ኑሯችን መደናቆር የበዛበት እንደሆነም አያጠያይቅም!… 

እናም እነዚህን የጤና ጠንቅ የሆኑ የመደማቆር ድርጊቶች ልናወግዛቸው ይገባል!… ባወገዝናቸው ልክ ወደ ሰላማዊ ኑሯችን እንጠጋለን… ሰባኪውም ያለ ብክለት ይሰብካል!… ነጋዴውም ያለ ብክለት ይነግዳል!… ተራማጁም ያለ ብክለት ይራመዳል!… ከድምጽ ብክለት የጸዱ ከተሞቻችንም ይበዛሉ!… ያብዛልን አቦ… 

ይህ ማለት ግን ትችቶች ሁሉ ስርአት በጎደለው መልኩ የግለሰብን ግላዊ ህይወት በሚያብጠለጥል ሁኔታ ይካሄዱ ማለት አይደለም… ደራሲውን በተመለከተም ምናልባት ስሜታዊ ሆኜ ስድብ ነገር ተጠቅሜ ከሆነ ከመናደድ የመነጨ ነውና ይቅርታ!… እታረማለሁ!… የጻፉኩት በሙሉ ግን ያየሁትን አንዳች ነገር ከራሴ አልጨመርኩም!… እታረማለሁ ስል ለስሜታዊነቱ ብቻ ነው!

ያነሳሁትን ጉዳይ ግን አሁንም ደግሜ አነሳለሁ… የሰፈር ሰላም ሊነሳ ፈጽሞ አይገባም!… ይህ አይነቱን የግዴለሽነት ተግባር ከደራሲ አልጠብቅም!… እናም ወይ ድርጅቱን ያስተካክል አልያም ለጫጫታና ለዳንኪራ በሚመቸው ሰፈር ወስዶ ይክፈተው… 

የሆነው ሆኖ ሃላፊነት የሚሰማው አስተዳደር ባይኖር እንኳ በሃላፊነት መነገድ የባለ ህሊና ግዴታ ይመስለኛል!… እናም ለድምጻችን ለከት እናብጅለት… 

መልካም ቅዳሜ!

አብዲ ሰዒድ

 
1 Comment

Posted by on March 30, 2013 in ስብጥርጥር

 

በ – ዣ – ን – ዣ – ድ . . . ሰላም ሲናድ …!

terre22
እግር ጥሎኝ… ውበትና ተፈጥሮን አድሎኝ… በፍቅርና በሃሴት ተፍነክነክ ብሎኝ… ደልቶኝ… ሞቆኝ… ምችት፣ ምችትችት ብሎኝ… የሐዋሳ ሰማይ ስር ከርሜ ነበር:: ሐዋሳ ፍቅር እንደሆነች ባየኋት ልክ የምታስደስተኝ… በኖርኩባት ልክ የምትናፍቀኝ… በሸሸኋት ልክ የምታስጨንቀኝ… መሽቶ በነጋ ቁጥር ነገን የምታስመኘኝ የስስት ከተማዬ ናት::

አይደለም አሁን እንዲህ በአስፋልትና በውስጥ ለውስጥ የኮብል ስቶን ንጣፍ አሸብርቃ ይቅርና አቧራ እየለበስን፣ በጠራራ ፀሃይ እየተጠበስን፣ የሞላልን ቀን በጋሪ፣ ያልሞላልን ቀን በኮቴ አሸዋውን በሲሊፐራችን እየዛቅን ስናዘግም እንኳ ለፍቅሯ ጥግ አልነበረኝም… ያን ደማቅ ሰማያዊ የታቦር ሃይስኩል ዩኒፎርም ራሳችን ላይ ጣል እንዳደረግን ጀላቲ እየመጠጥን… አሊያም ሸንኮራ እየጋጥን… ሲደላንም የማዘር ቤትን የ60 ሳንቲም አምባሻ እየጎመጥን… በላዩ ውሃችንን አንዳንዴም ʿሴሏችንንʾ እየጨለጥን ጎዳናውን ስንሸከሽከው እንኳ ለፍቅሯ ልክ አልነበረኝም…

እንዲህ እንደዛሬው በባጃጅ ሽር በሚባልበት ወቅት ይቅርና የጡረታ ዘመኗ ባለፈባት ድክሞ ሳይክል SOSን አልፌ ጥቁር ዉሃ ድረስ ስንተፋተፍ እንኳ ለፍቅሯ የሚያህላት አልነበረኝም!… ዛሬም የሰላምና የደስታ ጥጌ ሐዋሳ ናት!… ሐዋሳ ሰላም… ሐዋሳ ፍቅር!…

እናም የሲዳማን የቆጮ ምግቦችና የወተት አይነቶች እያጣጣምኩ፣ የቶኪቻውን (የዮሐንስ በቀለን) ጫምባላላ እየዘፈንኩ ሐዋሳ ከርሜ ነበር… ምንም እንኳ በዛ ያሉ የጭፈራ ዘፈኖች ቢኖሩም ጫምባላላን ግን እጅግ እወደዋለሁ… ከባህል አንፃር ደህና ትርጉም ስላለው ይሆን?!…ነሸጥ ስለሚያደርገኝ ይሆን?!… እንጃ ብቻ!… “አይዴ ጫምባላላ” … “አይዴ ጫምባላላ” … ማለት እጅጉን ያስደስተኛል …

♫… ሻፌቱ ሺቄና ጊሩ ማሲሬና
አይዴ ጫምባላላ ኢሌ ኢሌ… ♫

♫… ሲዳማ ጎባያ ሲዳማ አዋሳ
ስንቅ ይዤልሻለሁ ስምሽ እንዲነሳ
ቡርሳሜ ናፍቆኝ ስመለስ ሲዳማ
በሩቅ እየታየኝ የታቦሩ ግርማ… ♫

♫… ሌምቦ … ሌምቦ …
ሌምቦ ሌላ ሌምቦ …
ሌምቦ … ሌምቦ …
ሌምቦ ሌላ ሌምቦ… ♫

♫… አይዴ ጫምባላላ
አይዴ ጫምባላላ… ♫

ጫምባላላ የሲዳማ ብሔር የዘመን መለወጫ በዓል በሆነው በፊቼ በዓል ማግስት የሚከበር እለት ሲሆን እለቱ ልጆች ˝አይዴ ጫምባላላ”… ˝አይዴ ጫምባላላ”… እያሉ በየቤቱ በመዞር የሚዘፍኑበት… የተዘጋጀላቸውን ባህላዊ ምግብ የሚመገቡበት… ከማንኛውም ስራ ነፃ የሚሆኑበት፣ የሚመረቁበትና የሚከበሩበት ዕለት ነው… በነገራችን ላይ የሲዳማ ብሔር የጨረቃን ኡደት መሰረት ያደረገ የራሱ የሆነ የዘመን አቆጣጠር አለው… ፊቼ እና ጫምባላላም ከዚሁ ዘመን አቆጣጠር ጋር የሚያያዙ የዘመን መለወጫ ክብረ በዓሎች ናቸው… በየአመቱ የፊቼ በዓል ሲሆንም በሐዋሳ ከተማ ወደ አሞራ ገደል በሚወስደው መንገድ ጀርባ ሃይቅ ዳር በተዘጋጀ ቦታ ላይ በዓሉ ይከበራል… እኛም ታድመን ኮምኩመነው ነበር… አቤት ደስ ሲሲሲልልል….!

እንዲያው እግረመንገዴን አነሳሁት እንጂ የተነሳሁትስ ስለ ሲዳማ ባህልም ሆነ ስለ ፊቼ ዘመን መለወጫ በዓል አከባበር ለማውራት አይደለም!… ይልቁንም ወደ አሞራ ገደል በሚወስደውና የአካባቢው ድባብ ሰላምን በሚያድሰው ጎዳና… የፊቼ በዓል በጀርባው በሚከበርበት ጎዳና… ሰላማዊ ውሎ ብሎም ነፍስን በሃሴት የሚሞላ ፀጥታ የሚፈልግ ማንኛውም ግለሰብ ዘና ብሎ የእግር ጉዞ በሚያደርግበት ጎዳና… ፀጥ እረጭ ያለ የሰከነ ኑሮ የሚፈልግ ሰው ቤት ኪራይ በሚፈልግበት ጎዳና… በአካባቢው መኖሪያ ቤት ያለው ሰው ረጋ ብሎ አትክልቶቹ ዙሪያ ተቀምጦ ስሜቱን በሚያዳምጥበት ጎዳና… ማንም አካባቢውን የሚያውቀው ግለሰብ ስለፀጥታው ሰላማዊነት በሚመሰክርበት በአሞራ ገደል ጎዳና ላይ በዴርቶጋዳው ደራሲ በፊታውራሪ ይስማዕከ ወርቁ አማካኝነት ስለተከፈተው ዣንዣድ ባርና ሬስቶራንት ላወራ እንጂ …

ዣ – ን – ዣ – ድ … ባ – ር . . .

ስለ ዣንዣድ ባር ከሰማሁበት እለት ጀምሮ ልጎበኘው እጅጉን እፈልግ ነበር… በየጥጋጥጉ ጭፈራና መሸታ ቤት በበዛባት አገራችን ቢያንስ ደራሲ የሆነ ሰው የሚከፍተው ባር ነፍስን የሚያድስ… በሙዚቃ ምርጫው መንፈስን የሚያረካ… የንባብ ባህልን የሚያበረታታ… የህብረተሰብን ንቃተ ህሊና የሚያጎለብት እንደሚሆንም ቅንጣት ጥርጥር አልነበረኝም!… ብቻ ልጎብኘው እንጂ ያለኝን አክብሮትማ እገልጽለታለሁ ስልም አስቤ ነበር… 

“… ዴርቶጋዳ … ዴርቶጋዳ
እንነጠቃለን ከተጫነን ፍዳ
ማንም ሰው ላይመጣ እኛን ለመለወጥ
አናፈገፍግም አናቅማማም ለለውጥ
ያቀረቀርክበት አንገት ያስደፋህ ቀን
ነግቷል ብለህ ተነስ ፍዳና ሰቀቀን …”

እኒህንና መሰል የለውጥ ግጥሞችን የጻፈ ገጣሚ… የወጣቱ መለወጥ የሚያንገበግበው ደራሲ… የከፈተው ባርማ በእርግጥም የሚበረታታ እንደሚሆን ለመገመት አላንገራገርኩም!… ነገሩ ግራ የገባኝና የተገላቢጦሽ የሆነብኝ ግን ገና ዣንዣድ የተባለውን ባር በራፍ ስረግጥ ነው …

ዣንዣድን የጎበኘሁት በማታ ነበር… በግምት ከምሽቱ 2 ሰዓት ገደማ ይሆናል… ከአንዲት ሐዋሳ ከምትኖር ወዳጄ ጋር ነበርኩኝ… ገና ወደ ውስጥ እንደዘለቅኩ የዋት መጠኑ በውል ከማይታወቅ ʿትልቅ ሞንታርቦ እስፒከርʾ የሚለቀቅና የጆሮን ታምቡር የሚበጥስ ለዛ የሌለው ሙዚቃ ከሚሰነፍጥ ትንፋግ ጋር ተቀበለኝ… እንደምንም መቀመጫ አግኝተን እንደተቀመጥን…

እኔ: ˝እርግጠኛ ነሽ ግን ዣንዣድ ባር ይሄ ነው?!˝ ስል ወዳጄን በጥያቄ አጣድፋት ገባሁ… እስፒከሩ ሲያምባርቅብኝ የሳልኩት ዣንዣድ አፈር ከዲሜ ሲግጥብኝ ይሰማኛል …

ወዳጄ: “እንዴ አዎ ተረጋጋና በደንብ ተመልከተው እንጂ!”… ʿገና ምን አይተህ!… እኛም እንዲህ ነው የተሸወድነውʾ በሚል ቅላጼ!…

የወዳጄን ንግግር ተቀብዬ ዙሪያዬን ስቃኝ… መጽሃፍ ይዞ የቆመ ቅርጽ… የተለያዩ ደራሲዎችና ፈላስፎች ፎቶ… በቅርጽ የተሰራ ጣራ… አንዳች ነገር የተለበጠበት ግድግዳ… ድንግዝግዝ ያለ ክፍል… ብልጭ ድርግም የሚሉና የውስጥን ሰላም የሚያውኩ መብራቶች… ልጅነታቸው የሚያሳሳ ቢጢቆ ጉርድ የለበሱ ጨቅላ ሴት አስተናጋጆች (የትምህርት ቤት ዩኒፎርም የለበሱ የሚመስሉ)… ቅርጻ ቅርጾች… እና ወዘተ…. ነገሮችን ተመለከትኩኝ…

በʽርግጥ ቤቱ ያምራል… ለቤቱ ውበት የተሰጠው ግምትም ደስ ይላል… ብልጭ ድርግም የሚለው መብራትም የሆነ ቅርጽ እንዲሰራ የተፈለገ እንደሆነ ያስታውቃል… ምን አይነት ቅርጽ እንደሆነ የማይበትና የማገናዝብበት ትዕግስት ግን አልነበረኝም… ዴር33 ይሁን?!… ብቻ እንጃ!… በውስጠኛው ክፍል ያለማቋረጥ ብልጭ ድርግም ሲል ይታየኛል…

ወደ ውስጠኛው ክፍል ዘለቅኩ… ገና ስገባ የረበሸኝን አይነት ሁለተኛ ስፒከር እዚህም ከጣራ በላይ ያምባርቃል… እዚህም እዛም ወጣቶች ይደንሳሉ… ባንኮኒውን ከበው የሚጠጡም አሉ… የሚተሻሹ፣ የሚደባበሱ ጥንዶችም ይታዩኛል… መቀመጫ እንደሚልግ ዘወርወር አልኩና ወደነበርኩበት ወደ ሳሎኑ… ወደ ሶፋ መቀመጫዬ ተመለስኩ … ስቀመጥ ከበላዬ የጋሽ ስብሓት ምስል ይታየኛል…
ስሜቴ ተደበላለቀብኝ… የቤቱ ሁሉ ነገር አስጠላኝ… በዚህ ጥግ ካሸር… በዚያ ጥግ አልኮል ቀጂ… በሌላኛው ጥግ የጄኔሬተር ቤት… በአራተኛው ጥግ ሰላም የሚነሳ ስፒከር… በሌላኛው ክፍል ደሞ ሌላ ስፒከር… ደሞ ሌላ ረብሻ… ደሞ ሌላ መደነሻ… የሚያሳሱ አስተናጋጆች ብቻ ስብሰከሰክ የታዘዘችን አስተናጋጅ ምግቡንና መጠጡን እያቀራረበችልን ነበር… ጥያቄዬን አግተለተልኩላት…

እኔ: እኔ ምልሽ እናት በየት በኩል ነው ቤተ መጽሃፍቱ?
አሷ: እ…እ?!… እሱ እዚህ አይደለም ሌላ ቦታ ነው…
እኔ: ሌላ ቦታ?… የት?… (ሌላም ባር አለው ይሆን እያሰብኩ)…
እሷ: እ…እ? እኔጃ ግን አለ…
እኔ: እሺ እሺ … እዚህ ቤት ምንም የሚነበብ ነገር የለም?
እሷ: እ…እ?… የለም!…
እኔ: ሁሌም እንዲህ አይነት ሙዚቃ ነው የምትከፍቱት?
እሷ: እ…እ…?! አዎ!… ምነው ጥሩ አይደለም?… ዘፈን ላስቀይር?
እኔ: አይይ ትንሽ ድምፁ በዛ ብዬ ነው… እስቲ ቤቱ ምን የተለየ ነገር አለው?… አስጎብኚን?
እሷ: እ?… ዋሻውን አይታችሁታል?… በውስጥ በኩልʿኮ ዋሻ አለ…
እኔ: አይ አላየነውም… ዋሻው ውስጥ መቀመጥ ይቻላል?
እሷ: አዎ!… እዛም ልትዝናኑ ትችላላችሁ… አሁን ግን ጨለማ ነው… (በድንገት መብራት ጠፍቶ ጄኔሬተሩ እያምባረቀብን ነበር)
እሺ: እሺ እናመሰግናለን . . . 

የተባለውን ዋሻ ላየው ብፈልግም ወደ ውስጥ መዝለቁ አስጠላኝ… ከቤቱ ድባብ ስነሳ ባየውም የተለየ ነገር ጠብ የሚልልኝ አልመስልህ አለኝ… ደግሞም የአስተናጋጇ ˝ልትዝናኑ ትችላላችሁ˝ አባባል አላስደሰተኝም… ደሞ ሌላ ብስጭት ራሴ ላይ መጨመር አልፈለግኩም… እናም ያለማቋረጥ በሚያባርቀው ሙዚቃ እየተደናቆርን ከወዳጄ ጋር መደማመጥ እስኪያቅተን እየተጯጯህን ማውራታችንን፣ መብላት መጠጣታችንን ቀጠልን… ሙዚቃውም ያለማቋረጥ ማንባረቁን ቀጠሏል… ትዝ ከሚሉኝ ዘፈኖች መካከል የሚከተሉት ቁርጥራጭ ግጥሞ ች ይገኙበታል . . .

111 …
♫… ኤሶ … ኤሶ
ኤሶ ኤሶ ጦና ናታ ወላይታ

ዱርሳ ዱርሳ … ወላይታ…♫ 
ዱርሳ ዱርሳ … ወላይታ …♫

♫… ኪኪያ ዳሞታ
አዋንዳይ አዋንዳይ… ♫

222 …
♫… ትብላው ብሬን
ትብላው ብሬን
ለኔስ ግድ የለም
ትብላው ብሬን… ♫ 

♫… Chop my money
… Chop my money
… Cuz I dont care…
… I don’t care… ♫
… I don’t care… ♫

333 …
♫… ሻላዬ ሻላዬ ዮ
… ቴ ሻላዬ
… ሻላይቱ ገላ ዮ
… ቴ ሻላይ …♫

♫ … ዲላ ላይ… ዲላ ላይ… ዲላ ላይ…
… ዲላ ላይ… ዲላ ላይ… ዲላ ላይ… ♫

♫… ኤ አና ዴስኮ
ኤ አና ዴስኮ… ♫

እኚህንና መሰል የጭፈራ ዘፈኖችን እየከፈቱ ለማደናቆር ለምን ያን የመሰለ ሰላማዊ መንደር እንደተመረጠ ሊከሰትልኝ አልቻለም… ለዚህ ለዚህማ እነ ከላይ… እነ ቁልቢ… እነ ፍቅረ ሰላም… እና ሌሎች መሰል ጭፈራ ቤቶች የተኮለኮሉበት በተለምዶ ቤርሙዳ ሰፈር የሚባለው የሐዋሳ የጭፈራ መንደር አይሻለውም ነበርን?!… የሰፈር ሰላም መንሳት ምን ይባላል?!… ድንቄም ደራሲ እቴ!… እንዲህም አድርጎ ለወገን ተቆርቋሪነት የለ!… ቆሽቴ እርር ድብን አለብኝ…

ሂሳባችንን ከፍለን ለመውጣት ተጣራሁ… ያቺው አንድ ፍሬ ልጅ የልጅ ፈገግታዋን ይዛ ከች አለች… ጥቂት ላወራት ፈለግኩ…

እኔ: እናመሰግናለን… እንደው በቀን ብንመጣስ ምን ምን አላችሁ?!
እሷ: ሁሉም ነገር አለን…
እኔ: ቆንጆ ቡና አላችሁ?
እሷ: ውይይ ትኩስ ነገር የለንም…
እኔ: እንዴ ለምን?! … ”ይሄኔ ነው መሸሽ”… 
እሷ: አይ ለጊዜው ማሽናችን ተበላሽቶ ነው ይኖረናል…
እኔ: እሺ እንደው መልዕክት ብነግርሽ ለደራሲውና ለቤቱ ባለቤት ታደርሺልኛለሽ?
እሷ: ኧረ አዎ
እኔ: አረቄ ቤት ለመክፈት ደራሲ መሆን አያስፈልግም!… የመንደር ሰላም ለመረበሽ መጽሃፍ መቸርቸር አያስፈልግም!… ድርጅትህን የደራሲ የደራሲ ልታደርገው የማትችል ከሆነ ዝጋው!… ለወገን በቃላት ጋጋታ ያሰቡ ከመምሰል በፊት በተግባር ማሳየቱ ይቀድማል… በይልኝ አደራ!… ትነግሪዋለሽ ግን?…
እሷ: እንዴ አዎ!… እንዲሻሻል አይደል እንዴ?!… ሂሳቧን እየተቀበለችን… በክብር እየተሰናበተችን… አሳሳችኝ… በግምት 20 ዓመት የማይበልጣት እምቡጥ ናት… የልጅነት ወዟን በከንቱ ስማቸውና ገንዘባቸው አሳስተው ከሚቀራመቷት ክፉ አይኖች አንድዬ እንዲጠብቃት እየተመኘሁ ወጣሁ… መልካም ይግጠምሽ የኔ እህት!!!


ከወዳጄ ጋር እያወጋን ተመለስን… እሷም እንደኔው የጠበቀችውና የገጠማት አልጣጣም ብሏት ከምርቃቱ ጊዜ ወዲህ ዝር ብላ እንደማታውቅ ነገረችኝ… ˝ዛሬም ያንተን ስሜት ማወቅ ስለፈልግኩ እንጂ ባልመጣ ደስታዬ ነበር˝… ስትል ብስጭቷን አጠናከረችልኝ 
እንደተብሰለሰልኩ አደርኩ… ግን ቆይ ምን አግብቶኝ ነው የምቃጠለው?! ታዋቂ ሆነ!… ዝናውን ቢዝነስ ማድረግ ፈለገ!… እናም ጠጪ እስካገኘ ድረስ… ከልካይ እስካልገጠመው ድረስ… ያሻውን እያደረገ የቻለውን ያህል ገንዘብ ቢያግበሰብስስ?!… ስል አሰብኩ… ብሽቅ ደራሲ!… በበኩሌ ከመጀመሪያው ዴርቶጋዳ በቀር ሌሎቹ የ ”ቶ” ዲስኩሮች ባዶ እንቶፈንቶ እንደሆኑብኝ ሳስብ የበለጠ አበገነኝ… በተለይ ዣንቶዣራ የተባለው ቁጥር 3 ዴርቶጋዳ ለአንባቢውም ሆነ ለጥበብ ያለውን ንቀት ደህና አድርጎ ያሳየበት የልጅ ጨዋታ እንደሆነ ሲታወሰኝ ˝ድሮም ልጅ ያቦካው ለራት አይበቃም!˝ የምትለኝ አያቴ ታወሰችኝ… እናም በጥበብ እንዲያድግና የተሻለ ነገር እንዲሰራልን ብሎም የሰፈር ሰላም የነሳበትን ባር ተብዬ የሰፈሩንም የደራሲንም ክብር በሚመጥን የተሻለ ቤት ይለውጥልን ዘንድ ልቦና እንዲሰጠው ዱዓ አደረግኩለት…

ለቁርስ ወደቀጠረኝና የህግ ባለሙያ ወደሆነው ወዳጄም ተጣደፍኩ… ስለ ዣንዣድ የታዘብኩትን እና የበገንኩበትን አወጋሁት… እህህ ብሎ ካደመጠኝ በኋላ አንገት የሚያስደፋ ነገር ጨመረልኝ…

እሱ: ቀድመህ ብትነግረኝ ኖሮ ድርሽ እንዳትል እነግርህ ነበር… የክስ መዝገቡ እኮ ገና አልተዘጋም!… አለኝ
እኔ: እንዴ የምን ክስ?!
እሱ: ያካባቢው ሰዎች የመንደራችንን ሰላም ረበሸ… በሰላም መተኛት አልቻልንም… ኧረ በህግ!… አንድ በሉን… በምሽት ያለቅጥ የሚከፍተውን ሙዚቃ ይቀንስልን… አልያም ድርጅቱን ይዝጋልን… ሲሉ የከሰሱበት መዝገብ ነዋ!… ባክህ ልጁ ዝናና ገንዘብ እንዳያስብ ሳያደርጉት አልቀሩም … ያሳፍራል!

የምሬን አፈርኩ!!!… አዘንኩ!… አቀረቀርኩ!… በዝና አልያም በንዋይ ፍቅር ደንቁረው ከሚያደነቁሩን ይታደገን ዘንዳም ጸለይኩ!!!…

“ቱ በል!… ቱ!…
አለችው እናቱ …”
ብሎ እንዳለኝ ጸሃፊ
እንዳስተማረኝ ያ ገጣሚ
እውነት ጥበብን አታሚ
ህጸጽን በወግ ኮርኳሚ…

˝ቶ!…˝ በል እስቲ አንተ ሎጋ
˝ቶ!…˝ ባለ ነው ያኛው ለጋ
አገር ምድሩን ያንጋጋ
ከልሒቅ ተርታ የተጠጋ
የሰፈር ሰላም ያናጋ …

እናም ˝ቶ!˝ በል እስቲ …

ቶ ፊደል ነው የቃል አቻ
የቅንጣት ሚስጥር መፍቻ
የረቂቅ ጥበብ መግቻ
የዝና ጥማት ስልቻ
የንዋይ ማቆር ዘመቻ …

ቻ ቻ ቻ
ቻ ቻ ቻ
ከንቱ ከበር ቻቻ
ባዶ ወሬ ብቻ . . .
ልብ አይንሳው ብቻ !!!

_________//_________
አብዲ ሰዒድ

 
4 Comments

Posted by on March 25, 2013 in ስብጥርጥር