RSS

Monthly Archives: April 2013

ያገለገሉ ፓንቶች ሽቀላ . . .

እዚህ እኔ ያለሁበት አገር አገልግሎት የሰጡና የተጣሉ ፓንቶች ይነገዳሉ!… ይሸጣሉ!… ይለወጣሉ!… ገንዘብ ያመጣሉ!… ቀልድ እንዳይመስላችሁ የምር ነው!… ንግድ ፈቃድ ማውጣት ሳያስፈልገው… ግብር እንዲከፍል ሳይገደድበት… የስራ ቦታ ማደራጀት ግድ ሳይለው በቀላሉ ገንዘብ ማግኘት የፈለገ የትኛውም ግለሰብ ያለማንም ከልካይ ወደ ፓንት ሽቀላ ስራ ሊሰማራ ይችላል… 

ለዚህ ስራ የሚያስፈልገው ነገር ቢኖር ቆራጥነት ብቻ ነው!… በየጎዳናው የሚገኙ የሕዝብ ቆሻሻ መጣያ ሳጥኖችን እየከፈቱ ፓንት ለመፈልግ የሚያስችል ቆራጥነት… ከየቆሻሻ ዉስጥ የሰበሰቧቸውን ፓንቶች በፌስታል፣ በቦርሳ አልያም ባመቸ ነገር ቋጠር አድርጎ ለመንቀሳቀስ የሚያስችል ቆራጥነት… በየገበያ ማዕከሉ በተተከሉ የፓንት መግዣ ማሽኖች ፓንቶቹን አንድ በአንድ እየደመሩ ለመክተትና ደረሰኝ ለመቀበል የሚያስችል ቆራጥነት… ምናልባት ማሽን የተፋቸውና ቃርዳ የወጡ ፓንቶች ቢኖሩ አሊያም ፓንት ሳይሆኑ ከፓንት ጋር ተደባልቀው የተሰበሰቡ ቢያጋጥሙ እነሱን በአግባቡ ወደቆሻሻ ማስወገጃ ሳጥኖች ለመጣል የሚያስችል ቆራጥነት… 

እንግዲህ ይህ ቆራጥነት ያለው ማንኛውም ሰው ዛሬዉኑ የፓንት ስራን መጀመርና ሽቀላውን ማጧጧፍ ምርጫው ነው… ለበለጠ ውጤታማነት በሳይክል አሊያም መሰል ተሽከርካሪ መንቀሳቀስ ይመከራል… የበዙ የቆሻሻ መጣያ ሳጥኖችን ለማዳረስ ከማስቻሉም በላይ ፓንቶቹን በቀላሉ ለመያዝ ያመቻልና … 

“አበስኩ ገበርኩ ጌታዬ!… ምኑን ታሰማኛለህ!”… “የተጣሉ ፓንቶች ንግድ?!… ፓንትም ደግሞ ሊለበስ?!”… “ሆሆ ጆሮ አይሰማው የለ መቼም!”… “ወይ ጉድ!… ጉድ እኮ ነው!”… “አኡዙቢላሂ!… ኧረ ይሄስ ስራ ተብሎ አይወራም!”… “አቦ ንካው እንዲህ አይነት ሂራር አታውራብን!… ወላ ሳይሰራ ቢቀርስ!”… እና መሰል ግርምቶች እየተባሉ ሊሆን ይችላል… ግን ስራ ነው!… ፈረንካው ይሸቀልበታል… 

ባንግላዴሹ… ፓኪስታኑ… ህንዱ… ካሜሮኑ.. ጋናው… ናይጄሪያው… ታይላንዱ… ፖላንዱ… ፊንላንዱ… ስፓኞሉ… ስውዲኑ… ኖርዌዩ… ቱርኪው… እና ሌሎች በርካቶች ፈታ ዘና ብለው ለቀማቸውን በጠራራ ጸሃይ ሲያቀላጥፉት ቀብራራው የሃበሻ ልጅ ግን እምብዛም አይደፍረውም…. ታጥቦ ታጥኖ ደጁ ላይ የተከመረው ቆሻሻ ልብሱን እንዳያበላሽበት እየዘለላት ያደገው ኩሩው የኢትዮጵያ ልጅ ግን ይህችን ይህችን አይነት ስራ ንክችም አያደርጋት!… እንደው አልፎ አልፎ አፈንጋጭ ካልተገኘ በስተቀር!…

“ዘ ይግረም ነገር እኮ ነው!”…. “አጃኢበ ረቢ!”… ምናምን ብላችሁ ሳትጨርሱ ካፋችሁ ልንጠቃችሁና ልቀጥል… 

ፓንት ሲባል እኛ በለመድነው እና በምናውቀው አማርኛችን እንደሚገባን የውስጥ አልባስትን የሚገልጽ ቃል አይደለም… ፓንት ባገርኛው ቋንቋ የታሸጉ መጠጦች ከተሸጡና ከተጠጡ በኋላ እቃዎቹ ለዳግም አገልግሎት ይውሉ ዘንድ ያላቸው ዋጋ ማለት ነው… 

ባብዛኛው የታሸጉ መጠጦች የዳግም አገልግሎት ዋጋ አላቸው… የተለያዩ አይነት ለስላሳ መጠጦች… ቢራዎች… ዉሃዎች… ቫይታሚኖች… ጁሶች… ኢነርጂዎች… እና መሰል መጠጦች እሽጋቸው ላይ የፓንት ዋጋቸው ተጽፏል… እንደው ለምሳሌ ብንወስድ አንድ ባለ ሁለት ሌትር ኮካ ኮላ ገዝተን ከተጠቀምን በኋላ ኮካውን ይዞ የነበረው ፕላስቲክ ማሸጊያ በሁለት የስውዲን ክሮኖር (ወደ 6 ብር ገደማ) ይሸጣል… እና ይህ ነው ፓንት ማለት… የተጠቀሙበት ማሸጊያ ላይ PANT የሚል ጽሁፍ ከዋጋ ጋር ከተለጠፈበት ይሸጣል…. ወደ ገንዘብ ይለወጣል… ፕላስቲክም… ቆርቆሮም… ጠርሙስም ሊሆን ይችላል… 

የኔ ቢጤ ቋጣሪ የሆነ ሰው የጠጣባትን እቃ እቤቱ እያጠራቀመ ሰብሰብ አድርጎ ይሸጥና አስቤዛውን ሊሸማምትበት ይችላል… እንዴ ገንዘብ ነዋ!… መጀመሪያ ተከፍሎበታላ!… ገንዘብ እንዴት ይጣላል?… ወላሂ ሃራም ነው!… እንዲህ የማጠራቀም ትግስቱም ፍላጎቱም የሌለውና በየአጋጣሚው መንገድ ላይ ገዝቶ የሚጠቀመው ግን በየቆሻሻ መጣያው ይጥላቸዋል … ፓንት ሸቃዩ ደግሞ እያሳደደ ይለቅማቸዋል… ከዚያም ወደ ማሽኑ ያስገባቸዋል… ማሽኑም ደረሰኝ ይተፋለታል… በደረሰኙ ያሻውን መግዛት አልያም ፈረንካውን መቀበል ምርጫው ነው… 

በነገራችን ላይ ማሽኑ የእርዳታ አማራጭም አለው… የፓንቱን ገንዘብ መውሰድ የማይፈልግ ፓንቶቹን አምጥቶ ማሽን ውስጥ የሚጨምራቸው እቃው ለዳግም አገልግሎት ይውል ዘንድ ያለበትን ሃላፊነት ለመወጣት እንጂ ለገንዘብ ሽቀላ ካልሆነ… ለተራቡ… ለተጠሙ… እና ለተቸገሩ ህጻናት መርጃ ይውል ዘንድ ማበርከት ይችላል… ፓንቶቹን አስገብቶ ሲጨርስ የቢጫዋን በተን መጫን ብቻ ነው የሚጠበቅበት!… የረዳውን የብር መጠን የሚገልጽ የምስጋና ደረሰኝ እጁ ላይ ይወድቅለታል…. ግለሰቡም አከባቢውን ከቆሻሻ ታድጎ እግረ መንገዱንም የተቸገረን ህጻን ረድቶ ይመለሳል…. 

ዋናው ጉዳይ ለሸቃዩ የሚያስገኘው ገንዘብ ብቻ አይደለም!… ከአካባቢ ብክለት የጸዳች ከተማን ለመስራት ያለው አስተዋጽኦም ጭምር እንጂ!… ቸልተኛው ቢጥለው ገንዘብ ፈላጊው ያነሳዋል… በአግባቡም ለዳግም አገልግሎት እንዲውል ያደርገዋል… ከዚያም ለዚህ ጉዳይ በተሰማሩ ባለሙያዎችና ማሽኖች ታግዞ ይጨፈለቃል… ይቀጠቀጣል… ዳግም ይሰራል!… ጠርሙስ፣ ፕላስቲክና ቆርቆሮ ነክ በሆኑ ቆሻሻዎች የበከተች ከተማ ማየትም ብርቅ ይሆናል… የሰለጠነ ቆራሊዮ ይሏል ይህ ነው!… 

ውይ ውይ አዲስ አበባዬ… ውይ ውይ መርካቶዬ… ውይ ውይ ፒያሳዬ… ውይ ውይ ካዛንቺሴ… ውይ ውይ ኢትዮጵያዬ!…. እናንተስ መች ይሆን እንዲህ ያለው ወግ ደርሷችሁ የማየው ስትል የግድህን ትጠይቃለህ… 

አቦ እንዲህ ሰልጠን ያሉ ቆራሊዮዎች ይኑሩን… ይምጡልን… ድንገት የማናውቃቸው ካሉም ይታወቁ… ይንቀሳቀሱልን… አካባቢያችንን ከብክለት… ከተማችንንም ከቆሻሻ ይታደጓታልና!
Image

ሰላም! 
አብዲ ሰዒድ

 
Leave a comment

Posted by on April 28, 2013 in ስብጥርጥር

 

መልከ ብዙ . . .

melkebezu
አንቺ መልከ ብዙ ውበትሽ በዛና

ወዝሽን ሰፈሩት በአሲዳም ቁና።

ዓይንሽን፣ ጥርስሽን፣ ጸጉርሽን እያሉ፣
የአካልሽ ቀበኞች ሰርክ ሲጋደሉ፣
ወይ አንዱ ድል ነስቶ በስስት ሳይዝሽ፣
እንዲሁ በከንቱ ደም ሲፋሰሱብሽ፣

ዘመን መሽቶ ነጋ።
ዘመን መሽቶ ነጋ።

አንቺም ከዘመን ጋር ውበትሽ ረገፈ፣
የሞተልሽ ቀረ፣
የተረፈው ንቆሽ ተራምዶሽ አለፈ።

____ // © አብዲ ሰዒድ // ____
ተጻፈ: 2003 እ. ኢ. አ
ኡፕሳላ፣ ስውዲን።

 
Leave a comment

Posted by on April 12, 2013 in ግጥም

 

___ “በጀት አልተያዘም።” ___

በእንትን ጦርነት፣ 

_ አhumanityደጋ ደርሶበት አካሉ የተጎዳ፤
ጠይቋቸው ኖሮ፣
_ የሚታከምበት ገንዘብ እንዲረዳ፤

እነ እንትና ሲመልሱለት …

“በጦርነቱ ወቅት ንጹሃን ሲመቱ፣
ብትመታም ያኔ ቢደርስም ጉዳቱ፣
ለጊዜው ላሁኑ በጀት የተያዘው
ሰለባ የሆኑት የሚታሰቡበት
__ ሐውልት ማሰሪያ ነው።”

___ // አብዲ ሰዒድ // ___
ተጻፈ: 1997 እ. ኢ. አ
መቐለ፣ ኢትዮጵያ
(የኑሮ ቀለም፣ 1998 እ. ኢ. አ)

. . . የሰው ፍቅር ያብዛልን… ለሐውልት ብቻ ሳይሆን ለሰዎች ደህንነትም በጀት የሚይዝ አስተዳደር ያስፋልን …

 
Leave a comment

Posted by on April 12, 2013 in ግጥም

 

ውቢቱ ጎጃሜ . . .

peace

♪♪ ውቢቱ ጎጃሜ 

. . . ውቢቱ ጎጃሜ
ትመጫለሽ በህልሜ ♪♪ 

♪♪ ዓለም ዓለምዬ 
ዓለም ዓለምዬ . . . 

እስቲ ዝምድናሽን ቆጥረሽ ንገሪኝ፤
ከእህት ከወንድሜ የበለጥሽብኝ።

እመጣለሁ ብለሽ መቅረትሽ ምነው? 
የነማንን ጸባይ ልታመጭብኝ ነው?!

ትሁኔ . . . ትሁኔ . . . 
አንቺ አትመላልሽ እምጠለሁ እኔ። ♪♪ 

. . . ከአሶሳ ማዶ ያለች ትንሽዬ መንደር ውስጥ ያንጎራጉራል… እንደወጣች ቀርታ… እንደዋዛ ጠፍታ ከቀዬዋ የተሰወረችበት የጎጃም ኮረዳ ስትናፍቀው ይተካክዛል… ተስፋዬ ወርቅነህ የተባለ ዘፋኝ ለሱ ብቻ የዘፈነለት ይመስለዋል… በዚያ በሩቅ አገር በመሃል አዲስ አበባ… በስም ብቻ በሚያውቀው ጎጃም በረንዳ ላይ ክርትት ብሎ የተከተተውን ይህን ቅን ዘፋኝ ፈጣሪ ነፍሱን ከደጋጎች ተርታ እንዲያሰልፍለት እየተመኘ ይቀጥላል…

“እውን ግን ተስፋዬ እጅግ ድንቅ የሆነ ድምጻዊ አይደለምን?… ድምጹ?… ግጥሙ?… ዜማው?…” እያለ ሊተነትን ይቃጣዋል… እራሱ ጠያቂ እራሱ መላሽ ይሆንና ሙዚቃ እናውቃለን የሚሉ ተንታኞች ስለዚህ ዘፋኝ ሲተነትኑ ሰምቶ ባለማወቁ ይንቃቸዋል… “አያውቁማ!… ሙዚቃ የት ያውቃሉ?… ዝም ብለው በመንጋ ወደነፈሰበት ያጨበጭባሉ እንጂ!” ይሳደባል… 

ምንም እንኳን ከአሶሳ ማዶ ቢኖር ስለ ወሎ፣ ስለ ጎንደር፣ ስለ ጎጃም፣ ስለ ትግሬ፣ ስለ ኦሮሞ፣ ስለ ደቡብ ህዝቦች የተዘፈኑ ዘፈኖችን አዘውትሮ ያደምጣል… ያቺን ውብ ጎጃሜ ከወደደ ወዲህ ደግሞ ጎጃም ጎጃም ማለቱ ብሶበታል… አሁን ግን ካጠገቡ የለችም!… ስትናፍቀው… ባይኑ ላይ ስትመላለስበት… ይይዘው ይጨብጠው ሲያጣ… ከአሶሳ ማዶ አያመጣት ነገር መላው ሲጠፋበት… ጠቅልሎ አይሄድ ነገር አቅሙም ጉልበቱም ሲያንሰው…. ዝምምም ብሎ ያንጎራጉራል… ምስጋና ለተስፋዬ ወርቅነህ… 

♪♪ አስደግመሽብኝ አለቃ ፈንቴን 
ሳር ቅጠሉ ሁሉ መሰለኝ አንቺን 
አስተብትበሽብኝ የኔ ኩንስንስ 
ወገቤ ያላንቺ አይንቀሳቀስ …

ትሁኔ . . . ትሁኔ . . . 
አንቺ አትመላልሽ እምጠለሁ እኔ። ♪♪ 

. . . እሷ ብቻ ሳትሆን የማያውቃቸው አለቃ ፈንቴ ይናፍቁታል… “ምነው ለኔም መተው በደገሙልኝ… ምነው በደገሙብኝ… ምነው በዚህ ሕዝብ ላይ ሁሉ የፍቅር፣ የሰላም፣ አብሮ የመኖር ድግምታቸውን በተበተቡበት… ምናለ ፍቅር በፍቅር ቢያንበሸብሹንና ያለ ፍቅር መንቀሳቀስ ቢሳነን” … … “አይ አለቃ ፈንቴ!… ይበሉ እስቲ!… ወይ እሷን ያምጧት ወይ እኔን ይውሰዱኝ… እስቲ እንዮት!… ይድገሙ!… እስቲ ይሄ እንጉርጉሮዬ እውን እንዲሆን ይተብትቡ!”… የቀትር ጸሃዩ እንደወረደበት በትዝታ ይንከላወሳል ተስፋዬም ያስታምመዋል…

♪♪ እናናንዬ … እናናኔዋ …
እናናንዬ … እናናኔዋ … 

ሰባት ሰዓት ሲሆን ከብት ውሃ ሲጠጣ፤
ደግሞ አገረሸብኝ ትዝታዬ መጣ።

አቤት ያንቺ ጸባይ ለፍቅር ሲመች፤ 
ድፍን የጎጃም ልጅ አለ ወይ እንዳንቺ። ♪♪ 

♪♪ እናናይ ነይ ነይ …
እናናይ ነይ ነይ …

ሃብትና ንብረትሽ ምን ያደርግልኛል?
ካንቺ ጋር አድሬ ብሞት ይሻለኛል። 

ጨረቃ ስትወጣ ስትንቀለቀል፤
ላርግሽ ከደሬት እንደብር መስቀል።

እናናይ ነይ ነይ … 
እናናይ ነይ ነይ … ♪♪ 

. . . እናና እያሉ የሚጠሯት እናቷ ሳይቀሩ ትዝ ይሉታል… ግልምጫቸው… ቁጣቸው… ኩርፊያቸው… አሽሙራቸው… ተረታቸው ሳይቀር እየተፈራረቀ ይመላለስበታል… ይህ የተፈጠረ ከንቱ እንቶ ፈንቶ… ይህ የተንሰራፋ አጓጉል ድንቁርና ወደሚሄድበት ሄዶ… ያመጣው ጋኔል በሚወጣበት ምሱ ወጥቶ… ዳግም ጎጃሚትን ሊቀበላት ይጓጓል… እንደሚሆን ደግሞ ጥርጥር የለውም!… ፍቅር ጥግ የለውማ!… ፍቅር አሸናፊ ነዋ!… ልክ ባለፈው እንደሆነው ተሰብስበው ሲመጡ ተሰብስቦ ሊቀበላቸው ይጓጓል… አበባ ይዞ ወደቀዬዋ ሲያደርሳት ይታየዋል… 

♪♪ ደሞ አለው አበባ 
ደሞ አለው አበባ
ጎጃሜው ሲገባ ♪♪

♪♪ ደሞ አለው አበባ 
ደሞ አለው አበባ
ጎንደሬው ሲገባ ♪♪ 

♪♪ ደሞ አለው አበባ
ደሞ አለው አበባ
ወለዬው ሲገባ ♪♪ 

♪♪ ደሞ አለው ደስ ደስ
ደሞ አለው ደስ ደስ 
አዲስ ላይ ስንደርስ ♪♪ 

. . . አዲስ መሄድ ያምረዋል… እዚህ እሷ የሌለችበት መንደር ውስጥ በትዝታ ከሚያላዝን የማንም ባልሆነችው ሸገር ላይ በባዱ ኪሱ መንሸራሸር ያምረዋል… “አፈር ምን ያደርጋል?… እርሻ ምን ይሰራል?… ንግድስ ምን ፋይዳ አለው?.. እኚህ ሁሉ ጥቅማቸው ትርጉም የሚኖረው በፍቅር ውስጥ አይደል እንዴ?!… ፍቅር ከሌለ ሁሉም የለም!… አለቀ… ደቀቀ!” ሊፈላሰፍ ይቃጣዋል… “ምድሪቷን የሰሯት ይመስል የኔ የኔ እየተባባሉ ይፋጃሉ… ከንቱዎች!… ይሄን ከንቱ ኮተታቸውን ወስደው ፍቅሬን በመለሱልኝ… ውቢቷ ጎጃሜን!… ድህነቴን የምታስረሳኝን ውዴን!” … 

♪♪ ዓለም ዓለምዬ 
ዓለም ዓለምዬ . . . 

ሰላሌ ራስ ካሳ ቢያስፈልጉ አጡሽ 
ጎንደር አጼ ፋሲል ቢያስፈልጉ አጡሽ
ጎጃም ራስ ኅይሉ ቢያስፈልጉ አጡሽ
ደቡብ ንጉስ ጦና ቢያስፈልጉ አጡሽ
የሸዋው ምኒሊክ ቢያስፈልጉ አጡሽ 
ደሃ ቁርጠኛ ነው እኔ አገኘሁሽ ♪♪ 

. . . ቁርጠኛነቱን የሰለቡበትን… ተስፋውን ያደበዘዙበትን ሁሉ ይራገማል!… በፍቅራቸው ላይ የተጋረጠውን ጋሬጣ ከመፍታት ይልቅ “ውሻ በቀደደው ምን ይገባበታል” እንደሚባለው አይነት አጋጣሚውን ተጠቅመው የነፍሳቸውን ከንቱ መሻት እየፈተፈቱ የበለጠ ሊያቆራርጧቸው የሚማስኑትን ሁሉ የበለጠ ይራገማል… ከንቱዎች! 

ልክ እሱ እዚህ ውቢቱ ጎጃሜን እንደሚያንጎራጉረው ሁሉ እሷም ፍኖተ ሰላም ላይ የምጽዋት ስንዴ እየተሰፈረላትም ቢሆን ዙምባራን እየዘፈነች እሱን እየናፈቀች እንደሚሆን ቅንጣት አይጠራጠረም… የዙምባራ ጭፈራዋ ሁሉ ይታየዋል . . . 

♪♪ ይኸው ተነሳሁ 
. . . ልሄድ አሶሳ 
__ ሲኞር ከተማ ማማይ …

ዙምባ በሉማ … ዙምባ በሉማ …
ዙምባ በሉማ … ዙምባ ዙምባ …

ሸኙኝ ወደዛ 
ትዝታው በዛ 
__ ሲኞር ከተማ ማማይ ..

ዙምባ በሉማ … ዙምባ በሉማ … 
ዙምባ በሉማ … ዙምባ ዙምባ …
.
.
.

ዙምባራ… ዙምባራ… ዙምባራ… ዙምባ… ዙምባ… 
ዙምባራ… ዙምባራ… ዙምባራ… ዙምባ… ዙምባ… 

ቤኒ… ቤኒ… ቤንሻጉል!…
ቤኒ… ቤኒ… ቤንሻንጉል!… ♪♪ 

ትታየዋለች!… ስትዘፍን… ስትጨፍር… ደግሞም የዘመን ኮተት ሲያስቆዝማት!… ይተካክዛል ተስፋው ግን አይደበዝዝም… የሱ አገር የሱ መንደር… ልቦናው ውስጥ ያለችው ፍቅር ናትና! . . . 

. . . 
ዙምባራና ጎጃም አንድም ሁለት ናቸው
የፍቅር ሰንሰለት ያስተሳሰራቸው
ማነው የሚበጥስ የልብን ቋጠሮ
ከአገር ይሰፋል ፍቅር እኮ ውሎ አድሮ:: 
. . . 

______ // አብዲ ሰዒድ // _____

 
Leave a comment

Posted by on April 7, 2013 in ስብጥርጥር