ይህ ፎቶ ታሪካዊ ነው። የኢትዮጵያ የሴቶች የማራቶን ጀብዱ በኦሎምፒክ መንደር ሲበረበር በቅድሚያ የሚገኘው ይህ ፎቶ ስለመሆኑ ምንም ጥርጥር የለኝም። ይህች ብርቅዬ ሴት በ23 ዓመቷ ኢትዮጵያ ከዚያ በፊት በሴቶች ማራቶን በኦሎምፒክ ውድድር አግኝታ የማታውቀውን ክብር አላብሳታለች።
እ. ኤ. አ በ1996 በአታላንታ ተካሂዶ በነበረው ኦሎምፒያድ ኢትዮጵያችን 2 የወርቅ ሜዳሊያ ነበር ያገኘችው። አንዱን ይህች የኔ ጀግና ፋጡማ ሮባ በማራቶን ስታስመዘግብ ሌላኛው ደግሞ በ10ሺህ ሜትር በኃይሌ ገብረ ሥላሴ ነበር የተመዘገበው። በዚያ ውድድር የጌጤ ዋሚን ነሃስ ጨምረን ባጠቃላይ ሦስት ሜዳሊያ ይዘን ተመልሰናል።
በወንዶች ማራቶን አበበ ቢቂላን በሮም እንደምንዘክረው፣ በሴቶች 10ሺህ ደራርቱን በባርሴሎና እንደምንዘክራት ሁሉ በሴቶች ማራቶን የምናነሳትና ፋጡማን ነው። አይና አፋሯ ፋጡማ ህያው ታሪክ ሰርታለች። እንስፍስፉ ደምሴ ዳምጤ ሲቃ እየተናነቀው የመጀመሪያዋ እያለ ያወራላት ፋጡማን ነው። ዋዋዋ ደምሴ አወራሩ መጣብኝ ;(
አሁን በቅርቡ ሎንዶን ላይ ያስቦረቀችን ቲኪ ገላና ከድሏ በኋላ በሰጠችው ቃለ ምልልስ ይህችን ብርቅዬ ሴት አልዘነጋቻትም –
“. . . ፋጡማ ሮባ የኔ ጀግና ናት፤ የርሷን ታሪክ በመጋራቴ እጅግ በጣም ደስተኛ ነኝ፤ ይህን የወርቅ ሜዳልያዬን ለሁሉም ኢትዮጵያውያን አበርክቻለሁ፡፡ . . . ” ቲኪ ገላና።
እነሆኝ እኔም ነገ (Aug, 2013) በሚጀመረው የሞስኮ 14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በውድድሩ መጀመሪያ ቀን ቲኪን ጨምሮ በማራቶን ለሚወዳደሩት ሴቶቻችን መልካም ውጤት ስመኝ ፋጡማን እያስታወስኩ ነው።
ሴቶቻችን ሆይ ብርታት፣ ጥንካሬ፣ መረጋጋትና ድል ከናንተ ጋር ይሁን!… ይቅናችሁ!
> ቲኪ ገላና ይቅናሽ !
> መሰለች መልካሙ ይቅናሽ !
> ፈይሴ ታደሰ ይቅናሽ !
> አበሩ ከበደ ይቅናሽ !
> መሠረት ኃይሉ ይቅናሽ !
> መሪማ መሐመድ ይቅናሽ !
(መሪማ ተጠባባቂ ናት)
ሁሌም ክብር ለጀግኖቻችን!
ሰላም ኢትዮጵያዬ ❤
___________
አብዲ ሰዒድ
ነሐሴ 2005 E.C