እዚህ ᎐ ᎐ ᎐
ነጋሪት፣ ከበሮ ፡ ሲጎሰም ሲመታ
ጋሻ ጦር ተሰብቆ ፡ ሲነፋ በእምቢልታ
መለከት፣ ጸናጽል፣ አታሞ ሻኩራ
በሕብረ ዝማሬ ፡ በመድፍ እያጓራ …
ሽለላ እየደራ
ሻማም እየበራ
ፉከራ ቀረርቶ ፡ ያፈኞች ቱማታ
እዩልኝ ስሙልኝ ፡ ያድር ባይ ድንፋታ
ያደነቁረናል ፡ ያለ ቅንጣት ፋታ !
ስሟቸው !…
“የምልጃ ታቦቴ
አድባር ጉልላቴ
ምልክቴ ጌጤ
ማተቤ ነህ ፈርጤ…”
ሲሉ ሲባባሉ
በስም ሲማማሉ
ሲ – ሸ – ነ – ጋ – ገ – ሉ !
ሲ
. . . ያ
. . . . . . ስ
. . . . . . . . . ጠ
. . . . . . . . . . . . ሉ !!!
እዚያ ᎐ ᎐ ᎐
እዬዬና መርዶ፣ የእድር ጡሩንባ
ያስለቃሾች ዋሽንት፣ ያላቃሽ አዞ እምባ
ለዛ የለሽ ዜማ፣ ጣዕም የለሽ ንፍሮ
ቅጥ የለሽ ንፍረቃ፣ ገጽ አልባ እንጉርጉሮ …
ዝርጠጣ፣ ፍርጠጣ
የስሜት ሽምጠጣ
ልዝቡን ከግልቡ ብረዛ ቅየጣ . . .
ደራሽና ገስጋሽ ፡ ላይሆኑ ዘላቂ
በጅምላ ሲነዱ ፡ ሕዝቤን አሳቃቂ
ደግሞም አስጨናቂ
“ስስ ብርሃን ፈንጣቂ”
ግርዶሽ አሟሟቂ
ውዥንብር ናፋቂ . . .
ስሟቸው !…
“ተፋጀ ተጣላ
እርስ በርስ ተባላ
ሞተ ተሰደደ
ተቃጠለ አበደ …
አትነሳም ወይ አትለውም ጎኑን
ደምህን ታቅፈህ ከምትድህ ዘመኑን”
እያሉ እያስባሉ እሳት እየጫሩ
በስም ላይ ስም ጭነው እየተሞሸሩ…
“አዋቂው … ልሒቁ
ረቂቁ … ምጡቁ
ታጋዩ … አርበኛው
የፍትህ እረኛው
አንተ ብቻ ዳኛው “
“ከኛስ ወዲያ ላሳር – ለሕዝባችን ግርማ
እጃችን ያልነካው – ሁሉም ነው ጨለማ።”
ሲሉ ሲፈርጁ በመንጋ ሲያስቡ
ጽድቅና ኩነኔን ባንድ ገጽ ሲከትቡ
ሲያረቁ ሲያፀድቁ
በቃል ሲያስመርቁ
ሲ – ያ – ጨ – መ – ላ – ል – ቁ !
ሲ
. . . ያ
. . . . . . በ
. . . . . . . . . ሽ
. . . . . . . . . . . . ቁ !!!
እዚያና እዚህ ሆኖ የህልማችን ጫፉ
ስንፋተግ አለን ቀኖች ሲቀጠፉ
እስኪ እንጠጋጋ ወፎቹ እንዳይረግፉ።
/ አብዲ ሰዒድ – 2005 E.C /