RSS

እዚህ እና እዚያ

26 Aug

እዚህ ᎐ ᎐ ᎐

ነጋሪት፣ ከበሮ ፡ ሲጎሰም ሲመታ
ጋሻ ጦር ተሰብቆ ፡ ሲነፋ በእምቢልታ
መለከት፣ ጸናጽል፣ አታሞ ሻኩራ
በሕብረ ዝማሬ ፡ በመድፍ እያጓራ …
ሽለላ እየደራ
ሻማም እየበራ
ፉከራ ቀረርቶ ፡ ያፈኞች ቱማታ
እዩልኝ ስሙልኝ ፡ ያድር ባይ ድንፋታ
ያደነቁረናል ፡ ያለ ቅንጣት ፋታ !

ስሟቸው !…
“የምልጃ ታቦቴ
አድባር ጉልላቴ
ምልክቴ ጌጤ
ማተቤ ነህ ፈርጤ…”
ሲሉ ሲባባሉ
በስም ሲማማሉ
ሲ – ሸ – ነ – ጋ – ገ – ሉ !


. . . ያ
. . . . . . ስ
. . . . . . . . . ጠ
. . . . . . . . . . . . ሉ !!!

እዚያ ᎐ ᎐ ᎐

እዬዬና መርዶ፣ የእድር ጡሩንባ
ያስለቃሾች ዋሽንት፣ ያላቃሽ አዞ እምባ
ለዛ የለሽ ዜማ፣ ጣዕም የለሽ ንፍሮ
ቅጥ የለሽ ንፍረቃ፣ ገጽ አልባ እንጉርጉሮ …

ዝርጠጣ፣ ፍርጠጣ
የስሜት ሽምጠጣ
ልዝቡን ከግልቡ ብረዛ ቅየጣ . . .

ደራሽና ገስጋሽ ፡ ላይሆኑ ዘላቂ
በጅምላ ሲነዱ ፡ ሕዝቤን አሳቃቂ
ደግሞም አስጨናቂ
“ስስ ብርሃን ፈንጣቂ”
ግርዶሽ አሟሟቂ
ውዥንብር ናፋቂ . . .

ስሟቸው !…
“ተፋጀ ተጣላ
እርስ በርስ ተባላ
ሞተ ተሰደደ
ተቃጠለ አበደ …

አትነሳም ወይ አትለውም ጎኑን
ደምህን ታቅፈህ ከምትድህ ዘመኑን”
እያሉ እያስባሉ እሳት እየጫሩ
በስም ላይ ስም ጭነው እየተሞሸሩ…

“አዋቂው … ልሒቁ
ረቂቁ … ምጡቁ
ታጋዩ … አርበኛው
የፍትህ እረኛው
አንተ ብቻ ዳኛው “

“ከኛስ ወዲያ ላሳር – ለሕዝባችን ግርማ
እጃችን ያልነካው – ሁሉም ነው ጨለማ።”
ሲሉ ሲፈርጁ በመንጋ ሲያስቡ
ጽድቅና ኩነኔን ባንድ ገጽ ሲከትቡ
ሲያረቁ ሲያፀድቁ
በቃል ሲያስመርቁ
ሲ – ያ – ጨ – መ – ላ – ል – ቁ !


. . . ያ
. . . . . . በ
. . . . . . . . . ሽ
. . . . . . . . . . . . ቁ !!!

እዚያና እዚህ ሆኖ የህልማችን ጫፉ
ስንፋተግ አለን ቀኖች ሲቀጠፉ
እስኪ እንጠጋጋ ወፎቹ እንዳይረግፉ።

/ አብዲ ሰዒድ – 2005 E.C /

Image

 
Leave a comment

Posted by on August 26, 2013 in ግጥም

 

Leave a Reply

Fill in your details below or click an icon to log in:

WordPress.com Logo

You are commenting using your WordPress.com account. Log Out /  Change )

Facebook photo

You are commenting using your Facebook account. Log Out /  Change )

Connecting to %s

 
%d bloggers like this: