RSS

Author Archives: ኬር ሃሳብ

ዘ – ም – ዘ – ም !

 

በዚያ ሐሩር ምድር፣ በዚያ ጠፍ በረሐ
ከደም ተቆራርጠው የሰው ልጅና ውሃ
ሕይወት ልታከትም ተይዛ ገርገራ
በዘምዘም ጠብታ ሕላዌዋ በራ።

ሃጀር ተራወጠች ሰፍዋና መርዋ
ለአንድ ልጇ ጥማት መች ዛለ ገላዋ
እሪ በል እስማኢል አልቅስ ተንዘፍዝፈህ
በእንባህ ዘለላዎች በል ያዛት ቀስፈህ።

እናት ዓለም ልፊ፣ ወዲህ ወዲያ ቃኚ፤
ያንቺን ጥማት ሽረሽ፣
በአሸዋው ዳክረሽ፣
ለአብራክሽ ክፋይ፣ ለእስትንፋስሽ ባክኚ።

በመካከል ሩጪ፣ በላይ ተራመጂ
ከወደዚህ ማትሪ፣ ደግሞም ከዚያ ሂጂ፤
ጠብቂው በዓይንሽ፣
ፈልጊው በእግርሽ፣
ርሃብ ጥማትሽን ለልጅ ፍቅርሽ ማግጂ።

አንድ! ሁለት! ሶስት! አራት!
ጉልበት እያጠራት . . .
አምስት! ስድስት! ሰባት!
ሕልሟ እየራቀባት …
ቀልቧ እየሳሳባት …
እ – ና – ት!
አቤት እናት!

በዚያ ሐሩር ምድር፣ በዚያ ጠፍ በረሐ
ከደም ተቆራርጠው የሰው ልጅና ውሃ
በዘምዘም አገኙት የነፍስን ፍሰኃ።

በል እስማኢል ጠጣ፣ ሃጀር ሆይ ጥገቢ
ላንቺም ለልጅሽም ዘምዘምን መግቢ።
እፈሽው በእጅሽ፣
አዳርሽው በዓይንሽ፣
ርኪበት በነፍስሽ፣
በአሸዋ፣ በኮረት፣ ከልይው በድንጋይ
የ’ናትነትሽ ጥግ ዝንታለም እንዲታይ።

“ዞሚ!” … “ዝሚ!” … “ዞሚ!” …
ድምፅሽን አሰሚ!
ትውልድሽን ካድሚ።

ተጓዥ መንገደኛው ይረፍ ባንቺ መንደር
“ሻባእ” “ሻባእህ” እያለ መርካቱን ይናገር።
ኃይል ብርታት ይሁን ለመኖርሽ ተስፋ
የጤናሽ ምልክት ይኑር እንዳይጠፋ።

“ዞሚ!”… “ዝሚ!”… “ዞሚ!”
ድምፅሽን አሰሚ!
ዓለምሽን ካድሚ።
___________
2006 E.C
አብዲ ሰዒድ
ኡፕሳላ፣ ስውዲን

HAPPY EID TO ALL MUSLIMS
❤ EID MUBAREK ❤

Image

 
2 Comments

Posted by on October 15, 2013 in ግጥም

 

ጀ – ሚ – ላ !

የዓይንን አሰራር ጥበብ ያላወቀ፣
የጥርስን ተፈጥሮ ልክ ያላደነቀ፣
የቁመናን ልኬት ሚዛን ያልጠበቀ፣
ጀሚላን ቢያገኛት አወቀም ፀደቀ።

ቁም ነገር ወዴት ነው በማን ተወሰነ?
መልካምነት የታል እንዴት ተከወነ?
እውቀትስ ምንድን ነው የት ተተነተነ?
ከጀሚላ ወዲያስ ይህ ሁሉ ባከነ።

አልሐምዱሊላሂ ደርሶናል በረካ
በጀሚላ ፍቅር ቀልባችን ተነካ።

የቀሚሷ ፀዳል፣ የሂጃቧ ግርማ
የእርምጃዋ ስክነት፣ የገጿ ከራማ
የአንደበቷ ለዛ፣ የቃሏ ጥፍጥና
ማር ተምር ቢሏትስ መች ይበቃትና።

በዚህ ቁንጅና ላይ የአምላክ ፍራቻ
ተጣጥባ ተጣጥና ወደ መስጅድ ብቻ
ባያት አልሰለቻት አይነቀል ዓይኔ
የፍቅር ዓለም ሱሴ የነፍስ ኹረልዓይኔ።

አልሐምዱሊላሂ ደርሶናል በረካ
በጀሚላ ፍቅር ልባችን ተነካ።

እይዋት ስትመጣ . . .

ሽውው አለ ነፋሱ ሞገዱም ረገበ፣
ቀሚሷም ለአመል ያው ተርገበገበ፣
(ሸርተት አለ ሻሿ መልሰችው በእጇ
አምባሯን አየሁት ሲገለጥ ግዳጇ)
አትሞቅም አትበርድም ፀሐይዋም ልከኛ፣
ዛፎች ቅጠሎቹ ሆነዋት ምርኮኛ።

አበባውም ፈካ፣ ችግኙም ፀደቀ፣
ያገር ሽማግሌው በስሟ አስታረቀ፣
እናቶች ለክብሯ አወጡላት ዜማ፣
የጓዳ እድርተኛው ለቅሶውን ተቀማ።

ጀሚላ መኣረይ፣ ጀሚላ በሬዱ
ጀሚል ሸኮሪና፣ ጀሚል የውዱዱ
ጀሙ ጀሚላዬ፣ የሰው መጨረሻ
በፍቅር የሰራሽ፣ የውብ መዳረሻ።

አልሐምዱሊላሂ ደርሶናል በረካ
በጀሚላ ፍቅር ልባችን ተነካ።

እዪዋት ብቅ ስትል

’ሚያላዝነው ውሻ ብሶቱን አቆመ
ጭራውን ቆላና ፊቷ ተጋደመ።
ድመት ተንጠራራች ስስ እግሯ ረዘመ
‘አጃኢበ ረቢ’ ፍጥረት ተደመመ።

እርግቦች በዜማ እርግብኛ አወሩ
ጎጆአቸውን ረስተው በሽቶ ሰከሩ
ደነሱ ዘመሩ፣
ጨፈሩ ፎከሩ፣
ክንፋቸው ተማታ፣ ወደ ላይ በረሩ
”ምን አይነት ውበት ነው?!”
”ምን አይነት ሽታ ነው?!” እያሉ እያወሩ።

ጀሚላ መኣረይ፣ ጀሚላ በሬዱ
ጀሚል ሸኮሪና፣ ጀሚል የውዱዱ
ጀሙ ጀሚላዬ፣ የሰው መጨረሻ
በፍቅር የሰራሽ፣ የውብ መዳረሻ።

አልሐምዱሊላሂ ደርሶናል በረካ
በጀሚላ ፍቅር ስስ ልባችን ተነካ።

ምነው ባደረገኘ ቁርአን ማስቀመጫ
በስስ እጇ ዳብሳኝ ባገኝ መተጫጫ
ኧረ ምነው በሆንኩ ምንጣፍ ወይ ስጋጃ
ግንባሯ እንዲነካኝ ስታስገባ ምልጃ።

እንደመታጠቢያሽ እንደ ውዱእ ውኃ
ልቤ ፈሰሰልሽ በፍቅርሽ በረሃ
እስቲ በይ ቁጠሪኝ ልክ እንደ ሙስበሃ
በሚፈትለኝ ጣትሽ እንዳገኝ ፍሠሐ።

ጀሙ ጀሚላዬ፣ የሰው መጨረሻ
በፍቅር የሰራሽ፣ የውብ መዳረሻ።
ስለፍቅር ብለሽ፣ በአላህ በነቢ
የኒካውን ቀልቤን፣ ከቀልብሽ አስገቢ፤
አቤት ያንቺስ ውበት …
አቤት ያንቺስ ፍቅር …
. . . አ
. . . . . . ጃ
. . . . . . . . . ኢ
. . . . . . . . . . . . በ
. . . . . . . . . . . . . . . ረቢ።

/አብዲ ሰዒድ/
ተፃፈ 2005 E.C
ስቶክሆልም፣ ስውዲን

 Image

 
Leave a comment

Posted by on September 21, 2013 in ግጥም

 

እዚህ እና እዚያ

እዚህ ᎐ ᎐ ᎐

ነጋሪት፣ ከበሮ ፡ ሲጎሰም ሲመታ
ጋሻ ጦር ተሰብቆ ፡ ሲነፋ በእምቢልታ
መለከት፣ ጸናጽል፣ አታሞ ሻኩራ
በሕብረ ዝማሬ ፡ በመድፍ እያጓራ …
ሽለላ እየደራ
ሻማም እየበራ
ፉከራ ቀረርቶ ፡ ያፈኞች ቱማታ
እዩልኝ ስሙልኝ ፡ ያድር ባይ ድንፋታ
ያደነቁረናል ፡ ያለ ቅንጣት ፋታ !

ስሟቸው !…
“የምልጃ ታቦቴ
አድባር ጉልላቴ
ምልክቴ ጌጤ
ማተቤ ነህ ፈርጤ…”
ሲሉ ሲባባሉ
በስም ሲማማሉ
ሲ – ሸ – ነ – ጋ – ገ – ሉ !


. . . ያ
. . . . . . ስ
. . . . . . . . . ጠ
. . . . . . . . . . . . ሉ !!!

እዚያ ᎐ ᎐ ᎐

እዬዬና መርዶ፣ የእድር ጡሩንባ
ያስለቃሾች ዋሽንት፣ ያላቃሽ አዞ እምባ
ለዛ የለሽ ዜማ፣ ጣዕም የለሽ ንፍሮ
ቅጥ የለሽ ንፍረቃ፣ ገጽ አልባ እንጉርጉሮ …

ዝርጠጣ፣ ፍርጠጣ
የስሜት ሽምጠጣ
ልዝቡን ከግልቡ ብረዛ ቅየጣ . . .

ደራሽና ገስጋሽ ፡ ላይሆኑ ዘላቂ
በጅምላ ሲነዱ ፡ ሕዝቤን አሳቃቂ
ደግሞም አስጨናቂ
“ስስ ብርሃን ፈንጣቂ”
ግርዶሽ አሟሟቂ
ውዥንብር ናፋቂ . . .

ስሟቸው !…
“ተፋጀ ተጣላ
እርስ በርስ ተባላ
ሞተ ተሰደደ
ተቃጠለ አበደ …

አትነሳም ወይ አትለውም ጎኑን
ደምህን ታቅፈህ ከምትድህ ዘመኑን”
እያሉ እያስባሉ እሳት እየጫሩ
በስም ላይ ስም ጭነው እየተሞሸሩ…

“አዋቂው … ልሒቁ
ረቂቁ … ምጡቁ
ታጋዩ … አርበኛው
የፍትህ እረኛው
አንተ ብቻ ዳኛው “

“ከኛስ ወዲያ ላሳር – ለሕዝባችን ግርማ
እጃችን ያልነካው – ሁሉም ነው ጨለማ።”
ሲሉ ሲፈርጁ በመንጋ ሲያስቡ
ጽድቅና ኩነኔን ባንድ ገጽ ሲከትቡ
ሲያረቁ ሲያፀድቁ
በቃል ሲያስመርቁ
ሲ – ያ – ጨ – መ – ላ – ል – ቁ !


. . . ያ
. . . . . . በ
. . . . . . . . . ሽ
. . . . . . . . . . . . ቁ !!!

እዚያና እዚህ ሆኖ የህልማችን ጫፉ
ስንፋተግ አለን ቀኖች ሲቀጠፉ
እስኪ እንጠጋጋ ወፎቹ እንዳይረግፉ።

/ አብዲ ሰዒድ – 2005 E.C /

Image

 
Leave a comment

Posted by on August 26, 2013 in ግጥም

 

ፋጡማ ሮባ

Image

ይህ ፎቶ ታሪካዊ ነው። የኢትዮጵያ የሴቶች የማራቶን ጀብዱ በኦሎምፒክ መንደር ሲበረበር በቅድሚያ የሚገኘው ይህ ፎቶ ስለመሆኑ ምንም ጥርጥር የለኝም። ይህች ብርቅዬ ሴት በ23 ዓመቷ ኢትዮጵያ ከዚያ በፊት በሴቶች ማራቶን በኦሎምፒክ ውድድር አግኝታ የማታውቀውን ክብር አላብሳታለች። 

እ. ኤ. አ በ1996 በአታላንታ ተካሂዶ በነበረው ኦሎምፒያድ ኢትዮጵያችን 2 የወርቅ ሜዳሊያ ነበር ያገኘችው። አንዱን ይህች የኔ ጀግና ፋጡማ ሮባ በማራቶን ስታስመዘግብ ሌላኛው ደግሞ በ10ሺህ ሜትር በኃይሌ ገብረ ሥላሴ ነበር የተመዘገበው። በዚያ ውድድር የጌጤ ዋሚን ነሃስ ጨምረን ባጠቃላይ ሦስት ሜዳሊያ ይዘን ተመልሰናል።

በወንዶች ማራቶን አበበ ቢቂላን በሮም እንደምንዘክረው፣ በሴቶች 10ሺህ ደራርቱን በባርሴሎና እንደምንዘክራት ሁሉ በሴቶች ማራቶን የምናነሳትና ፋጡማን ነው። አይና አፋሯ ፋጡማ ህያው ታሪክ ሰርታለች። እንስፍስፉ ደምሴ ዳምጤ ሲቃ እየተናነቀው የመጀመሪያዋ እያለ ያወራላት ፋጡማን ነው። ዋዋዋ ደምሴ አወራሩ መጣብኝ ;( 

አሁን በቅርቡ ሎንዶን ላይ ያስቦረቀችን ቲኪ ገላና ከድሏ በኋላ በሰጠችው ቃለ ምልልስ ይህችን ብርቅዬ ሴት አልዘነጋቻትም – 
“. . . ፋጡማ ሮባ የኔ ጀግና ናት፤ የርሷን ታሪክ በመጋራቴ እጅግ በጣም ደስተኛ ነኝ፤ ይህን የወርቅ ሜዳልያዬን ለሁሉም ኢትዮጵያውያን አበርክቻለሁ፡፡ . . . ” ቲኪ ገላና።

እነሆኝ እኔም ነገ (Aug, 2013) በሚጀመረው የሞስኮ 14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በውድድሩ መጀመሪያ ቀን ቲኪን ጨምሮ በማራቶን ለሚወዳደሩት ሴቶቻችን መልካም ውጤት ስመኝ ፋጡማን እያስታወስኩ ነው። 

ሴቶቻችን ሆይ ብርታት፣ ጥንካሬ፣ መረጋጋትና ድል ከናንተ ጋር ይሁን!… ይቅናችሁ!

> ቲኪ ገላና ይቅናሽ !
> መሰለች መልካሙ ይቅናሽ !
> ፈይሴ ታደሰ ይቅናሽ !
> አበሩ ከበደ ይቅናሽ !
> መሠረት ኃይሉ ይቅናሽ ! 
> መሪማ መሐመድ ይቅናሽ ! 
(መሪማ ተጠባባቂ ናት)

ሁሌም ክብር ለጀግኖቻችን! 
ሰላም ኢትዮጵያዬ ❤

___________
አብዲ ሰዒድ 
ነሐሴ 2005 E.C

 
Leave a comment

Posted by on August 9, 2013 in ስብጥርጥር

 

የሩጫችን ፈርጥ – ዋሚ ቢራቱ

14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ሊጀመር በአንድ እጅ ጣቶች የሚቆጠሩ ቀናት ብቻ ቀርተውታል… እኛም በአትሌቶቻችን ድል ልንሸልልና ልንፎክር አሰፍስፈናል… ይቅናቸው አቦ!… ይህ እንዲህ ከጫፍ እስከ ጫፍ በአንድነት የሚያስፈነድቀን የአትሌቶቻችን ድል በዓለም መለያችን ከሆነ ዘመን ውሎ አድሯል- እድሜ ለሯጮቻችን ብርታት!…

እስቲ አጋጣሚውን አስታከን ህያው ታሪክ እንቆንጥር!… ክቡር ስም እንዘክር!…

ከ50 ዓመት በፊት አበበ ቢቂላ የሮምን ማራቶን በባዶ እግሩ ፉት ሲላትና ሕዝቡን አጃኢብ ሲያሰኝ… 42 ኪሎ ሜትር ይቅርና 42 ሜትር የሮጠ በማይመስል መልኩ ሩጫ እንደሚጀምር አይነት ሰውነቱን ሲያፍታታ… ዘና ብሎ ዱብ ዱብ ሲል… ጎንበስ ቀናውን ሲያጧጡፈው ያዩት ሲደመሙ… “ምን ያለው ሰው ነው?… አይደክምምን?” ሲባባሉ… ተሸክመውት ሲጨፍሩ… በአድናቆት ሲጠይቁት… የአበበ መልስ ይበልጥ አስደንግጧቸው ነበር…

“እኔ የዓለም አንደኛ፣ የኢትዮጵያ ግን ሁለተኛ ሯጭ ነኝ”
“እንዴት?… ኢትዮጵያ ካንተም የተሻለ ሯጭ አላትን?
“አዎን… እሱ ስለታመመ ነው እኔ የመጣሁት!”

ጋዜጠኞችም ተገረሙ… ተገርመውም ወሬውን አራገቡት… ኢትዮጵያ በሁለተኛ ሯጯ ድል አደረገች ሲሉ አጧጧፉት… ያ አንደኛ የተባለውን አትሌት ለማየትም ጉጉታቸውን ገለፁ… ይህ አበበ ቢቂላ በኩራትና በአድናቆት አክብሮቱን የገለጸለት ታላቅ አትሌት ሻምበል ባሻ ዋሚ ቢራቱ ነው… ይህ ሰው ወደድንም ጠላንም… አመንም አላመንም…. በኢትዮጵያ ሩጫ እና ፉክክር በወጉ እንዲታወቁ ካደረጉ በጣም ጥቂት ፊታውራሪዎች ዋነኛው ነው!

አንጋፋው የብስክሌት ተወዳዳሪ ገረመው ደንቦባም ይህን ያረጋግጣል “በኢትዮጵያ ጦር ኃይሎች ውድድር ላይ ማንም ሰው ተከትሎት አይገባም ነበር… ቁመናው፣ ጥንካሬው፣ ብርታቱ፣ ሁሉ ነገሩ ለሩጫ የተፈጠረ ነው… የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያውቀውንና እንዲህ በአድናቆት የሚመለከተውን ሩጫ በሚገባ ያስተዋወቀ ዋሚ ነው… በየቀኑ ከሱሉልታ አዲስ አበባ ጠዋትና ማታ ይሮጥ ነበር…. “

በ1909 ዓ.ም ሱሉልታ የተወለደው ዋሚ ሩጫን ለውድድር ማሰብ የጀመረበት ሁኔታ የሚገርም ነበር… እናቱ በጋዜጣ የተጠቀለለ ቡና ከገበያ ገዝታ ትመጣለች… አዲስ አበባ ውላ ከግብይት የተመለሰችው እናቱ ቡናዋን ቆልታ ጋዜጣውን ትጥለዋለች… አንስቶ ሲያየው አንድ አጭር ሰው ሲሮጥ የተነሳውን ፎቶ ያያል… “እኔ እዚህ ጋራ ሸንተረሩን ስወጣ ስወርድ የምውል ሰውዬ ብወዳደር አሸንፋለሁ”… ሲል ተነሸጠ… ተነሽጦም አልቀረ… ሩጫውን ተያያዘው…

ከዓመታት በኋላ በ1945 ዓም አዲስ አበባ መጣ… በዘበኝነት ሥራ ተሰማራ… ጦር ሰራዊትን ከዛም ክቡር ዘበኛን ተቀላቀለ… ከዚያ በኋላማ የ5 ሺህ… የ10ሺህ እያለ የበርካታ ሩጫዎች ባለድል ሆነ… የሜዳሊያ እና የማእረግ ሽልማቶችንም ከንጉሡ እጅ ተቀበለ… በዘመኑ የሚፎካከረው እንዳልነበር ብዙዎች ይስማማሉ… የዋሚን ታዋቂ መሆን ተከትሎ ብዙ ጥሩ ጥሩ ሯጮች እንደመጡም እሙን ነው…
በዘመኑ ድንቅ የነበሩት እነ ማሞ ወልዴ… እነ ባሻዬ ፈለቀ… እነ አበበ ዋቅጅራ… እነ ገብሬ… እያልን ብናወራ ሁሉም የሚወራ ታሪክ ይኖራቸዋል…

ለኢትዮጵያ ሁለተኛ ተሳትፎዋ ለነበረው የሮም ኦሎምፒክ ከታጩት ፊታውራሪ አትሌቶች መካከል አንዱና ተስፋ የተጣለበት ዋሚ ቢራቱ ነበር… አበበ ቢቂላ ምንም እንኳ ጎበዝ ሯጭ ቢሆንም በእድሜ ልጅ ስለነበር (ከነ ዋሚ አንፃር) ብሎም ሌሎቹ ከሱ የተሻለ ሰዓት ስለነበራቸው በሮም ኦሎምፒክ ቡድን ውስጥ አልተካተተም ነበር… የወቀቱ ስውዲናዊ አሰልጣኝ አበበን እምነት የጣሉበት ለቀጣዩ ኦሎምፒክ ነበር…

መጨረሻ ላይ ግን ታሪክ ተለወጠ… ደብረዘይት ስልጠና ቆይተው የጉዞ ዝግጅት ሲጠናቀቅ ዋሚ ታመመ መሄድ እንደማይችልም ተረጋገጠ… አሰልጣኙም “በሉ አበበን አምጡልኝ!” አሉ… አበበም ዋሚን ተክቶ ሄደ… ታሪክ ጠራችው… ዋሚን ግን ታሪክ ረሳችው…

አበበ ጀግና ነው ሁላችንም እንወደዋለን… እናከብረዋለን… እናደንቀዋለን… ነገር ግን ራሱ አበበ የሚያደንቀውን ዋሚን ብንዘነጋ ልክ አይሆንም… በነገራችን ላይ የዘንድሮን አላውቅም እንጂ እስከ ባለፈው ዓመት ድረስ እኝህ ታላቅ የሩጫ አባት በሕይወት እንደነበሩ አውቃለሁ… በ96 ዓመት እድሜያቸው እንኳ ይሮጡ ነበር…

ተረስተው ከከረሙበት ጥቂት አስታዋሽ አግኝተው በጣም መጠነኛ የሆነች ድጎማ ተደርጋላቸው እንደነበርም አስታውሳለሁ…
ዋሚ
. . . ዋሚ
. . . . . . ዋሚ!

ሁሌም ክብር ለታላላቆቻችን!

 

Image

 
Leave a comment

Posted by on August 6, 2013 in ስብጥርጥር

 

የራስ ጨዋታ !

ዛፍ ተጥሏል አሉኝ ማዶ ከዚያ መንደር 
ጉዞ ጀምሬያለሁ ማገዶ ልበደር። 
መንደርተኛው ሁሉ መጥረቢያውን ታጥቆ 
ግንድ ይሸነሽናል ሥሩን ሰነጣጥቆ። 

ፍልጡስ ይጠቅመናል ግዴለም ፍለጡ
ግን አደራችሁን ችግኝ አትርገጡ። 
ቡቃያውም ይዟል አምሮበታል ሰብሉ
ምነው ባያረግፉት ወፎች እየበሉ። 
*
ወፍዬ ወፊቱ 
ወፍዬ ወፊቱ
የታደልሽ ፍጥረት ባለጸጋይቱ።

አታርሺ አትዘሪ
ፍቅር ነሽ ስትዞሪ
ማንስ ይከስሻል አገዳ ብትሰብሪ።
*
እኔስ አልዘረጋም፣ ወንጭፌን ጨክኜ
የደም ጎጆ አልሰራም፣ ጠጠር አባክኜ።
ይድላት ትፈንጭበት፣ ያውላት እርሻዬ
የተረፈው ይበቃል፣ አይጠፋም ድርሻዬ
ወፍዬን አትንካት፣ በል ተዋት ባሻዬ።

አንዳንዴ ደግ ነው፣ አንዳንዴም ይከፋል 
የቀበሌው ባሻ፣ ያለማል ያጠፋል። 
ዝንጉርጉር ነው ሆዱ፣ አይለይም መልኩ
ይጠባል ይሰፋል፣ አይታወቅ ልኩ 
ለወፍ ይታጠቃል፣ ጀግና ነው ምትኩ። 
*
ወፍዬ ወፊቷ 
ወፍዬ ወፊቷ
አልጠረጠርሽም ወይ ልበ መልካሚቷ።

ባታርሺ ባትዘሪ 
ፍቅር ብትዘምሪ 
አይተዉሽም እኮ ተይ አትዳፈሪ።

/አብዲ ሰዒድ/
Image

 
Leave a comment

Posted by on August 2, 2013 in ግጥም

 

/ ማስታወቂያ ! /

ታላቅ ብለን ያልነው የሰቀልነው ከላይ
ይፈርጥ ጀምሯል እንደበሰለ እንቧይ
ይወርዳል፣ ይዘቅጣል ይሰራል አምቡላ
ማር ጠጅ እንዳልነበር ይሆናል አተላ።

እንደጥሬ እንቁላል ከእጅ እንደወደቀ
አያነሱት ነገር ተጨመላለቀ 
ቦካ ተለወሰ … አካሉ ረከሰ
ገማ በሰበሰ … ሃሳቡ ኮሰሰ።

አድንቀን … አድንቀን 
መርቀን … አፅድቀን 
ሳይቸግር አርቅቀን 
ድንገት አሳቀቀን! 
ኧረ አሸማቀቀን!

ህልማችን መከነ፣ ተስፋችን ተነነ 
ትክን አለ አረረ፣ ውስጣችን በገነ
“ሀ”ብለን ተነሳን፣ ያለፈው ባከነ 
ወየው ታናሽነት !
ወየው ርካሽነት !
‘ወየው… ወየው… ወየው 
እኔስ ስንቱን አየው’ 
ወየው ብለን ቀረን፣ ፀጉራችን በነነ!


… ቃ
….. ጠ
……… ል
……….. ን !

ከንግዲህስ ወዲያ አቋም አውጥተናል!
ላልተወሰነ ቀን፣ 
… ላልተወሰነ ማታ፣
…… ላልተወሰነ ዘመን 

ማድነቅ አቁመናል!
…… ማክበር አቁመናል!
……… አጉል ማሞጋገስ መስቀል አብቅተናል!

መ፟ሸ፟ንገል፣ መ፟ደለል
መ፟ገ፟ፈተር፣ መ፟በደል 
መታሸት፣ መ፟ቀ፟ሸር
መ፟ፈ፟ተግ፣ መበጠር 
መሰጣት፣ መ፟ከካት 
መታመስ፣ መቆላት
መ፟ሰልቀጥ፣ መበላት 
ከንግዲህ በቅቶናል!
ይኸው በአቋምችን ላንዋዥቅ ጸንተናል!

ላልተወሰነ ቀን፣ 
… ላልተወሰነ ማታ፣
…… ላልተወሰነ ዘመን 

ማድነቅ አቁመናል!
…… ማክበር አቁመናል!
……… አጉል ማሞጋገስ ማሽቋለጥ ትተናል!
ይልቅ ለጎጇችን ለራስ በርትተናል!!!

//©አብዲ ሰዒድ //

Image

 
Leave a comment

Posted by on August 2, 2013 in ግጥም

 

“ተው ስማኝ ሃገሬ!”

እኔ እዚህ እየጮህኩኝ፣ እሱ እዚያ እየተኛ
በምን በኩል ይሆን የኛስ መገናኛ ?!
መጠየቄን አልተው፣ ዛሬም እጮሃለሁ
መልካም ቀን ይመጣል፣ አይቀርም አምናለሁ።

‘ባካችሁ ቀስቅሱት ያንን ባለ ተራ
የተሸከመው ቃል አለበት አደራ።
ምነው ለገመሳ ምነው ደነቆረ ?!
በገደል ማሚቱው ድምፄ ውሎ አደረ። 

ተሰማ አስተጋባ ይኸው ዳር እስከዳር 
አውቆ ተኝቶበት ሲያመቻቸው ለአዳር 
ዛሬም አልረፈደም ቀን አለን ወዳጄ
በል ስማኝ ጩኸቴን ብያለሁ ማልጄ።

አማን ሰላም ይሁን፣ ቸር ይዋል መንደሩ 
በፍቅር ይሻላል፣ ተሳስቦ ማደሩ።
ሃገርህ ሃገሬ፣ ርስትህም ናት ርስቴ
አብረን እንገንባት ተው ስማኝ በሞቴ።

ተው ስማኝ ሃገሬ 
ተው ስማኝ ሃገሬ 
ምነው መጨነቄ፣ ምነው መቸገሬ።

የተቀመጥክበት ዙፋንህ ቢደረጅ 
አያልፍ እንዳይመስልህ ተው አታስጠናኝ ደጅ
ይልቅ ፅደቅበት መልካም አድርግና
ለዘመንህ ክብር ለስምህ ልዕቅና።

የከርቸሌውን በር ከፈት አርገው ባሻ
ህብረት ነው ‘ሚበጀን እስከመጨረሻ !
ፍቅር ነው ጥረቴ፣ ሳላም ነው ብርታቴ 
እታገልሃለሁ፣ አይደክምም ጉልበቴ።

የነጃሺን አድባር፣ የቢላልን ምድር 
የሙአይመንን ጡት፣ የረሱልን ፍቅር
በሳላም ልጠብቅ ላልደፍር ላልነካ
እኔስ ቃል አለብኝ በጡት የተነካ።

ዝምታህ ይከብዳል፣ እኔስ ሰግቻለሁ
አስረግጠህ ስማኝ፣ ተው ጓዴ ብያለሁ
ቃሌን ተቀበላት፣ ያው አስረክቤያለሁ።

ተው ስማኝ አገሬ 
ተው ስማኝ አገሬ 
በዛ መጨነቄ፣ በዛ መቸገሬ።
_________
(አብዲ ሰዒድ)

Image

 

 
Leave a comment

Posted by on August 2, 2013 in ግጥም

 

. . . በሬው! . . .

Image
እዩት ያንን በሬ በቀንዱ ተማምኖ
ያሸብረን ይዟል ላሞች ላይ ጀግኖ
ላሞች እንደሆኑ መጠቃት ልምዳቸው
ወተት እንዲያጠጡ ኮርማ ነው ግዳቸው።

በሬ እየሸለለ፣ በሬ እየፎከረ 
በሬው እያጓራ፣ ስንቱ ደጅ አደረ፤
ይወጋል ይረግጣል፣ ሲሻው ያንሳፍፋል
በሬ ሆይ አይምሬው፣ ትውልድ ያጣድፋል።

ተው በሬ … ተው ኮርማ 
እባክህ ተመከር፣ ያገር ምክር ስማ 
ተጥለህ እንዳናይህ፣ ከቄራው አውድማ።

የሚሮጥ፣ የሚሸሽ፣ የሚበረግገው፣ 
ቀንድህን በመፍራት፣ የሚያደገድገው፣
ገና ብቅ ስትል መንገድ የሚጠርገው ᎐᎐᎐ 

ይሄ ሁሉ ፈሪ፣ ይህ ሁሉ ቦቅቧቃ
ከዘመን ፍራቻው፣ ሲባንን ሲነቃ
ሆ! ያለብህ እንደሁ ታጥቆ በቆንጨራ
ያዝ ያለህ እንደሆን ከቦ በገጀራ 
ማምለጫም አይኖርህ ለአንገትህ ካራ። 

“በሬ ሆይይ 
በሬ ሆይይ 
ሳሩን አየህና ገደሉን ሳታይ 
መግባትህ ነው ወይይይይ”

ብለን እንዳናለቅስ ቆዳህን ሲገፉ
ዛሬን አታስጀግር ተው ሰዎች ይለፉ
በሰላም፣ በጤና፣ በፍቅር ይረፉ 
ላንተም አይበጅህም፣ ያጠፋሃል ግፉ።

________
አብዲ ሰዒድ 
2005 E.C

 
Leave a comment

Posted by on August 2, 2013 in ግጥም

 

የዓለም ፀሐይ ዓለም . . .

ዓለም ፀሐይ ወዳጆ . . .

alem1
አርቲስት ዓለም ፀሐይ ወዳጆን የማያውቅ የጥበብ ቤተሰብ ይኖራል ብዬ አልገምትም… ከኖረም ከቲያትሩም፣ ከትወናውም፣ ከዘፈኑም፣ ከግጥሙም ዓለም ራሱን ያራቀ… በስሚ ስሚ ወሬ እንኳን በኪነ ጥበብ ዘርፍ ነፍሱን ያላፀደቀ መሆን አለበት… ዓለም ፀሐይ ዘርፈ ብዙ የሆነች የጥበብ ፈርጥ ናት!… የተውኔት ጸሐፊ፣ የቲያትር አዘጋጅ፣ ተዋናይ፣ ገጣሚ ከመሆኗም በተጨማሪ የኢትዮጵያ ሕጻናት ቲያትር መስራች እንዱሁም በውጭው ዓለም በተለይም በአሜሪካ ኢትዮጵያዊ የጥበብ ስራዎች ከኢትዮጵያዊያን ልቦች እንዳይጠፉ በብርቱ የምትንቀሳቀስ የጥበብ አድባር ናት!… ጣይቱ የጥበብ ማእከልን ይጠቅሷል…

የሷን የጥበብ ስራዎች በሙሉ ልዘረዝር አልተነሳሁም!… ሁሉም በየመስኩ እንደመልካቸው ለየብቻ ሊዘርዘሩና ሙያዊ ትንተና ሊሰጥባቸው የሚችሉ ናቸው… ስለ ትያትር ስራዎቿ ለብቻ… በመጽሃፍና በሲዲ ስላሳተመቻቸው ግጥሞቿ ለብቻ… ለበርካታ ዘፋኞች ስለሰጠቻቸው የዘፈን ግጥሞች ለብቻ.. እያልን ከጥበብ ባሕሯ ልንጨልፍ ይቻለናል!… እናም ይህ ጽሁፍ ትኩረት የሚያደርገው የዘፈን ግጥሞቿ ላይ ብቻ መሆኑን መግለጹ ያስፈልገኛል…

አብዛኞቻችን ብዙውን ጊዜ ትኩረት የምንሰጠው ለዘፋኞች እንጂ ለግጥምና ዜማ ደራሲዎችም ሆነ ለአቀናባሪዎች አይደለም… በእርግጥ ዘፈን የድምጽ ስራ በመሆኑ ዘፋኙን ማወደስና ማክበር የተገባ ነው… አንድ ሙዚቃ ሙሉእ ሆኖ ቀልብን እንዲገዛ የሁሉም አስተዋጽኦ የየራሱ ዋጋ እንዳለው መዘንጋቱ ግን የጥበብን ውህደት እንደመዘንጋት ይቆጠራል… ዜማ ያለ ግጥም… ግጥምም ያለ ዜማ… ሁለቱም ያለ ጥሩ ቅንብር ለመንፈስ እርካታን የሚለግስ ዘፈን ሊሰጡን አይቻላቸውም… ሶስትም አንድም እንደማለት ነው… የማይነጣጠሉ!… ዓለም ፀሐይ የምትታወቀው ውስጥ ዘልቀው በሚገቡ ግጥሞቿ ነው… እናም ግጥም ላይ ብቻ ትኩረት አደርጋለሁ…

ከወራት በፊት ስለ ዘፈን ግጥሞቿ አወራኋት… ባጋጣሚ ውይይታችንን የቀረጽኩበት ድምጽ መቅጃ ከጄ ወጣ… በሲዲ አሊያም በሌላ መሰል ነገር አልገለበጥኩትም ነበርና ተበሳጨሁ… በድጋሚ ላውራሽ ማለቱ ደግሞ እሷን ማድከም እንደሆነ ተሰማኝ… እፍረትም ሸንቆጥ አደረገኝ… እናም መልሼ እስካገኘው መጠባበቅ ግድ ሆነብኝና እስካሁን ቆየሁ… መቼም ቅር እንደማትሰኝብኝ እምነቴ ነው… ከራሷ የሰማሁትን ለማጠናቀር ስለፈለግኩ እንጂ በተባራሪ የሰማኋቸውን እንዲሁም ካሴቶች ላይ ያየኋቸውን ለቃቅሞ መጻፍ እንደሚቻለኝ ዘንግቼው አይደለም… ጊዜዋን ሰውታ ስለ ስራዎቿ ስላዋየችኝ እጅግ እያመሰገንኩ ከራሷ አንደበት የሰማሁትን በራሴ መንገድ ለመነካካት እሞክራለሁ…. እጅግ ከባድ ቢሆንም…

ከ400 በላይ የዘፈን ግጥሞች . . .

ስለ ሙሉ የዘፈን ግጥሞቿ በዚህ ጽሁፍ ለመዘርዘር መሞከር የማይታሰብ ነው… ምን ያህል ግጥሞች ለምን ያህል ዘፋኞች እንደሰጠች በእርግጠኝነት ለመናገር ይቸግራታል… “የማታ እንጀራ” የተሰኘው የግጥም መጽሐፏ ሲመረቅ በድምጽ ባለሙያዎችና በጓደኞቿ ትብብር የተዘጋጀ ‘ሰርፕራይዝ’ አይነት ስጦታ ተበረከተላት… ስጦታው ሲታይ እስካሁን የሰራቻቸውን የዘፈን ስራዎች ያሰባሰቡ ሲዲዎች ነበሩ… በደስታና በአግራሞት መሃል ሆና አመስግና ተቀበለቻቸው… በኋላም ከ400 በላይ የዘፈን ግጥሞች ለ47 ዘፋኞች እንደሰጠች ተረዳች… ተገረመችም… ተደሰተችም… አመሰገነችም…

ምንም እንኳ ወዳጆቿ የቻሉትን ያህል ለማሰባሰብ ቢሞክሩም ሙሉ ነው ለማለት ግን አይቻልም… ምክኒያቱም በካሴት የመቀረጽ እድል ያላገኙ በድሮው ጊዜ በቲያትር ቤቱ የባሕል ክፍል ይዘፈኑ የነበሩ ዘፈኖችን ማካተት አልተቻለምና ነው… እንደ ምሳሌም የነ ጠለላ ከበደን፣ የነ ፀሐይ እንዳለን፣ የነ መልካሙ ተበጀን በካሴት ያልታተሙ ዘፈኖች መጠቃቀስ ይቻላል….

የሷን ግጥም ያልዘፈነ ዝነኛ ድምጻዊ ማግኘት ይከብዳል ከክቡር ዶክተር ጥላሁን ገሠሠ ጀምሮ እነ ማሕሙድ አህመድ፣ ሙሉቀን መለሰ፣ ቴዎድሮስ ታደሰ፣ ፀሐዬ ዮሐንስ፣ ሻምበል በላይነህ፣ ዳዊት መለሰ፣ ኅይልዬ ታደሰ፣ ግርማ ተፈራ፣ ብዙአየሁ ደምሴ፣ ሰጠኝ አጣናው እንዲሁም ከሴቶች አስናቀች ወርቁ፣ አስቴር አወቀ፣ ኩኩ ሰብስቤ፣ በዛወርቅ አስፋው፣ አቦነሽ አድነው፣ ሂሩት በቀለ፣ ፋንትሽ በቀለ፣ አሰፉ ደባልቄ እያልን ከብዙ በጥቂቱ መጠቃቀስ ይቻለናል… የቻልኩትን ያህል በቀጣይ ለመነካካት እንደምሞክር ቃል እየገባሁ ላሁኑ ሙሉቀን መለሰ ላይ ብቻ ትኩረት አደርጋለሁ…

ሙሉቀን መለሰና የዓለም ፀሐይ ግጥሞች . . .

muluken
ሙሉቀን በተነሳ ቁጥር የዘፈኖቹን ግጥሞች ውበትና ጥልቀት… የተሸከሙትን መልእክትና ቁምነገር ያለማንሳት አይቻልም!… ዘመናችንን ሙሉ ካጣጣምናቸው ከአብዛኛዎቹ ድንቅ ግጥሞች ጀርባ ደግሞ ዓለም ፀሐይ አለች… ሙሉቀን በአብዛኛው የእሷን ግጥሞች ሲጫወት ነው የኖረው… “ሌቦ ነይ” ከሚለው የመጀመሪያ የካሴት ስራው ጀምሮ ዘፈን እስካቆመበት ጊዜ ድረስ የዓለም ፀሐይን ግጥሞች አዚሟቸዋል… ባጋጣሚ ሙሉቀንን ብታገኘውና “እንትን የሚለው ዘፈንህ ግጥሙን ማን ነው የጻፈው?” ብትለው ድንገት የሰጠውን ገጣሚ ቢዘነጋው አልያም በጊዜያዊነት ግር ቢለው በርግጠኝነት “ያው ዓለም ፀሐይ ትሆናለች” ብሎ ነው የሚመልስልህ….

ሙሉቀን እጅግ ውብ የሆኑ ዘመን ተሻጋሪ ስራዎቹን ለኢትዮጵያ ሙዚቃ አበርክቶ ዓለማዊውን ዘፈን የተሰናበተና መንፈሳዊውን ዓለም የተቀላቀለ ብርቅዬ አርቲስት ነው… የቋንቋው ውበት… የአዘፋፈኑ ለዛ… የሚጫወታቸው ግጥሞችና ዜማዎች… ቅንብሮቹ… ብቻ በሁሉም የተዋጣለትና የተለየ ቦታ መቀመጥ የቻለ ድምጻዊ ነው… ዓለም ፀሐይ ራሷ ምንም እንኳ ስራዎቿን የተጫወቱላትን ዘፋኞች በሙሉ እንደየመልካቸው ብትወዳቸውም… ብታከብራቸውም… ብታደንቃቸውም… ለሙሉቀን ያላት ስሜት ግን ይለያል….

ሙሉቀን ቋንቋ አዋቂ ነው… ቋንቋን የማሳመር ተክኖ አለው… ዜማ መርማሪ ነው… አንድን ዘፈን የሚሰራው ብዙ ተጨንቆና ተጠቦ… ብዙ ዜማዎችን አጥንቶና መርምሮ… ብዙ ጊዜ ወስዶ… ከነፍሲያው ጋር አዋህዶ ነው… ጥድፍ ጥድፍ ያለ ጥናት አይወድም!… የተዋከበ ቀረጻም አይዋጥለትም!… ያልመሰለውን ቅንብር አይቀበለም!… በወቅቱ የነጋዴዎችን ተጽእኖ ተጋፍጦ ለጥበቡና ለስሜቱ ያደረ በሳል አርቲስት ነው!… በዚህም የኢትዮጵያ ሙዚቃ በቅንብር ረገድ እንዲያድግ የበኩሉን አስተዋጽኦ አድርጓል… እነ ሙላቱ አስታጥቄን የመሳሰሉ ሊቅ አቀናባሪዎች ስራዎቹን ተግተው እንዲያቀናብሩለት ድርሻውን ተወጥቷል… በክፍያም ረገድ በዘመኑ ለዘፋኞች የሚከፈለው ክፍያ ከፍ እንዲል ፈር የቀደደ ነው…

ዓለም ፀሐይን የሚያበሳጫት አንድ ችግር ግን ነበረበት… ግጥሞቿ ውስጥ የባህል፣ የህዝብ፣ አሊያም ገጣሚያቸው በውል የማይታወቁ ስንኞችን እያመጣ ይጨምራል… አንዳንድ ዘፈኖቹ ላይ ግማሹ ግጥም የሷ ይሆንና ግማሹ የሌላ ይሆናል… ይህን ስራውን አትወድለትም!… “እንደዚህ አታድርግ ግጥሞቹን እንዳሻሽላቸው ከፈለግክ እራሴው ላሻሽላቸው እንጂ የሌላን አምጥተህ ስራዎቼ ውስጥ አትጨምርብኝ!” ብትለውም እሱ ከወደደና ካመነበት ያደርገዋል… ካሴቱ ከወጣ በኋላ ለተወሰነ ጊዜ ከፊቷ ይሸሻል… “እስቲ ጥይቋት… ምን አለች?… ተቆጣች?…” እያለ ይጠይቃል… በኋላም ስራው ይቀጥላል… እንዲህ አይነቶቹን ዘፈኖች በሙሉ ልብ የኔ ናቸው ለማለት አትደፍርም… ይህ ግን ባንዳንዶቹ ስራዎቿ እንጂ በሁሉም ላይ አይደለም…

በአብዛኛው ሙዚቃ አፍቃሪ እጅግ የሚወደዱት እነ “ገላዬዋ”… “ሰውነቷ”… “ወይ እዳዬ”… “አልዘገየሽም ወይ”… “ቁመትሽ ሎጋ ነው”… “መውደዴን ወደድኩት”… “ቁረጥልኝ ሆዴ” እና ሌሎች በርካታ ስራዎቹ የሷ ግጥሞች ናቸው… ጥቂት ስንኞችን ልቆነጣጥርና ለዛሬ ላብቃ…

1) ♪♪ ገላዬዋ ♪♪

♪♪ ገላዬዋ ነይ ነይ
ገላዬዋ ነይ ነይ
ሰው በገላው ውበት ይናፈቅ የለም ወይ♪♪

♪♪ ያይን ሽፋሽቷን ቅንድቧን አድንቁ
ጣቷን አስተውሉ ስትተዋወቁ
ዓይኗን ተመልከቱት እኔው ፈቅጃለሁ
ከኔው ጋር እያለ ሲዋሽ ይዤዋለሁ ♪♪

♪♪ አንገቷን አድንቁ መቃ ነው ብላችሁ
አካባቢ ሲቃኝ ታገኙታላችሁ
ቁጣ ግልምጫውን እችላለሁ ያለ
ጡቷን ቢመለከት ከልካይ አንድም የለ ♪♪

♪♪ ጥርሷን አሳስቁት ዝምታን አያውቅም
ፈገግታ በሷ ዘንድ ብዙ አያስጨንቅም
ዳሌ አቀማመጡን እዩት ለናሙና
እግሯን አትንኩብኝ መምጫዋ ነውና♪♪

♪♪ ገላዬዋ ነይ ነይ
ገላዬዋ ነይ ነይ ♪♪

2) ♪♪ ቁመትሽ ሎጋ ነው ♪♪

♪♪ ቁመትሽ ሎጋ ነው ሰንደቅ ያሰቅላል
የሰላም የፍቅር ምልክት ያሳያል ♪♪

♪♪ አሸን ክታብ ድሪ አልቦ ለቋ* ቀርቶ
ሽመል ሰውንተሽ ይታያል አብርቶ
ድሪውን ጠልሰሙን ገላሽ ባያደርግም
የፍኝ እኩሌታ ውበትሽን አይነፍግም ♪♪

♪♪ ለምድና ጎፈሬ ምን ይሆነኝ ብለሽ
ጌጤ መድመቂያዬ እራስ ወርቄ አንቺ ነሽ
የኔ በትረ ሙሴ መጥፎሽን አልወድም
ጠምበለል ነሽ ሎጋ ይህንን አልክድም ♪♪

♪♪ ቁመትሽ ሎጋ ነው ሰንደቅ ያሰቅላል
የሰላም የፍቅር ምልክት ያሳያል ♪♪

3) ♪♪ መውደዴን ወደድኩት ♪♪

♪♪ አንቺን መሳይ ቆንጆ ለኔ የሰጠኝን
መውደዴን ወደድኩት ያንቺ ያረገኝን
የኔ ያረገሽን መውደዴን ወደድኩት
ሳስብ ሳሰላስል ቆየሁ ከወሰንኩት ♪♪

♪♪ ሃር ከመሰለው ከጸጉርሽ ጀምሮ
እንከን የሌለብሽ ውብ ነሽ በተፈጥሮ
ትኩስ የፈነዳው ጽጌሬዳ ከንፈር
እስኪ አፍ ያውጣና ውብትሽን ይናገር ♪♪

♪♪ የሐረር መንደሪን የመስከረም አደይ
የሞጆ ብርትኳን የነሐሴ እንጉዳይ
ከንፈርሽ እንጆሪ ቀይ ጽጌሬዳ
ወፍ ጭጭጭ ሳይል ማልዶ የፈነዳ ♪♪

♪♪ አንቺን መሳይ ቆንጆ ለኔ የሰጠኝን
መውደዴን ወደድኩት ያንቺ ያረገኝን
የኔ ያረገሽን መውደዴን ወደድኩት
ሳስብ ሳሰላስል ቆየሁ ከወሰንኩት ♪♪

. . . በመጨረሻም እስቲ እናንተም የምታውቁትን ስራዎቿን ጻፍ ጻፍ አድርጉልኝ… ከዓለም ፀሐይ ጋር ያወጋነው ብዙ ነው… በቀጣይ ደግሞ ከሌላ ብርቅዬ ድምጻዊ ጋር ይዣት እመለሳለሁ… ረጅም እድሜ ላንቺ ዓለም ፀሐይ… ሰላም ለሁላችን!!!

ክብር ለጥበበኞች!
አብዲ ሰዒድ
2005 E.C

 
Leave a comment

Posted by on May 21, 2013 in ስብጥርጥር