RSS

Category Archives: ስብጥርጥር

ተው

የተስፋዋን ጭላንጭል

ድርግም!

የፀሐይዋን መፍካት

ጭልም!

የንጋቷን ዘመን

ርዝም!

እያደረግክባት

ተው አትነግድባት!

የመሻገሪያዋን ድልድይ

ስብር!

የመናገሪያዋን ቃል ቅብር!

የማደሪያዋን ቀዬሽብር!

እያስደረግክባት

ተው አትቀልድባት!

የልጆቿን እድሜቅጭት!

ቂም በቀል ጥላቻን

ቅብት!

ግፍና ሰቀቀን

ዝርት!

እያስደረግክባት

ተው አትሸልልባት!

ተው!

.

.

.

ተው ባይጠቅምም ቃሉ

ተው ነው ሰው አመሉ!!!

 
Leave a comment

Posted by on September 10, 2021 in ስብጥርጥር

 

ዘ – መ – ቻ !

አያቴ ኮርያ ዘማች ነበር። እናቴ ቡና አፍልታ መንደርተኛው በተሰበሰበ ቁጥር ምክኒያት እየፈለገ ስለ ኮሪያ ማውራት ይወዳል።

<< እኛኮ ለዓለም ኩራት ለሃገርም ክብር ነን!… እዚህ ተጥለን ብንታይ ዝናችን የተረሳ እንዳይመስላችሁ… በሄድንበት ያገራችንን ስም ከፍ አድርገን ኒሻን በኒሻን ተምነሽንሸን… በሊጎፍኔሽን አርማ ደምቀን… ባገራችን ባንዲራ አሸብርቀን… የተመለስን ጀግኖች ነን!… አታዩትም ግርማ ሞገሴን!>>… እያለ ያቺን ለዘመናት ያየናትን ጥቁር ፎቶ ያሰየናል… አያቴ ሙሉ የጦር ልብሱን ገጭ አድርጎ የለበሰባትን ፎቶ…

እውነቱን ነው!… አያቴ ያምራል… ግርማ ሞገሱ ያስፈራል… ቆራጥ አመለካከቱ ያስደነብራል… እንዲህ አርጅቶ እንኳ አትንኩኝ ባይ ነው… እማዬ ለምን ይሄን ፎት ፊት ለፊት እንደሰቀለችው ግልፅ ነው…. አያቴ ምንም ከምታደርግለት የጥንት ፎቶውን እያየህ ስለ ኮሪያ ብትጠይቀው እንደወደድከውና እንዳከበርከው ይረዳሃል… “አረጀህ፣ ደከምክ፣ አረፍ በል፣ ተኛ ፣ተነስ…” ምናምን ልትለው ብትሞክር ግን ይጣላሃል.. “ወግድልኝ!… የኮሪያ ዘማች እኮ ነኝ”… እያለ ይሸልልብሃል… ከቶም እጅ አይሰጥም!… ቆራጥ… በራሱ ብቻ መቆም የሚሻ ደፋር ሰው ነው… ብልጧ እናቴም ይህን ባህሪውን ጠንቅቃ ስላወቀች ተጠቅማበታለች… ባይሆንማ አያቴ እንደሞተ ፎቶውን አታነሳውም ነበር… እሺ ከዚያ በኋላ ፎቶው የት ገባ?!… ያያቴ ፎቶ የት ደረሰ?!… ያን ምርጥ ታሪካዊ ፎቶ ምን ወሰደው?…

<< እንደው ማማሩስ ጥርጥር የለው… መቼም ያላዩት አገር የለ… ይሄ መቼ መሆኑ ነው ታዲያ?>> ይጠይቃሉ የጦቢዬ እናት… አያቴም ፊቱ በደስታ እየፈካ… ቡናውን በፍቅር እያጣጣመ… ኮሌታውን እያስተካከለ… አፉን በእጁ እየሞዠቀ ይመልሳል…

<<ይሄማ ከዘመቻው ቀደም ብሎ ነው… በግርማዊነታቸው ቆራጥ ንግግር “ቃኘው ሻለቃ” አርማውን ከዣንሆይ እጅ ተቀበሎ በተሸኘ ጊዜ… አይ ዣንሆይ!… ያደረጓት ንጥር ያለች ንግግር!… የዋዛ ንግግር እንዳይመስላችሁ… ዣንሆይ እንዲሁ በከንቱ ቃል አያባክኑም… ሁሏም ቃላቸው ፍሬ አላት… እስታሁን እንኳ መልክታቸው አይዛነፈኝም>>

ሬዲዮኑን አስተካክሎ እያስቀመጠ ይቀጥላል… አያቴና ሬዲዮ ተለያይተው አይቼ አላውቅም… የዜና ፍቅሩ ሁሌም እንደገረመኝ ነው… በሄደበት ሁሉ በካኪ ጨርቅ የተሸፈነችው ሬዲዮ ከእጁ አትጠፋም…

<< እናላችሁ በተጠንቀቅ ለተዘጋጀነው የቃኘው ሻለቃ አባላት በሙሉ የጦር አርማውን እያበረከቱ ዣንሆይ እንዲህ አሉ… ‘ይህንን የጦር መለዮ ዓላማ በምታደርጉበት ጦርነት ሁሉ በጀግንነት ከፍ አድርጋችሁ ትይዙታላችሁ።… ለኢትዮጵያ ነፃነት ከብዙ ሺህ ዓመት ጀምሮ የተጋደሉት ጀግና አባቶቻችሁ መንፈስ ይከተላችኋል፤ በጦር ሜዳ ክንዳችሁን ያፀናል፤ ልባችሁንም ያበረታል!’…>>

<< እውነት ነው ጀግንነት ከደማችን ነው ሐበሻ ተደፍሮም አስደፍሮም አያውቅም>> ጣልቃ ይገባሉ እትዬ ሸጌ…

<<ታዲያሳ!… መይሳው ካሳም ቢሆን ያን የንግሊዝ ጭባ ሁላ እያዳፋ መድፍ ሲያስቀጠቅጠውና ወባ እንደያዘው ቆለኛ ሲያንቀጠቅጠው ነው የኖረ… ምኒሊክም ቢሆን ያን ሶላቶ ጣልያን በዱር በገደሉ ሲያርበደብደው ነው የከረመ… ጥበበኛዋ ጣይቱም ብትሆን ለአርበኛው ጠጇን እያስጣለች ሶላቶውንና ባንዳውን ውሃ ውሃ እያሰኘች በእንፉቅቅ ያስኬደች ጀግና ናት… አባቴ ራሱ በሚኒሊክ ጊዜ አርበኛ ነበር… ስንቱን ያርበኛ ጀብዱ እንዳጫወተኝ ባወጋችሁ ዘበኑም አይበቃን>> …

አያቴ ላፍታ በዝምታ ትንፋሽ እየወሰደ ይተክዛል… በትዝታ አባቱን እያሰባቸው ይሆናል… የቡና እድምተኛም በጉጉት ይጠባበቃል… አያቴ የሚነግረን ታሪክ ተመሳሳይ ቢሆንም አይሰለችም… እሱ ሲያወራው የሆነ እንዳይሰለች የሚያደርግ ነገር አለው… ሁላችንም በጉጉት እንዲቀጥል እንጠብቃለን… አያቴም ቤቱን ገርመም ገርመም አድርጎ ጨዋታውን ይቀጥላል …

<< እኛም ታዲያ ጀግኖች አባቶቻችንንም ሆነ ዣንሆይን አላሳፈርንም!… ሃገራችንንም በሽንፈት አላስጠራንም!… በተሰለፍንበት ውጊያ ሁሉ አልተበገርንም… አንድም የቃኘው ወታደር እጁን አልሰጠም!… ከ16 ሃገራት የተሰበሰበው ተዋጊና አዋጊ ሁላ እኛን እንደ ተአምር ነበር የሚያየን… ‘ኢትዮጵያውያን ከሰው ፍጡር በላይ ናቸው’ እስከመባል ድረስ ተደርሶ ነበር… በዚያ መሳይ ከባድ ውጊያ ባጠቃላይ በክብር የተሰዋው የቃኘው ወታደር 120 አይበልጥም… ቁስለኛውም ቢሆም ከሌላው አንፃር ሲታይ እምብዛም ነው!>>

የአያቴን በወኔ የተሞላ ንግግር በገብረ ክርስቶስ ግጥም እያወራረድኩ… እኔም አብሬው ዘምቼ እመለሳለሁ…

“… ደስታና ሐዘን በቦታው ጨፈሩ
ሣቅ ለቅሶ እየሆነ እምባ ሄደ በግሩ
በያይነቱ ኒሻን ጠመንጃ ሸክሙ
ወቴ ከነደሙ
እዚህ ይዞ መጥቷል ከሩቅ ከኮሪያ
ተቃጥሎ ይጋያል የባቡሩ ጣቢያ
. . . . . . . . . ብቻ እዚህ አይደለም…”

ከዘመቻ ሲመለስ ባቡር ጣቢያ ሄጄ የተቀበልኩት ያህል ይሰማኛል… ሁሌም ትረካው እንደተዋሃደኝ ነው…

<<አንቱ እንደሁ እድለኛ ኖት… በደጉ ዘመን ሁሉን አሳልፈዋል… ጥጋቡንም ዓለሙንም እስኪበቃዎት አይተውታል… ምን ቀሮት እቴ!>> እማማ ዘኔ ናቸው…

<<ይመስገን… ይመስገን… ደግሞ አንቺስ ብትሆኚ ምን ቀረሽና ነው… ኮሪያ ባትዘምቺም መቼም ከኮሪያ ዘማች ጋር ሳትኮምሪ አልቀረሽም… እሱም ቢሆን ዝና ነው እኮ… እኛ እንደሁ ብርቅ ነበርን… አሃሃ… ጥጋቡንማ ተይኝ!… ዣንሆይ እኮ በችጋር ለተጎዱትና ይልሱት ይቀምሱት ለቸገራቸው የፓኪስታን ዜጎች አይዟችሁ እግዜር እንደሰጠን እንሰጣችኋለን ብለው ረብጣ ዶላር ለሩዝ መግዣ ይሰዱላቸው ነበር!>>

<<እንዴ አባ ኢትዮጵያ እርዳታ ትሰጥ ነበር እንዴ?!>> እጠይቃለሁ እኔ

<<ኋላስ!… ስንቱን ረሃብተኛ ከረሃቡ ታድጋው የለ እንዴ!… ስንቱን ችጋራም አርጥባው የለም እንዴ!… ምድራቸው እህል አላበቅል ሰማያቸውም ውሃ አላፈስ ብሎ በረሃብና በቸነፈር ሲቀጣቸው አይዟችሁ ብላ የለም እንዴ!… ስማ ልጄ! ይህች ለምለም ሃገር እኮ ታላቅ ናት!… ዛሬ ተራቁታ ብታያት የዋዛ እንዳትመስልህ… በወስላቶች ዝርፊያ የደኸየች ቢሆንም ሃብታም ነበረች…. ደግሞም ዳግም ማበቧ አይቀርም!>>

የአያቴን በተስፋ የተሞላ ንግግር እያዳመጥኩ… እርዳታ አድራጊዋን ኢትዮጵያ እየታዘብኩ… እማዬ ከሱንከሞ ሱቅ ለቡና ቁርስ እንዲሆናት (በአቋራጭ ምሳም ይሆናል) በብድር ያስመጣችውን ሽንብራ እየቆረጠምኩ… (ግን መቼ ልትከፍለው ነው? ከየት አምጥታ ልትከፍለው ነው? – እሱን አላህ ነው የሚያውቀው)… ለአያቴ ይልሰው ይቀምሰው ያላተረፉለትን ዣንሆይና አያቴ ለሳቸው ያለውን ክብር እያሰላሰልኩ… አንድ የመርቲ ጣሳ የጉድጓድ ውሃዬን ጭልጥ አድርጌ ጠጥቼ (ሆዴ እየተንቦጫቦጨ) ወጣሁ… እኔም ወደ ዘመቻዬ በምንጋ ተመምኩ…

እነሆኝ አደግኩ!
እነሆኝ የኔ ዘመቻ!

… የበደሌ ዘመቻ!
… … የኮካ ኮላ ዘመቻ!
… … … የቀ እና ቐ ዘመቻ!
… … … … የለ እና ሌ ዘመቻ!

ቻ! ቻ! ቻ!
ከንቱ ብቻ!

አጁዛ አለ አዳም ረታ!
እውነትም አጁዛ!

Image

 
1 Comment

Posted by on January 9, 2014 in ስብጥርጥር

 

የዞረው ጎዳና

በጠማማ መንገድ ጉዞ የጀመረ
ሲወድቅ ሲነሳ ባለበት አደረ።
መንገዱስ ከራቀ የህልሜ መድረሻ
አንቺንና መጠጥ ሃዘኔን ማስረሻ።
________

ይህ ፅሁፍ የአልኮል መጥጥ ማስታወቂያዎችን የሚነካካ ነው። ማንኛውንም ግለሰብ ወይም የትኛውምንም አይነት አምራች ድርጅት አይመለከትም። በአንዲት ነፍስ የሚብሰከሰክ ግለሰባዊ ትዝብት ነው። ሃሳቡ ቢስማማህ አንተም ውስጥ የሚብሰለሰል ነገር ስለነበረ ቢሆን እንጂ አዲስ ተዓምር ፈጥሬልህ አይደለም፤ ሃሳቡ ቢጎረብጥህ አላማዬ አንተን ማስደሰት አይደለምና ሃሳቤን አክብረህ ማስታወቂያህንም፣ ጨብሲህንም የመቀጠልና የማስቀጠል ምርጫው ያንተ ነው።

“ሸገር ላይ አብቦ ሸገር ላይ ያፈራ
የጥንት የማለዳው ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ
አብሮ እየዘመነ ከዘመኑ ጋራ
አራዳን ያሞቀ አራዳን ያደራ

ዘላለም ጥም ቆራጭ ዘላለም ፍሰሀ
ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ የነፍስ እህል ውሃ
ወዳጅነት ጠብቆ ጨዋታ እንዲደራ
ይንቆርቆር ይቀዳ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ!”

ይህ የማንቆለጳጰሻ ግጥም በጥላሁን ገሠሠ “የጥንቱ ትዝ አለኝ” ዜማ ታጅቦና በአንባቢው አስገምጋሚ ድምፅ ግርማ ሞገስ ተላብሶ በሸገር ኤፍ ኤም ሲቀርብ ለጆሮ ደስ ይላል። ደስ ማሰኘትና ለመጠጥ ማነሳሳት የማስታወቂያው አላማ በመሆኑ በዚህ በኩል ተሳክቶለታል። ፋብሪካው ለዚህ ሙገሳ የተጠየቀውን ቢከፍልም አይቆጨው፤ ለአርቲስቱም ለድርጅቱም የገቢ ምንጭ ሆኗልና ይቅናቸው።

በግጥሙ ውስጥ ከተካተቱት የማስዋቢዋ ቃላት ጋር ግን በግሌ ፀበኛ ነኝ። ‘ዘላለም ጥም ቆራጭ’… ‘ዘላለም ፍሰሃ’… ‘የነፍስ እህል ውሃ’… ‘ወዳጅነት አጥባቂ’… ምናምን የሚሏቸውን የውዳሴ ቃላት በሰማኋቸው ቁጥር ግርም ይሉኛል። ገንዘብ ስለተከፈለና እድሉ ስለተገኘ ብቻ የሚንፎለፎል ቅጥፈት አይጥመኝም። ቢራ በየትኛው ስሌት ዘላለማዊ ጥም ሊቆርጥ እንደቻለ አልገባኝም። ዝንታለም ፍሰሃ ሊለግስ ይቅርና በብዙ መከራዎች ተቀነጣጥሳ ያጠረች እድሜን የባሰ የሚያሳጥርም ይሄው ልኩ የማይታወቀው አልኮል ነው። የነፍስ እህል ውሃነቱም ጠግቦ ላላደረ አንጀት የሰማይ ያህል ሩቅ ነው፤ ጠግቦ ላደረው ግን ምን እንደሆነ አላውቅም።

“ስማ ይሄ እኮ ማስታወቂያ ነው!… ማሻሻጫ እንጂ ሃቅ አይደለም!… ጅል ነህ እንዴ?!… ምን ታካብዳለህ?… ክባዳም!” አይነት ሰልጠን ያለ ቡጢ ከሰለጠኑት አካባቢ የሚሰነዘር ከሆነም ይህችን ጣል አድርገን እንቀጥላለን …

ዘላለም ጥም ቆራጭ ከሆነማ አርኪ
ለዝንታለም ሃሴት ከተሰኘ ምልኪ
የነፍስ እህል ውሃው በወግ ተበጥብጦ
በብልቃጥ በሲኒ ተደርጎ በጡጦ
ልልጆች ለህፃናት ይመረት አደራ
ታላቋን ኢትዮጵያ በቶሎ እንድንሰራ።

ቺርስ
በጊዮርጊስ

በርግጥ የአልኮል መጠጦችን በሬዲዮ፣ በቴሌቪዥን፣ በተለያዩ የህትመት ውጤቶች እንዲሁም በእስፖንሰር መልክ ማስተዋወቅ በጭራሽ አይገባም የሚል ደረቅ አቋም የለኝም። መንግሥትስ ለምን በህግ ‘ፈፅሞ እንዲከለከል’ አያደርግም?! የምል ወገኛም አይደለሁም፤ አይተዋወቅ ብዬም እየተነሳሁ አይደለም። በህግ የተከለለ የማስተዋወቅ ስርዓት ይኑረው (ወይም ህጉ ካለ በብርቱ ይተግበር) ነው መነሻዬ። አዎ በነጋ በጠባ ቢራ ቢራ አይበሉብን!.. ጎዳናዎቻችንን ሁሉ በቢራ አይሙሉብን!… ኧረ በዛ!… ኧረ ለከት ይኑረው!… ነው የኔ ሃሳብ። እኛ’ኮ ባይተዋወቅም በመጠጣት አንታማም!… ኑሯችን ለስካር ሩቅ አይደለም!… እንኳን አይዞህ ጠጣ ተብለን እንዲሁም ጠጪዎች ነን… ለዚህ እንኳን ብቁ ነን!…

የኛ አርቲስቶች፣ የኛ አስተዋዋቂዎች፣ የኛ ጋዜጠኞች፣ እና ሌሎች የሚመለከታቸው ባለሙያዎች አልኮልን የሚያስተዋውቁበትን መንገድ ልብ ብሎ ላስተዋለው ያስተዛዝባል ብቻ ሳይሆን ያሳስባልም። በተለይ ይሄን ማስታወቂያ እየሰሙ የሚያድጉ ልጆችስ ብሎ ማሰብ ለሞከረ የኔ ብጤ ክባዳም አንገት ያስደፋል።

‘የነፍስ እህል ውሃ ነው’… ‘የዘላለም ፍሰሃ ይሰጥሃል’… ‘ጨዋታህ ያለ ቢራ አይደራም’… ‘ወዳጅነትህ ያለ መጠጥ አይቀጥልም!’… እያልክ ላሳደግከው ልጅህ ኋላ ላይ ደግሞ ‘መጠጥ ይጎዳሃል’… ‘ጤናህን ያዛባብሃል’… ‘ከወዳጅ ያጣላሃል’… ምናምን ብትለው “አባዬ ደግሞ ታሾፋለህ እንዴ?!… አንተ አይደለህ እንዴ ለህዝቡ ስታውጅ የነበረው?!” ብሎ እንደሚያፌዝብህ ለማሰብ ጥልቅ ተመራማሪ መሆን የሚሻ አይመስለኝም። ያው እንዳላገጥን እንለቅ ካልሆነ በቀር…

አብዛኞቹ አርቲስቶች በግጥም፣ በዜማና በሙዚቃ ቅንብር ሲያንቆለጳጵሱት፤ በተለያየ የምስል ዲዛይን ሲያስሽሞነሙኑትና ሲያሞጋግሱት ስራዬ ብሎ ላያቸው አስካሪ መጠጥ የሚያስተዋውቁ ሳይሆን ብርቱ የነፍስ አድን መድሃኒት ሊያድሉ የሚሰናዱ ነው የሚመስሉት። አብዛኞቹ ነገረ ስራቸው ቅጥ ያጣ፣ የሚከፈላቸውን ገንዘብ እንጂ የሚሉትን ነገር ለሽራፊ ሰከንድ እንኳ ያሰቡበት የማይመስሉ ናቸው። በርግጥ ሁሉም ብሎ በአንድ ላይ መጨፍለቅ አግባብ አይደለም (እዚህ ውስጥ ያልተካተቱ አርቲስቶች ይቅር ይበሉኝ) በአብዛኛው ለአይናችን አሊያም ለጆሯችን የከበዱት አርቲስቶቻችን (ትልልቆቹም መጤዎቹም) ግን ቢያንስ የአንድ ቢራ አስተዋዋቂ መሆናቸው የአደባባይ ሃቅ ነው።

በነጠላ ዜማም ይሁን በነጠላ ፊልም ትንሽ ዝና ከተፍ ካለች ጥቁር መነፅርና ቢራ መለያቸው እየሆነች ነው። ኧረ ጎበዝ እየተሳሰብን እንጂ!… በጥቁሩ መነፅር ስታዩት ሌላ ነገር ወይም ሌላ ሃገር እየመሰላችሁ ይሆን እንዴ?!… እስቲ ከጥቁሩ መነፅር ውጡና ጎዳናዎቻችሁን… ህዝባችሁን እዩት… በሃላፊነት ጠጡ ከማለታችሁ በፊት በሃላፊነት ታስተዋውቁ ዘንድ ትለመናላችሁ።

“አውዳመት ሲደገስ ጎረቤት ሲጠራ
ወዳጅ ለመጋበዝ ገበታ ሲሰራ
እንዲሞቅ እንዲደምቅ ጨዋታ እንዲደራ
ይንቆርቆር ይቀዳ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ

ደስ ብሎ እንዲውል ያውዳመቱ ቆሌ
ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ አብሮ ይኑር ሁሌ
ወዳጅነት ጠብቆ ፍቅር እንዲደራ
ቅዱ ቅዱስ ጊዮርጊስ
ያዘቦት ያውዳመት የሁል ጊዜ ቢራ።”

ያዝ እንግዲህ!… ቢራ ከሌለህ አውዳመት የለም!… ወዳጅነት የለም!… ጎረቤት የለም!… መሰባሰብ የለም!… መተሳሰብ የለም!… ፍቅር ብሎ ነገር የለም!… ይልሃል!… በል እንግዲህ ጠጣና አውዳመትህን አድምቅ!… ወዳጅነትህንም ቀጥል… ቢራህም ሁሌም አብሮህ ይኑር ይልሃል!…

እኔም ልጨምርልህ… ከቢራህ የተለየህ እለት ድህነትህና ድንቁርናህ ፍንትው ብሎ ይታይሃልና በድህነትህ እንዳታፍር በኋላቀርነትህም እንዳታዝን ለከት የሌለው አጠጣጥ ጠጣ!… ጠጥተህ ድህነትህን እርሳ!… ይሄንንማ መፅሐፉም ብሎኛል ካልክም መብትህ ነው… መፅሐፉንም… ማስታወቂያውንም… እኔንም “እምቢኝ!” ያልክ ቀን ግን ወዳጅነት እንዴት እንደሚጠብቅና ድህነት እንዴት እንደሚፋቅ ሊከሰትልህ ጀምሯል ማለት ነው። ያኔ እናወጋለን!… ላሁኑ ግን ይህችን ሚጢጢዬ ግጥም እያላመጥክ ቀጥል …

‘አባቱ ደንዳና ብርቱ ጌሾ ወቃጭ፤
እናቱ ታታሪ ብቅል አብቃይ ቀያጭ፤
ኮበሌ ልጃቸው ሆነላቸው በጥባጭ፤
በል ዝም ብለህ ጨልጥ ያገር ሰው ተቀማጭ።’

ላሁኑ ሰላም
ትዝብቱ ግን ይቀጥላል

አብዲ ሰዒድ

Image

 
Leave a comment

Posted by on January 6, 2014 in ስብጥርጥር

 

የኤልያስ መንገድ

 

ኤልያስ መልካን የማያውቅ ይኖራል ብዬ አልገምትም። ካለም ዓለማዊ ሙዚቃ ሰምቶ የማያውቅ ሰማያዊ ሰው መሆን አለበት። ለነገሩ ኤልያስ ሰማያዊ ፋይዳ ያላቸው መዝሙሮችም አቀናባሪ ስለነበር ቢያንስ በዚያም መንገድ የሚያውቀው ይኖራል። የሙዚቃ ሰዎቻችን ወርቃማው የኢትዮጵያ ሙዚቃ ዘመን እያሉ የሚያወዱስት የነናልባንዲያን፣ የነሙላቱ፣ የነሮሃ፣ የነዋሊያስ እና መሰል የሙዚቃ ዘመኖችን ነው።

ከሮሃ ባንድ መቋረጥ በኋላ (በኢትዮጵያ አቆጣጠር ከ1980ዎቹ አጋማሽ ወዲህ) በሃገራችን ይህ ነው የሚባል ተፅዕኖ መፍጠር የቻለ የሙዚቃ ቅንብር ሂደት የነበረ አይመስለኝም። ከዚህ በኋላ የሰማናቸው ሙዚቃዎችም በአብዛኛው የከተፋና የአዝማሪ ቤት ስልቶች የሚጎላባቸው ለቀጥታ ጨዋታ እንደሆን እንጂ ሙዚቃዊ ጣዕማቸው እርካታን አጎናፅፎ በምሳጤ የሚያዳምጧቸው አልነበሩም። ይህን ማለት በዘመኑ የነበሩ ባለሙያዎችን ማጣጣል አይሆንም። ከነ ሮሃ በኋላ ኤሊያስና ሌሎች ብርቱ ወጣቶች እስኪመጡ ድረስ ሙዚቃው ፈዛዛ ነበር ብሎ በድፍረት መናገር የሚቻል ይመስለኛል። ታመነም አልታመነም የዚህን ዘመን የሙዚቃ ቅንብር ልዩ መልክ ከሰጡት ብርቅዬ ወጣቶች መካከል ኤልያስ ፊታውራሪው እንደሆነ የማይታበል ሃቅ ነው።

በዚህ ፅሑፍ ስለ ኤልያስ የቅንብር ርቀትና ጥልቀት ማውራት ጉዳዬ አይደለም፤ ላውጋው ቢባልም ተወርቶ አያልቅምና! እንደው ለመነካካት ያህል ጥቂት ስራዎቹን ልጠቃቅስና ወደ ሌላኛውና ወደምፈልገው የኤልያስ መንገድ አቀናለሁ። ከአፍሮ ሳውንድ፣ ከዜማ ላስታስ፣ ከደመራና ከሌሎች ባንዶች ጋር ኤልያስን ከሊድ ጊታሩ ጋር ማየት ምን አይነት ስሜት ይፈጥር እንደነበር የሚያውቅና የገባው ያስታውሰዋል። ከያሬድ የሙዚቃ ትምህርት ቤት በፈረንጆቹ የሙዚቃ መሣሪያዎች በቼሎና በፒያኖ በሀገር ውስጥ የባህል መሳሪያ ደግሞ በክራር መመረቁን ማውጋትም ለቀባሪው ማርዳት ነው።

ቴዲ አፍሮ የሚባልን ዘፋኝ በ’አቦጊዳ’ የቅንብርና የድምፅን ልኬት ሀ-ሁ ያስቆጠረው ኤልያስ ነው፤ ሚካኤል በላይነህን በ’አንተ ጎዳና’ ወደ ስኬት ጎዳና ያመጣው ኤልያስ ነው፤ ዘሪቱ ከበደን የእርካታ ዘር የዘራባት ኤልያስ ነው፤ ሚካያ በኃይሉን በልዩ ቀለም ያስዋባትና በ’ሸማመተው’ ደስታን እንድትሸምት ያስቻላት ኤልያስ ነው (ሰላማዊ እረፍት ሚካያ)፤ ኢዮብ መኮንንን እንደዚህ ያለ ልዩ የጣዕም ለዛ ያላበሰውና ‘እንደ ቃል’ ሲል የእውቅና ቃሉን የነፋበት ኤልያስ ነው (ሰላማዊ እረፍት እዮባ)። ጌዲዮን፣ ኃይልዬ፣ ጎሳዬ ኧረ ስንቱ ተዘርዝሮ ይዘለቃል?!… እንደው ዝም ብሎ መደመምና ማድነቅ እንጂ ምን ይባላል። በኢትዮጵያ አቆጣጠር ከ1990ዎቹ ወዲህ የታተመ ማንኛውንም አንድ አልበም ብታነሳና የተመቹህን ዘፈኖች ብትመረምራቸው ከጀርባቸው ኤልያስን የማግኝትህ እድል እጅግ ከፍተኛ ነው። እድሜህ ይለምልም አቦ!

ሌላኛው መንገድ – ግጥምና ዜማ

ኤልያስን ከአቀናባሪነቱ ባለፈ በግጥምና በዜማ ስራዎቹ ታደንቁት ይሆን?!… ከሆነ እሰየው!.. ካልሆነ ግን እንካችሁ አብዛኛዎቹ የኢዮብ መኮንን ግጥሞችም ዜማዎችም የኤልያስ መሆናቸውን ሳስታውስ በአድናቆት ነው፤ በተጨማሪም ለሚካያ፣ ለዘሪቱ፣ ለጎሳዬ፣ ለጌዲዮን እና ለሌሎችም ሰጥቷቸዋል። የትኞቹ እንደሆኑና በምን እንደሚለዩ… እነማንንን ከጀማሪነትና ከከታፊነት ወደ ዝና ማማ እንዳመጡ እናንተ ፍርዱባቸው፤ እኔ ግን በቅርቡ ዘመናችን ከወጡት ዘፈኖች መካከል አንድም በምልከታቸው (በግጥማቸው ይዘት)፣ ሌላም በዜማቸው ወይም በቅንብራቸው ለየት ያለ ነገር ይዘው ከመጡ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የኤልያስ እጅ አለበት የሚል የግሌ ድምዳሜ ላይ ደርሻለሁ። እስቲ ትዝ የሚሉኝን የኢዮብን ዘፈኖች ብቻ ልቆንጥርላችሁ

(1) ♫ እንዳጠፋሽ ♫

♫ እንዳጠፋሽ አጥፍቻለሁ
እንደሸፈትሽ ሸፍቻለሁ
ያየሽውን አይቻለሁ
ያለ ፅድቄ
ያለ ፍርድ ቆሜያለሁ ♫

♫ ቅጣትና ምህረት ዛሬ ሰው ለያዩ
አንዱን ከፍለው አንዱን አለፉ እንዳላዩ
ይማሩኝ ይክፈሉኝ ሳላውቅ የነገዬን
ልክ እንደ ንፁህ ሰው ተጠየፍኩት ያንቺን
ማነው ፃድቅ ሰው ሁሉም ሰው ሞኝ
እራሱም ሰርቆ ሌላ ሚዳኝ
ማነው ፃድቅ ሰው ካለ ይገኝ
እራሱም ሳይሰርቅ ሌላ ማይዳኝ ♫

(ግጥም፣ ዜማ፣ ቅንብር በሙሉ ኤልያስ መልካ)

(2) ♫ ደብዝዘሽ ♫

♫ መልክን የሻረው
አንቺ ጋር ምን ተሻለው
ከሩቅ ሳትስቢ
አየሁ ልቤ ስትገቢ ♫

♫ ካንቺ በላይ ቆንጆ ሞልቶ
ያውቃል ልቤም ቀርቦም አይቶ
ግን በምን በለጥሻቸው
ቆንጆዎቹን አስናቅሻቸው ♫

♫ ካንቺ በላይ እውቀታቸው
ስቄም ነበር በቀልዳቸው
ዝምታሽ በለጣቸው
ደብዝዘሽ አጋለጥሸቸው♫

♫ተቀይሯል ዓይኔ ወዷል መልክሽን
ሲመስሉሽ ያደንቃል ሲቀርቡሽ አንቺን
ቆንጆም ውብም ለኔ ያንቺ አይነት ብቻ
ባይም ልቤ አያምንም እንዳለሽ አቻ♫

(ግጥም፣ ዜማ፣ ቅንብር በሙሉ ኤልያስ መልካ)

(3) ♫ የቋንቋ ፈላስፋ ♫

♫ ይገርማል ይገርማል
ተርቦ ልብስ ይደርባል
ይደንቃል ይደንቃል
ተጠምቶ እሳት ይሞቃል ♫

♫ ለመናገር መጎምጀቱ
ለኛስ ነው ወይ መድሃኒቱ ?!
ተጠራርተን ከየቤቱ
ቃልን መርጠን መሻማቱ ♫

♫ ሃምሳ ሎሚ ከብዶት ሊሸከም ጉልበቴ
አታግዙኝ ይቅር ጌጤ ነው ቅርጫቴ
ለምን አደንቃለሁ ጥሩ ቃል መራጩን
በምናብ ውብ ስለት የምናብ ቆራጩን ♫

♫ ሁላችን ከሆንን የቋንቋ ፈላስፋ
በተግባር መስካሪ እማኝ እንዳይጠፋ
አንድም ሳይጨበጥ ሳይዳሰስ ስንኳን
ጀግና ልንባል ነው ቃል እንዳሰካካን ♫

(ግጥም፣ ዜማ፣ ቅንብር በሙሉ ኤልያስ መልካ)

ሁሉን መዘርዘር ድካም ነው። ብቻ ከኢዮብ ዘፈኖች መካከል ከሦስቱ በስተቀር በሙሉ የኤልያስ ናቸው። የ’እውነቷን ነው’ና ‘የኔ ቆንጆ’ የሚሉት ዘፈኖች ዜማውም ግጥሙም የዘሪቱ ከበደ ሲሆን ‘ረከዴ’ የሚለው የኦሮምኛ ዘፈን ደግሞ ግጥሙ የአብዲ ውቃና ጌታቸው ኃማሪያም ዜማውና ቅንብሩ ደግሞ የኤልያስ ነው። ‘ወኪል ነሽ’፣ ‘ማን እንደ ቃል’፣ ‘ደብዝዘሽ’፣ ‘ይዘባርቃሉ’፣ ‘የምድር ድርሻዬ’ በሙሉ የኤልያስ ናቸው። ግጥሞቹ ደግሞ ተስፋን፣ ብርሃንንና መልካምነትን እንጂ እዬዬን አያላዝኑም… ከሜሪ ዮናስ ጋር በትብብር የፃፉትን ግጥም ቆንጥሬ ላብቃ መሰለኝ …

♫ ነገን ላየው እጓጓለሁ
በል ሂድ ዛሬ ጠግቤያለሁ
ከንግዲህ መቼም ላትመጣ
ደህና ሁን በል ሌላ መጣ

በል ሸኘኝ በሰላም ልሂድ
ልጀምር የነገን መንገድ

ባዶ ቢመስልም ላንተ
በቅቶት የተቆረጠ
አለው የሁሉም ድርሻ
ጨለማውን ማስረሻ
በል በርታ አይቀርም ያንተ
ይመጣል ያንተን በእጁ ያካበተ♫

♫ ባይኖቼ እስካይ . . .
እጠብቃለሁ…
ተስፋን ይዣለሁ…
ድቅድቅ ቢሆንም…
ጨልሞ አይቀርም…
አብሬ አላልፍም… ከዛሬ ጋራ…
አላንቀላፋም… የነገን ጮራ… ♫

(ግጥም: ኤልያስ መልካና ሜሪ ዮናስ
ዜማ: ኤልያስ መልካና ጎሳዬ ተስፋዬ
ቅንብር: ኤልያስ መልካ)

ኤልያስ ሆይ!… ባለህበት አክብሮቴ ይድረስህ !
________
አብዲ ሰዒድ

Image

 
Leave a comment

Posted by on December 26, 2013 in ስብጥርጥር

 

ከግርግሩ መልስ – ¶ እኛና እነሱ ¶

“ይህን መሬታችሁን ትታችሁ ወደ ሐበሻ ተሰደዱ! (ወደ ሐበሻ ሂዱ)፤ በእርሷ አንድ ንጉሥ አለ። እርሱ ፊት ማንም ተበዳይ አይሆንም። ሐበሻ የእውነት ምድር ነች።”- ነቢዩ ሙሐመድ (ሰ.ዐ.ወ)

ይህ ነቢዩ ሙሐመድ በገዛ ወገኖቻቸው ተንኳሽነት በተከታዮቻቸው ላይ የሚፈጸመው ግፍና መከራ ሲበዛባቸውና ተከታዮቻቸውን ሊታደጓቸው እንደማይችሉ ሲገነዘቡ የተናገሩት ቃል ነው። ምክራቸውንም ተከትሎ 16 አባላትን የያዘው የመጀመሪያው የስደተኞች ቡድን ወደ ኢትዮጵያ ተጓዘ፤ ከመካከላቸውም ልጃቸው ሩቅያና ሌሎች ሦስት ሴቶች ሲኖሩ የተቀሩት ወንዶች ነበሩ። ኢትዮጵያም መሸሸጊያ አጥተው የነበሩ አማኞች ማረፊያ ሆነች፤ ተቀበለቻቸው፣ አስተናገደቻቸው፣ ጋሻ መከታም ሆነቻቸው፤ ይህም ኢትዮጵያን የመጀመሪያዋ የኢስላም የስደት አገር አድርጓታል። ከዚያም በተከታታይ ስደተኞች እየመጡ ለዘመናት ኢትዮጵያ ውስጥ በሰላም እንደኖሩ ብዙ ማጣቀሻዎች ተፅፈዋል።

አስሐማ ኢብን አብሑር (በአረቡ ዓለም አጠራር) በአክሱም ከነገሱ ነገስታት አንዱ ሲሆን የንጉስ አብሑር ብቸኛ ልጅ እንደነበር ይነገራል። በኢትዮጵያ በኩል የሚገኙ ታሪኮች ስሙ አፄ አደርእዝ እንደሚባል ያስቀምጣሉ። ሙስሊሞች ነጃሺ ወይም ሰይድ አህመድ ነጋሽ ብለው ይጠሩታል። ሌሎች የታሪክ ሊቃውንት ደግሞ ነብዩ ሙሐመድ በአረቢያ ምድር ነብይ ነኝ ብሎ በተነሳ ዘመን (በ7ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ አካባቢ) የነበረው የኢትዮጵያ ንጉሥ አርማሐ (ዳግማዊ አርመሐ) በመባል እንደሚታወቅና በስሙም ቅንስናሽ ሳንቲም ታትሞ እንደነበር ይገልፃሉ፤ በሳንቲሞቹ ላይም “ንጉሥ አርመሐ አዛኙና ሰላማዊው” የሚል ተከትቧል ይላሉ። ይህ ክርስቲያን ንጉስ ፍፁም ፍትሃዊና ሰላማዊ እንደነበር በተለያዩ ፀሐፊዎች ተመስክሮለታል፤ እንግዲህ ይህ ንጉስ ነው የነቢዩ ሙሐመድን ተከታዮች ተቀብሎ ያስጠለላቸው።

እዚህ ላይ አንድ ነጥብ ማንሳት ግድ ነው፤ እነዚህ ስደተኞች ሳውዲ አረቢያ በሌላ አገር በደረሰባት በደል ምክኒያት ሸሽተው የመጡ አይደሉም፤ በኃይማኖታቸው ምክኒያት የተገፉ፣ በራሳቸው ወገኖች ግፍ የተፈፀመባቸው ተበዳዮች እንጂ። በዘመኑ ሳውዲ አረቢያ በሃብቱና በጎሳው የሚመካ ጉልበተኛ ሁሉ ፈለጭ ቆራጭ የሆነ አንባገነናዊ ስርአት የሚያራምድባት ነበረች። ይህ ነው የሚባል አስተዳደራዊም ሆነ ኃይማኖታዊ ስርአት አልነበራትም፤ ሁሉም ያሻውን ጣኦታት እያመለከ ጉልበተኛው ደካማውን ይረግጥባት ነበር።

እንግዲህ እነዚህ አማኞችም በገዛ ሃገራቸው መድረሻ ሲያጡ ነው ወደ ሐበሻ ምድር የተሰደዱት፤ እነዚያ ጉልበተኛ ባለስልጣኖቻቸው ቢሰደዱም አልተዋቸዉም ነበር፤ ሁለት አንደበት ርቱእ የሆኑ ተናጋሪዎቻቸውን መርጠው ለንጉሱና ለሹማምንቱ የሚሆኑ የተለያዩ ስጦታዎችን አስታቅፈው ወደ ሐበሻ ላኩዋቸው። ኢትዮጵያ ከደረሱም በኋላ ንጉሱን እጅ ነስተው ተናገሩ -“እነዚህ ያስጠለልካቸው ሰዎች አጥፊዎች ናቸውና አሳልፈህ ስጠን፤ ወደ አገራችንም ወስደን እንቅጣቸው!” አሉት። ንጉስም ከመወሰኑ በፊት ችሎት እንዲሰየም አደረገ፤ በችሎቱ ላይም ብርቱ ሙግት ተካሄደ፤ ከወሳኞቹ ጥያቄና መልሶች በኋላ የንጉሱ ፍርድ ተሰማ –

“እኔንና ሃገሬን አምነው የመጡ ሰዎች ከዛሬ ጀምሮ በኔ ሃገርና ግዛት ጥብቆች ናቸው። ተራራን የሚያህል ወርቅ እንኳ ብትሰጡኝ አሳልፌ አልሰጣችሁም። አይዟችሁ! አትፍሩ! ማንም አይነካችሁም! በክፉ የሚደርስባችሁ ቢኖር መቀጫ ደንግጌበታለሁ። በፈለጋችሁት ስፍራ መስፈር ትችላላችሁ። ከእንግዲህ በኢብራሒም ወገኖች ላይ ፍርሃት አይኖርም።” (የሐበሻው ንጉሥ ነጃሺ)

ይህ የንጉሱ ውሳኔ ተወካዮቹን ያስደነገጠ ነበር። በስልጣናቸውና በሃብታቸው ብቻ ለሚመኩት ጉልበተኞች ይሆናል ብለው ያልጠበቁት ነገር ነው። ልብ በል! ይህ ንጉሥ በዚህ ወቅት ክርስቲያን ነው፤ ስደተኞቹ ደግሞ ሙስሊሞች ናቸው፤ በስልጣንና በሃብት ቢታሰብም እነዛ ይበልጥ ይበጁታል፤ ቢሆንም ፍትህን ማጓደል አልፈቀደምና ውሳኔው አልተዛነፈችም፤ ውሳኔው ላይ ኃይማኖትም ሆነ ሌላ ተቀጥላ አልነበረበትም፤ በርግጥ ያለፈን ዘመን የሐይማኖት ታሪክ ማወቁ ለውሳኔም አስተዋፅኦ አድርጓል የሚሉ አሉ። የሆነው ሆኖ ይህ ማንም ኢትዮጵያዊ ሊኮራበት የሚገባ የፍትህ ታሪክ ነው። ስደተኞቹ ከማመናቸው በስተቀር አንዳች ጥፋት ያልሰሩ ነበሩና!… ንጉሱም የመዘናቸው በዛ ነበርና!…

ከዚህ ውሳኔ በኋላ የነብዩ ሙሐመድ ተከታዮች በኢትዮጵያ ምድር በሰላም ኖረዋል። አግብተዋል፣ ወልደዋል፤ የተመለሱም እዚሁ ኖረው የሞቱም ብዙ ናቸው። የዚህ ህያው ታሪክ መዘከሪያ የሆነው ነጃሺ መስጂድም ከመቐለ 65 ኪ.ሜ ርቃ ከምትገኘው ውቅሮ ከተማ ወጣ ብላ በምትታይ ጉብታ ላይ ጉብ ብሎ ይገኛል። የንጉሱንና የስደተኞችን ቀብርም መጎብኘት ይቻልል። በተወሰኑ ርቀቶች ደግሞ “ከዲሕ ማርያም!” ቤተ ክርስቲያን ትገኛለች። ከነጃሺ ጋር ተዛማጅ ታሪክ እንዳላት ይነገራል። በመስጂዱም ሆነ በቤተ ክርስቲያኒቱ እድሜ የጠገቡ ሽማግሌዎችን ማግኘትና ትረካቸውን ማዳመጥ እዚህ ከተፃፈው የሚያስከነዳ ቁም ነገር ያስጨብጣል። በተለይ ትግርኛ ለሚችል ጉብኝቱ ይበልጥ ያማረ ይሆንለታል፤ ዛሬ ይሄን ስፅፍ ከአምስት ዓመት በፊት በቦታው ያገኘሁዋቸው ሽማግሌዎች፣ እየተሯሯጡ የከበቡኝ አቧራ የጠገቡ ህፃናትና ከመስጂዱ ጎን ካልበላህ ካልጠጣህ ብለው ያስቸገሩኝ ልበ ቀና እናቶች ከነ ሙሉ ፍቅራቸው ውል እያሉኝ ነው . . .

በነገራችን ላይ በዓለም ላይ የሚገኝ የትኛውም ሙስሊም ከመካ ቀጥሎ ሊጎበኛቸው ከሚመኛቸው ኢስላማዊ ቦታዎች አንዱ ነጃሺ ነው። በርካታ ሙስሊሞች ከአመታዊው የሳውዲ የሃጅ ስነ ስርአት በኋላ ወደ ውቅሮ በመምጣት የንጉሱን መቃብርና መስጂዱን ይጎበኛሉ፤ ይህ ነው የሚባል ምቹ ነገር ባይኖረውም ቅሉ የእስልምና ባለውለታ የነበረውን ንጉስ ቦታ በመዘየራቸው ብቻ ምስጋና አቅርበው ይመለሳሉ።

በነጃሺና በነቢዩ ሙሐመድ መካከል የነበረው ግንኙነት ለዘመናት የቀጠለ ነበር። ሙስሊሞች ድል ካደረጉና ማስተዳደር ከጀመሩ በኋላም በርካታ ደብዳቤዎችና ስጦታዎች እንደተለዋወጡ ተፅፏል። ጫማ፣ መቋሚያ፣ ልብስና ሽቶዎች ከተለዋወጧቸው ስጦታዎች መካከል ናቸው። ነብዩ ሙሐመድ በዘመኑ ለነበሩ የዓለም መሪዎች የኃይማኖት ጥሪ ደብዳቤ መላክ ሲጀምሩ በቅድሚያ የሰደዱት ወደ ሐበሻ ምድር ነው። ኢትዮጵያ ኖረው የተመለሱ ስደተኞችም ኢትዮጵያ ሳሉ የነበራቸውን መልካም ቆይታ መዝግበው አቆይተዋል፤ ይህም በመላው አለም የሚኖሩ ሙስሊሞች ሐበሻን እንዲወዱና እንዲያከብሩ ያደርጋቸዋል።

“ሐበሻ ገባን፥ መልካም ጎረቤቶችም አገኘን፥ በኃይማኖታችን ምክኒያት የሚደረግብን ተጽዕኖ አልነበረም። አላህንም በሰላም መገዛት ጀመርን። አንድም ችግርና መከራ አላጋጠመንም። የምንጠላው ነገርም አልሰማንም።” ሶሐባዎች (የነቢዩ ተከታዮች)

በአንድ ወቅት የሐበሻ ንጉስ ልዑካን ቡድን ወደ ነቢዩ ሙሐመድ አገር ደረሰ። ነቢዩም እንግዶቹን እራሳቸው ማስተናገድ ጀመሩ። ባልደረቦቻቸውም አሏቸው –
“የአላህ መልክተኛ ሆይ!… እኛ እኮ እነሱን ለማስተናገድ እንበቃለን!” 
ነብዩም መለሱ – 
“እነኚህ ሰዎች ባልደረባዎቼን በሚገባ አስተናግደውልኛል። በመሆኑም ራሴ በማስተናገድ ውለታቸውን ልመልስ እወዳለሁ።” (ሐዲስ)

ታዲያ የዛሬዎቹ የሳውዲ ገዢዎች ለጎሳቸው እንኳን ያልሆኑትን… ነቢዩንና ተከታዮቻቸውን ያሰቃዩትን… የዛኔዎቹን አሳዳጆች አይነት መሆናቸው ለምን ነው?!… ሙስሊም የሆነ ሁሉ ይህን ውለታ እንደማይረሳና የነቢዩንም ቃል እንደሚያከብር ይታመናል። እነሱ ደግሞ ሙስሊሞች ናቸው። ምነው ታዲያ ቃላቸውን በሉ?… ግራ ያጋባል። ስለሆነም ታሪክ የሚያውቅ ሁሉ እውነታውን እያነሳ ለእኩይ ስራቸው ቢወቅሳቸው የተገባ ነው።

ይህ ሲባል ግን በሰሞኑ አንዳንዶች ሲያደርጉ እንደታዘብነው አይነት ኃይማኖታዊ በሆነ መልኩ መላው አረብን “ከኑግ የተገኘህ ሰሊጥ አብረህ ተወቀጥ” አይነት ፈሩን የለቀቀ ጭፍጨፋና የእስልምና መመሪያዎችን ረገጣ ሚዛናዊ አይደለም ብቻ ሳይሆን የሚያስከትለው መዘዝ የከፋ እንዳይሆንም መጠንቀቅ ያስፈልጋል። ሳውዲ አረቢያ አገር ናት፤ እስልምና ኃይማኖት ነው። በጥንቱ ዘመን ኢትዮጵያና ንጉሷ ውለታ የዋሉት ለሙስሊሞች እንጂ ፖለቲካዊ ወይም ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያገኙበትት ዘንድ በሚል ለሳውዲ አረቢያ አይደለም። ንጉሳዊያኑ የሳውዲ ገዢዎች የለየላቸው አምባገነኖች ናቸው። ከዘመናዊው ዓለም አስተሳሰባዊ ስልጣኔም ቢሆን የራቁ ናቸው። ለዜጎቻቸውም ሆነ ለሙስሊሞችም የሚመቹ እንዳልሆኑ በበርካታ አጋጣሚዎች አሳይተዋል። ስለዚህም ቁጣና ውግዘት ሲያንሳቸው ነው!!!

ለነቢዩ ሙሐመድ የተደረገውን ውለታ እያስታወስን ችግር ላይ ያሉ ዜጎቻችን ያለ ስቃይና እንግልት ወደ ሃገራቸው በሰላም እንዲመለሱ ግፊት ማድረጋችንን መቀጠሉ እጅግ መልካምና የሚገባ ነው። በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ከኃይማኖት ጋር ማደበበላለቁ ግን አይጠቅምም። ሰበካውን ማካሄድ የሚፈልግ የትኛውም ሃይማኖተኛ በየማምለኪያው ያድርገው፤ ይህ ጉዳይ የሰው ልጆች መበደል እንጂ የሰማይ ቤት ንግድ አይደለም። ሳውዲ አረቢያ ለምን ተነካች በሚል አጉል ጠበቃነት የሚቃጣቸው “ሙስሊሞችንም” ታዝበናል፤ ለነዚህኞቹ ደግሞ የጀነት መንገድ በሳውዲ አረቢያ በኩል ሳይሆን በልቦናችሁ በኩል ነውና ኢ-ሰብአዊ ድርጊትን ለማውገዝ ቅድመ ሁኔታ ማበጃጀት አያስፈልግም እንላለን። ሳውዲ አረቢያ ወገኖቻችን ላይ የምታደርገውን እንግልት ታቁም!!!

ሰላም ለወገኖች!
ሁላችሁም ያለ ስቃይና እንግልት በሰላም እንድትመጡ ይሁን! 
___________
አብዲ ሰዒድ

መረጃዎች: “እስልምናና ኢትዮጵያ” እና “የሰይድ አህመድ ነጋሽ ታሪክ” ከሚሉት መፃፎች ተጠናቅረዋል!

Image

 
Leave a comment

Posted by on November 21, 2013 in ስብጥርጥር

 

ብቃት!

 

ከመውለድ ከመክበድ ከ’ናትነት በላይ
ከእልፍኝ ከማጀት ከኩሽናም በላይ
ይልቃል ይርቃል የተሰጠሽ ፀሐይ
ተ – ነ – ሽ !
አ – ት – ል – ፈ – ስ – ፈ – ሽ
ን – ቂ !
አ – ት – ው – ደ – ቂ
የትም አታርክሽው የውስጥሽን ሲሳይ!
____________________

ከዚህ ፅሁፍ ጋር የተያያዘው ምስል J. Howard Miller በተባለ አሜሪካዊ ግራፊክ አርቲስት የዛሬ 70 አመት ገደማ የተሰናዳ ነው። ይህ ግለሰብ በሁለተኛው የአለም ጦርነት ወቅት ለጦርነቱ ማነሳሻነት የሚውሉ የፕሮፓጋንዳ ምስሎችን በማዘጋጀት ይታወቃል። “We Can Do It!” የሚል ርዕስ የተሰጠው ይህ ምስልም ከስራዎቹ አንዱ ነው።

በምስሉ ላይ የምትመለከቷት ሴት Geraldine Hoff Doyle ትባላለች። በ1942 በአሜሪካ ሚቺጋን በሚገኝ የማሽነሪ ፋብሪካ ውስጥ የብረታ ብረት ሰራተኛ ነበረች። በወቅቱ የ18 ዓመት ወጣት የነበረችውን ይህችን የብረት ሰራተኛ አንድ የዩናይትድ ፕሬስ ኢንተርናሽናል ፎቶ አንሺ በስራዋ ላይ ሳለች ፎቶ አነሳት… ይህን ፎቶ ደግሞ ሚለር በዚህ መልኩ አሰናዳው… ከዚያም ይህ ፎቶ ሴቶችን ለፋብሪካ ስራና ለጦርነቱ እገዛ እንዲያደርጉ በማነሳሳት በኩል ብርቱ አስተዋጽኦ እንዳደረገ ይገመታል።

በዘመኑ የፋብሪካ ስራዎች በአብዛኛው የሚከወኑት በወንዶች ነበር… የወንዶች ስራ ብቻ ተደርገው ይቆጠሩም ነበር… በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ምክኒያት በርካታ ወንዶች ወደ ውትድርናው በመሰማራታቸው ሴቶችን ማበርታት ግድ ሆነ… በዚህም በርካታ ሴቶች የብረታ ብረትና የተለያዩ የፋብሪካ ስራዎች ላይ በመሳተፍ ጦርነቱን እንዲያግዙ ሆነዋል። አግዘዋልም!

ምንም እንኳን በ1943 ገደማ ለተካሄዱ ጥቂት የጦርነት ቅስቀሳዎች ያገለገለ ቢሆንም ያን ያህል ለማላው ጦርነት ጥቅም ሰጥቷል ማለት ግን አይቻልም… ጦርነቱም አበቃ… ፎቶውም ተረሳ!…

በ1980ዎቹ መጀመሪያ አካባቢ ግን ምስሉ ከተመሸገበት ስርቻ ተጎተተ… ከ40 አመታት በኋላ ዳግም ነፍስ ዘርቶ ተነሳ… የምስሉ ትንሳኤም ሆነ!… ያሁኑ አነሳስ ግን ለጦርነት ቅስቀሳ አልነበረም… ይልቁንም ለሴቶች መብት ተሟጋቾች ልሳን ሆኖ ለማገልገል እንጂ!

ምስሉ በብዙ ሺህ ኮፒዎች ተባዛ… በርካቶች አደባባይ ይዘውት ወጡ… መጽሐፎች፣ መፅሄቶች፣ ቴምብሮች፣ እና በርካታ የጥናት ስራዋችም ይህን ምስል ተጠቅመዋል… በቤት ውስጥ… በትምህርት ቤት… በስራ ቦታ እና በተለያዩ አካባቢዎች የሚካሄዱ ቅስቀሳዎች ተጧጧፈውበታል…

“ሴቶችን ማሳነሱ ይቁም!”…
“አትችይም የሚል አስተሳሰባችሁን ዋጡት!”…
“እችላለሁ!”
“እንችላለን!”
“ትችላለች!”
ለሚሉ ዘመቻዎች በሚገባ አገለገለ… አሁንም ድረስ እያገለገለ ይገኛል… የተጠቀሙበት ተጠቀሙ!… በርግጥም ሁሉም ሴቶች ይችላሉ… እመኚኝ ትችያለሽ!

ይህን ማራኪና አነቃቂ ምስል እንዳስታውሰው ያደረገኝ World Economic Forum በሰሞኑ ያወጣው የ2013 Global Gender Gap Report ነው… ይህ ሪፖርት አገሮች በሴቶች ተሳትፎ ዙሪያ ያለቸውን ደረጃ ያስቀምጣል…

በኢኮኖሚው፣ በፖለቲካው፣ በትምህርቱ እና በጤናው ዘርፍ የሴቶች እኩልነት የት ድረስ እንደደረሰ በተለያዩ መመዘኛዎቹ መዝኖ ደረጃውን ይሰጣል… በዚህ አመት በወጣው ሪፖርት መሠረት ኢትዮጵያችን ከ136 ሃገሮች 118ኛ ደረጃን ይዛለች… ይህ ማለት ሴቶች ከላይ በተዘረዘሩት መስኮች ያላቸው ተሳትፎ እንዲያው ዝም የሚያሰኝ መሆኑን የሚያሳይ ነው!!…

በዚህ ሪፖርት አይስላንድ 1ኛ ስትሆን… የመን የመጨረሻ ደረጃን ይዛለች… የኖርዲክ ሃገሮቹ እነ ፊንላንድ፣ ኖርዌይ እና ስውዲን አይስላንድን ሲከተሉ እነ ደቡብ አፍሪካ ሌሴቶ እና ፊሊፒንስ ደህና ተስፋ ያላቸው በሚል ተፈርጀዋል… ጎረቤታችን ኬንያ እንኳ ኢትዮጵያን ታስከነዳታለች (ያው የሷም ገና ቢሆንም)…

አዎ ኢትዮጵያ ዛሬም ለሴቶች የምትመች አይደለችም!… ብትመችም እጅግ ጥቂት ለሆኑና ከቁጥር ለማይገቡ የከተማ ሴቶች ነው (እሱም ምቾት ከተባለ ማለቴ ነው)… የሴቶችን ምቾት ሳትጠብቅ መሰልጠንና ማደግ ደግሞ ከቶም የማይታሰብ ቅዠት ነው… ሴቶችን የዘነጋህበት ጉዞህ አንተም የተዘነጋህ ያደርግሃል… ሴትን ስታቀና መንገድህ ይቀናል… ሴትን ስትንቅ በርግጥም ትናቃለህ!… ይህን ደግሞ ባይናችን እያየን ነው… ያከበሩት ሃገራት ከብረዋልና!

እናም ፈረንጆቹ ከ60ና 70 አመት በፊት የተጠቀሙት አይነት ዘመቻ ሳያስፈልገን አይቀርም… ከ20ና 30 አመት በፊት ጀምረው የተጓዙበት ጎዳና ሳይጠቅመን አይቀርም… “አትችይም!”… “አይሆንም!”… ምናምን የሚሉሽን አትስሚያቸው… እመኚ አሳምረሽ ትችያለሽ!…

ምናልባት ይህን የምታነብ ነቃ ያለች ከተሜ ሴት ብትገኝ…

“ምን ትችያለሽ ትሽያለሽ ይለኛል?… ይህ አባባል በራሱ የበታች ነሽ አይነት ነው!… እናም ይህ አይነት ቅስቀሳ አይመቸኝም!”… ምናምን የሚል ፍልስፍና ይቃጣት ይሆናል…
ለዚህች አይነቷ ነቄ… አየሽ ነፍሴ… ይኸው መልሴ እንላታለን… “ትችያለሽ!” የሚል ቃል እንደውሃ የጠማት… ህልሟን አጉል ልማድ የጨፈለቀባት… ውጥኗን ከንቱ ቃል ያጨነገፈባት… ትችያለሽ… ተነሽ የሚለው ቃል ብቻውን የሚያለመልማት በሚሊዮን የምትቆጠር ኢትዮጵያዊት ሴት አለች ነው …

እናም ተነሽ… አንቺ ስትነሽ ሃገር ትነሳለችና!
YES YOU CAN DO IT !!!

Image

 
Leave a comment

Posted by on November 3, 2013 in ስብጥርጥር

 

ፋጡማ ሮባ

Image

ይህ ፎቶ ታሪካዊ ነው። የኢትዮጵያ የሴቶች የማራቶን ጀብዱ በኦሎምፒክ መንደር ሲበረበር በቅድሚያ የሚገኘው ይህ ፎቶ ስለመሆኑ ምንም ጥርጥር የለኝም። ይህች ብርቅዬ ሴት በ23 ዓመቷ ኢትዮጵያ ከዚያ በፊት በሴቶች ማራቶን በኦሎምፒክ ውድድር አግኝታ የማታውቀውን ክብር አላብሳታለች። 

እ. ኤ. አ በ1996 በአታላንታ ተካሂዶ በነበረው ኦሎምፒያድ ኢትዮጵያችን 2 የወርቅ ሜዳሊያ ነበር ያገኘችው። አንዱን ይህች የኔ ጀግና ፋጡማ ሮባ በማራቶን ስታስመዘግብ ሌላኛው ደግሞ በ10ሺህ ሜትር በኃይሌ ገብረ ሥላሴ ነበር የተመዘገበው። በዚያ ውድድር የጌጤ ዋሚን ነሃስ ጨምረን ባጠቃላይ ሦስት ሜዳሊያ ይዘን ተመልሰናል።

በወንዶች ማራቶን አበበ ቢቂላን በሮም እንደምንዘክረው፣ በሴቶች 10ሺህ ደራርቱን በባርሴሎና እንደምንዘክራት ሁሉ በሴቶች ማራቶን የምናነሳትና ፋጡማን ነው። አይና አፋሯ ፋጡማ ህያው ታሪክ ሰርታለች። እንስፍስፉ ደምሴ ዳምጤ ሲቃ እየተናነቀው የመጀመሪያዋ እያለ ያወራላት ፋጡማን ነው። ዋዋዋ ደምሴ አወራሩ መጣብኝ ;( 

አሁን በቅርቡ ሎንዶን ላይ ያስቦረቀችን ቲኪ ገላና ከድሏ በኋላ በሰጠችው ቃለ ምልልስ ይህችን ብርቅዬ ሴት አልዘነጋቻትም – 
“. . . ፋጡማ ሮባ የኔ ጀግና ናት፤ የርሷን ታሪክ በመጋራቴ እጅግ በጣም ደስተኛ ነኝ፤ ይህን የወርቅ ሜዳልያዬን ለሁሉም ኢትዮጵያውያን አበርክቻለሁ፡፡ . . . ” ቲኪ ገላና።

እነሆኝ እኔም ነገ (Aug, 2013) በሚጀመረው የሞስኮ 14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በውድድሩ መጀመሪያ ቀን ቲኪን ጨምሮ በማራቶን ለሚወዳደሩት ሴቶቻችን መልካም ውጤት ስመኝ ፋጡማን እያስታወስኩ ነው። 

ሴቶቻችን ሆይ ብርታት፣ ጥንካሬ፣ መረጋጋትና ድል ከናንተ ጋር ይሁን!… ይቅናችሁ!

> ቲኪ ገላና ይቅናሽ !
> መሰለች መልካሙ ይቅናሽ !
> ፈይሴ ታደሰ ይቅናሽ !
> አበሩ ከበደ ይቅናሽ !
> መሠረት ኃይሉ ይቅናሽ ! 
> መሪማ መሐመድ ይቅናሽ ! 
(መሪማ ተጠባባቂ ናት)

ሁሌም ክብር ለጀግኖቻችን! 
ሰላም ኢትዮጵያዬ ❤

___________
አብዲ ሰዒድ 
ነሐሴ 2005 E.C

 
Leave a comment

Posted by on August 9, 2013 in ስብጥርጥር

 

የሩጫችን ፈርጥ – ዋሚ ቢራቱ

14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ሊጀመር በአንድ እጅ ጣቶች የሚቆጠሩ ቀናት ብቻ ቀርተውታል… እኛም በአትሌቶቻችን ድል ልንሸልልና ልንፎክር አሰፍስፈናል… ይቅናቸው አቦ!… ይህ እንዲህ ከጫፍ እስከ ጫፍ በአንድነት የሚያስፈነድቀን የአትሌቶቻችን ድል በዓለም መለያችን ከሆነ ዘመን ውሎ አድሯል- እድሜ ለሯጮቻችን ብርታት!…

እስቲ አጋጣሚውን አስታከን ህያው ታሪክ እንቆንጥር!… ክቡር ስም እንዘክር!…

ከ50 ዓመት በፊት አበበ ቢቂላ የሮምን ማራቶን በባዶ እግሩ ፉት ሲላትና ሕዝቡን አጃኢብ ሲያሰኝ… 42 ኪሎ ሜትር ይቅርና 42 ሜትር የሮጠ በማይመስል መልኩ ሩጫ እንደሚጀምር አይነት ሰውነቱን ሲያፍታታ… ዘና ብሎ ዱብ ዱብ ሲል… ጎንበስ ቀናውን ሲያጧጡፈው ያዩት ሲደመሙ… “ምን ያለው ሰው ነው?… አይደክምምን?” ሲባባሉ… ተሸክመውት ሲጨፍሩ… በአድናቆት ሲጠይቁት… የአበበ መልስ ይበልጥ አስደንግጧቸው ነበር…

“እኔ የዓለም አንደኛ፣ የኢትዮጵያ ግን ሁለተኛ ሯጭ ነኝ”
“እንዴት?… ኢትዮጵያ ካንተም የተሻለ ሯጭ አላትን?
“አዎን… እሱ ስለታመመ ነው እኔ የመጣሁት!”

ጋዜጠኞችም ተገረሙ… ተገርመውም ወሬውን አራገቡት… ኢትዮጵያ በሁለተኛ ሯጯ ድል አደረገች ሲሉ አጧጧፉት… ያ አንደኛ የተባለውን አትሌት ለማየትም ጉጉታቸውን ገለፁ… ይህ አበበ ቢቂላ በኩራትና በአድናቆት አክብሮቱን የገለጸለት ታላቅ አትሌት ሻምበል ባሻ ዋሚ ቢራቱ ነው… ይህ ሰው ወደድንም ጠላንም… አመንም አላመንም…. በኢትዮጵያ ሩጫ እና ፉክክር በወጉ እንዲታወቁ ካደረጉ በጣም ጥቂት ፊታውራሪዎች ዋነኛው ነው!

አንጋፋው የብስክሌት ተወዳዳሪ ገረመው ደንቦባም ይህን ያረጋግጣል “በኢትዮጵያ ጦር ኃይሎች ውድድር ላይ ማንም ሰው ተከትሎት አይገባም ነበር… ቁመናው፣ ጥንካሬው፣ ብርታቱ፣ ሁሉ ነገሩ ለሩጫ የተፈጠረ ነው… የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያውቀውንና እንዲህ በአድናቆት የሚመለከተውን ሩጫ በሚገባ ያስተዋወቀ ዋሚ ነው… በየቀኑ ከሱሉልታ አዲስ አበባ ጠዋትና ማታ ይሮጥ ነበር…. “

በ1909 ዓ.ም ሱሉልታ የተወለደው ዋሚ ሩጫን ለውድድር ማሰብ የጀመረበት ሁኔታ የሚገርም ነበር… እናቱ በጋዜጣ የተጠቀለለ ቡና ከገበያ ገዝታ ትመጣለች… አዲስ አበባ ውላ ከግብይት የተመለሰችው እናቱ ቡናዋን ቆልታ ጋዜጣውን ትጥለዋለች… አንስቶ ሲያየው አንድ አጭር ሰው ሲሮጥ የተነሳውን ፎቶ ያያል… “እኔ እዚህ ጋራ ሸንተረሩን ስወጣ ስወርድ የምውል ሰውዬ ብወዳደር አሸንፋለሁ”… ሲል ተነሸጠ… ተነሽጦም አልቀረ… ሩጫውን ተያያዘው…

ከዓመታት በኋላ በ1945 ዓም አዲስ አበባ መጣ… በዘበኝነት ሥራ ተሰማራ… ጦር ሰራዊትን ከዛም ክቡር ዘበኛን ተቀላቀለ… ከዚያ በኋላማ የ5 ሺህ… የ10ሺህ እያለ የበርካታ ሩጫዎች ባለድል ሆነ… የሜዳሊያ እና የማእረግ ሽልማቶችንም ከንጉሡ እጅ ተቀበለ… በዘመኑ የሚፎካከረው እንዳልነበር ብዙዎች ይስማማሉ… የዋሚን ታዋቂ መሆን ተከትሎ ብዙ ጥሩ ጥሩ ሯጮች እንደመጡም እሙን ነው…
በዘመኑ ድንቅ የነበሩት እነ ማሞ ወልዴ… እነ ባሻዬ ፈለቀ… እነ አበበ ዋቅጅራ… እነ ገብሬ… እያልን ብናወራ ሁሉም የሚወራ ታሪክ ይኖራቸዋል…

ለኢትዮጵያ ሁለተኛ ተሳትፎዋ ለነበረው የሮም ኦሎምፒክ ከታጩት ፊታውራሪ አትሌቶች መካከል አንዱና ተስፋ የተጣለበት ዋሚ ቢራቱ ነበር… አበበ ቢቂላ ምንም እንኳ ጎበዝ ሯጭ ቢሆንም በእድሜ ልጅ ስለነበር (ከነ ዋሚ አንፃር) ብሎም ሌሎቹ ከሱ የተሻለ ሰዓት ስለነበራቸው በሮም ኦሎምፒክ ቡድን ውስጥ አልተካተተም ነበር… የወቀቱ ስውዲናዊ አሰልጣኝ አበበን እምነት የጣሉበት ለቀጣዩ ኦሎምፒክ ነበር…

መጨረሻ ላይ ግን ታሪክ ተለወጠ… ደብረዘይት ስልጠና ቆይተው የጉዞ ዝግጅት ሲጠናቀቅ ዋሚ ታመመ መሄድ እንደማይችልም ተረጋገጠ… አሰልጣኙም “በሉ አበበን አምጡልኝ!” አሉ… አበበም ዋሚን ተክቶ ሄደ… ታሪክ ጠራችው… ዋሚን ግን ታሪክ ረሳችው…

አበበ ጀግና ነው ሁላችንም እንወደዋለን… እናከብረዋለን… እናደንቀዋለን… ነገር ግን ራሱ አበበ የሚያደንቀውን ዋሚን ብንዘነጋ ልክ አይሆንም… በነገራችን ላይ የዘንድሮን አላውቅም እንጂ እስከ ባለፈው ዓመት ድረስ እኝህ ታላቅ የሩጫ አባት በሕይወት እንደነበሩ አውቃለሁ… በ96 ዓመት እድሜያቸው እንኳ ይሮጡ ነበር…

ተረስተው ከከረሙበት ጥቂት አስታዋሽ አግኝተው በጣም መጠነኛ የሆነች ድጎማ ተደርጋላቸው እንደነበርም አስታውሳለሁ…
ዋሚ
. . . ዋሚ
. . . . . . ዋሚ!

ሁሌም ክብር ለታላላቆቻችን!

 

Image

 
Leave a comment

Posted by on August 6, 2013 in ስብጥርጥር

 

የዓለም ፀሐይ ዓለም . . .

ዓለም ፀሐይ ወዳጆ . . .

alem1
አርቲስት ዓለም ፀሐይ ወዳጆን የማያውቅ የጥበብ ቤተሰብ ይኖራል ብዬ አልገምትም… ከኖረም ከቲያትሩም፣ ከትወናውም፣ ከዘፈኑም፣ ከግጥሙም ዓለም ራሱን ያራቀ… በስሚ ስሚ ወሬ እንኳን በኪነ ጥበብ ዘርፍ ነፍሱን ያላፀደቀ መሆን አለበት… ዓለም ፀሐይ ዘርፈ ብዙ የሆነች የጥበብ ፈርጥ ናት!… የተውኔት ጸሐፊ፣ የቲያትር አዘጋጅ፣ ተዋናይ፣ ገጣሚ ከመሆኗም በተጨማሪ የኢትዮጵያ ሕጻናት ቲያትር መስራች እንዱሁም በውጭው ዓለም በተለይም በአሜሪካ ኢትዮጵያዊ የጥበብ ስራዎች ከኢትዮጵያዊያን ልቦች እንዳይጠፉ በብርቱ የምትንቀሳቀስ የጥበብ አድባር ናት!… ጣይቱ የጥበብ ማእከልን ይጠቅሷል…

የሷን የጥበብ ስራዎች በሙሉ ልዘረዝር አልተነሳሁም!… ሁሉም በየመስኩ እንደመልካቸው ለየብቻ ሊዘርዘሩና ሙያዊ ትንተና ሊሰጥባቸው የሚችሉ ናቸው… ስለ ትያትር ስራዎቿ ለብቻ… በመጽሃፍና በሲዲ ስላሳተመቻቸው ግጥሞቿ ለብቻ… ለበርካታ ዘፋኞች ስለሰጠቻቸው የዘፈን ግጥሞች ለብቻ.. እያልን ከጥበብ ባሕሯ ልንጨልፍ ይቻለናል!… እናም ይህ ጽሁፍ ትኩረት የሚያደርገው የዘፈን ግጥሞቿ ላይ ብቻ መሆኑን መግለጹ ያስፈልገኛል…

አብዛኞቻችን ብዙውን ጊዜ ትኩረት የምንሰጠው ለዘፋኞች እንጂ ለግጥምና ዜማ ደራሲዎችም ሆነ ለአቀናባሪዎች አይደለም… በእርግጥ ዘፈን የድምጽ ስራ በመሆኑ ዘፋኙን ማወደስና ማክበር የተገባ ነው… አንድ ሙዚቃ ሙሉእ ሆኖ ቀልብን እንዲገዛ የሁሉም አስተዋጽኦ የየራሱ ዋጋ እንዳለው መዘንጋቱ ግን የጥበብን ውህደት እንደመዘንጋት ይቆጠራል… ዜማ ያለ ግጥም… ግጥምም ያለ ዜማ… ሁለቱም ያለ ጥሩ ቅንብር ለመንፈስ እርካታን የሚለግስ ዘፈን ሊሰጡን አይቻላቸውም… ሶስትም አንድም እንደማለት ነው… የማይነጣጠሉ!… ዓለም ፀሐይ የምትታወቀው ውስጥ ዘልቀው በሚገቡ ግጥሞቿ ነው… እናም ግጥም ላይ ብቻ ትኩረት አደርጋለሁ…

ከወራት በፊት ስለ ዘፈን ግጥሞቿ አወራኋት… ባጋጣሚ ውይይታችንን የቀረጽኩበት ድምጽ መቅጃ ከጄ ወጣ… በሲዲ አሊያም በሌላ መሰል ነገር አልገለበጥኩትም ነበርና ተበሳጨሁ… በድጋሚ ላውራሽ ማለቱ ደግሞ እሷን ማድከም እንደሆነ ተሰማኝ… እፍረትም ሸንቆጥ አደረገኝ… እናም መልሼ እስካገኘው መጠባበቅ ግድ ሆነብኝና እስካሁን ቆየሁ… መቼም ቅር እንደማትሰኝብኝ እምነቴ ነው… ከራሷ የሰማሁትን ለማጠናቀር ስለፈለግኩ እንጂ በተባራሪ የሰማኋቸውን እንዲሁም ካሴቶች ላይ ያየኋቸውን ለቃቅሞ መጻፍ እንደሚቻለኝ ዘንግቼው አይደለም… ጊዜዋን ሰውታ ስለ ስራዎቿ ስላዋየችኝ እጅግ እያመሰገንኩ ከራሷ አንደበት የሰማሁትን በራሴ መንገድ ለመነካካት እሞክራለሁ…. እጅግ ከባድ ቢሆንም…

ከ400 በላይ የዘፈን ግጥሞች . . .

ስለ ሙሉ የዘፈን ግጥሞቿ በዚህ ጽሁፍ ለመዘርዘር መሞከር የማይታሰብ ነው… ምን ያህል ግጥሞች ለምን ያህል ዘፋኞች እንደሰጠች በእርግጠኝነት ለመናገር ይቸግራታል… “የማታ እንጀራ” የተሰኘው የግጥም መጽሐፏ ሲመረቅ በድምጽ ባለሙያዎችና በጓደኞቿ ትብብር የተዘጋጀ ‘ሰርፕራይዝ’ አይነት ስጦታ ተበረከተላት… ስጦታው ሲታይ እስካሁን የሰራቻቸውን የዘፈን ስራዎች ያሰባሰቡ ሲዲዎች ነበሩ… በደስታና በአግራሞት መሃል ሆና አመስግና ተቀበለቻቸው… በኋላም ከ400 በላይ የዘፈን ግጥሞች ለ47 ዘፋኞች እንደሰጠች ተረዳች… ተገረመችም… ተደሰተችም… አመሰገነችም…

ምንም እንኳ ወዳጆቿ የቻሉትን ያህል ለማሰባሰብ ቢሞክሩም ሙሉ ነው ለማለት ግን አይቻልም… ምክኒያቱም በካሴት የመቀረጽ እድል ያላገኙ በድሮው ጊዜ በቲያትር ቤቱ የባሕል ክፍል ይዘፈኑ የነበሩ ዘፈኖችን ማካተት አልተቻለምና ነው… እንደ ምሳሌም የነ ጠለላ ከበደን፣ የነ ፀሐይ እንዳለን፣ የነ መልካሙ ተበጀን በካሴት ያልታተሙ ዘፈኖች መጠቃቀስ ይቻላል….

የሷን ግጥም ያልዘፈነ ዝነኛ ድምጻዊ ማግኘት ይከብዳል ከክቡር ዶክተር ጥላሁን ገሠሠ ጀምሮ እነ ማሕሙድ አህመድ፣ ሙሉቀን መለሰ፣ ቴዎድሮስ ታደሰ፣ ፀሐዬ ዮሐንስ፣ ሻምበል በላይነህ፣ ዳዊት መለሰ፣ ኅይልዬ ታደሰ፣ ግርማ ተፈራ፣ ብዙአየሁ ደምሴ፣ ሰጠኝ አጣናው እንዲሁም ከሴቶች አስናቀች ወርቁ፣ አስቴር አወቀ፣ ኩኩ ሰብስቤ፣ በዛወርቅ አስፋው፣ አቦነሽ አድነው፣ ሂሩት በቀለ፣ ፋንትሽ በቀለ፣ አሰፉ ደባልቄ እያልን ከብዙ በጥቂቱ መጠቃቀስ ይቻለናል… የቻልኩትን ያህል በቀጣይ ለመነካካት እንደምሞክር ቃል እየገባሁ ላሁኑ ሙሉቀን መለሰ ላይ ብቻ ትኩረት አደርጋለሁ…

ሙሉቀን መለሰና የዓለም ፀሐይ ግጥሞች . . .

muluken
ሙሉቀን በተነሳ ቁጥር የዘፈኖቹን ግጥሞች ውበትና ጥልቀት… የተሸከሙትን መልእክትና ቁምነገር ያለማንሳት አይቻልም!… ዘመናችንን ሙሉ ካጣጣምናቸው ከአብዛኛዎቹ ድንቅ ግጥሞች ጀርባ ደግሞ ዓለም ፀሐይ አለች… ሙሉቀን በአብዛኛው የእሷን ግጥሞች ሲጫወት ነው የኖረው… “ሌቦ ነይ” ከሚለው የመጀመሪያ የካሴት ስራው ጀምሮ ዘፈን እስካቆመበት ጊዜ ድረስ የዓለም ፀሐይን ግጥሞች አዚሟቸዋል… ባጋጣሚ ሙሉቀንን ብታገኘውና “እንትን የሚለው ዘፈንህ ግጥሙን ማን ነው የጻፈው?” ብትለው ድንገት የሰጠውን ገጣሚ ቢዘነጋው አልያም በጊዜያዊነት ግር ቢለው በርግጠኝነት “ያው ዓለም ፀሐይ ትሆናለች” ብሎ ነው የሚመልስልህ….

ሙሉቀን እጅግ ውብ የሆኑ ዘመን ተሻጋሪ ስራዎቹን ለኢትዮጵያ ሙዚቃ አበርክቶ ዓለማዊውን ዘፈን የተሰናበተና መንፈሳዊውን ዓለም የተቀላቀለ ብርቅዬ አርቲስት ነው… የቋንቋው ውበት… የአዘፋፈኑ ለዛ… የሚጫወታቸው ግጥሞችና ዜማዎች… ቅንብሮቹ… ብቻ በሁሉም የተዋጣለትና የተለየ ቦታ መቀመጥ የቻለ ድምጻዊ ነው… ዓለም ፀሐይ ራሷ ምንም እንኳ ስራዎቿን የተጫወቱላትን ዘፋኞች በሙሉ እንደየመልካቸው ብትወዳቸውም… ብታከብራቸውም… ብታደንቃቸውም… ለሙሉቀን ያላት ስሜት ግን ይለያል….

ሙሉቀን ቋንቋ አዋቂ ነው… ቋንቋን የማሳመር ተክኖ አለው… ዜማ መርማሪ ነው… አንድን ዘፈን የሚሰራው ብዙ ተጨንቆና ተጠቦ… ብዙ ዜማዎችን አጥንቶና መርምሮ… ብዙ ጊዜ ወስዶ… ከነፍሲያው ጋር አዋህዶ ነው… ጥድፍ ጥድፍ ያለ ጥናት አይወድም!… የተዋከበ ቀረጻም አይዋጥለትም!… ያልመሰለውን ቅንብር አይቀበለም!… በወቅቱ የነጋዴዎችን ተጽእኖ ተጋፍጦ ለጥበቡና ለስሜቱ ያደረ በሳል አርቲስት ነው!… በዚህም የኢትዮጵያ ሙዚቃ በቅንብር ረገድ እንዲያድግ የበኩሉን አስተዋጽኦ አድርጓል… እነ ሙላቱ አስታጥቄን የመሳሰሉ ሊቅ አቀናባሪዎች ስራዎቹን ተግተው እንዲያቀናብሩለት ድርሻውን ተወጥቷል… በክፍያም ረገድ በዘመኑ ለዘፋኞች የሚከፈለው ክፍያ ከፍ እንዲል ፈር የቀደደ ነው…

ዓለም ፀሐይን የሚያበሳጫት አንድ ችግር ግን ነበረበት… ግጥሞቿ ውስጥ የባህል፣ የህዝብ፣ አሊያም ገጣሚያቸው በውል የማይታወቁ ስንኞችን እያመጣ ይጨምራል… አንዳንድ ዘፈኖቹ ላይ ግማሹ ግጥም የሷ ይሆንና ግማሹ የሌላ ይሆናል… ይህን ስራውን አትወድለትም!… “እንደዚህ አታድርግ ግጥሞቹን እንዳሻሽላቸው ከፈለግክ እራሴው ላሻሽላቸው እንጂ የሌላን አምጥተህ ስራዎቼ ውስጥ አትጨምርብኝ!” ብትለውም እሱ ከወደደና ካመነበት ያደርገዋል… ካሴቱ ከወጣ በኋላ ለተወሰነ ጊዜ ከፊቷ ይሸሻል… “እስቲ ጥይቋት… ምን አለች?… ተቆጣች?…” እያለ ይጠይቃል… በኋላም ስራው ይቀጥላል… እንዲህ አይነቶቹን ዘፈኖች በሙሉ ልብ የኔ ናቸው ለማለት አትደፍርም… ይህ ግን ባንዳንዶቹ ስራዎቿ እንጂ በሁሉም ላይ አይደለም…

በአብዛኛው ሙዚቃ አፍቃሪ እጅግ የሚወደዱት እነ “ገላዬዋ”… “ሰውነቷ”… “ወይ እዳዬ”… “አልዘገየሽም ወይ”… “ቁመትሽ ሎጋ ነው”… “መውደዴን ወደድኩት”… “ቁረጥልኝ ሆዴ” እና ሌሎች በርካታ ስራዎቹ የሷ ግጥሞች ናቸው… ጥቂት ስንኞችን ልቆነጣጥርና ለዛሬ ላብቃ…

1) ♪♪ ገላዬዋ ♪♪

♪♪ ገላዬዋ ነይ ነይ
ገላዬዋ ነይ ነይ
ሰው በገላው ውበት ይናፈቅ የለም ወይ♪♪

♪♪ ያይን ሽፋሽቷን ቅንድቧን አድንቁ
ጣቷን አስተውሉ ስትተዋወቁ
ዓይኗን ተመልከቱት እኔው ፈቅጃለሁ
ከኔው ጋር እያለ ሲዋሽ ይዤዋለሁ ♪♪

♪♪ አንገቷን አድንቁ መቃ ነው ብላችሁ
አካባቢ ሲቃኝ ታገኙታላችሁ
ቁጣ ግልምጫውን እችላለሁ ያለ
ጡቷን ቢመለከት ከልካይ አንድም የለ ♪♪

♪♪ ጥርሷን አሳስቁት ዝምታን አያውቅም
ፈገግታ በሷ ዘንድ ብዙ አያስጨንቅም
ዳሌ አቀማመጡን እዩት ለናሙና
እግሯን አትንኩብኝ መምጫዋ ነውና♪♪

♪♪ ገላዬዋ ነይ ነይ
ገላዬዋ ነይ ነይ ♪♪

2) ♪♪ ቁመትሽ ሎጋ ነው ♪♪

♪♪ ቁመትሽ ሎጋ ነው ሰንደቅ ያሰቅላል
የሰላም የፍቅር ምልክት ያሳያል ♪♪

♪♪ አሸን ክታብ ድሪ አልቦ ለቋ* ቀርቶ
ሽመል ሰውንተሽ ይታያል አብርቶ
ድሪውን ጠልሰሙን ገላሽ ባያደርግም
የፍኝ እኩሌታ ውበትሽን አይነፍግም ♪♪

♪♪ ለምድና ጎፈሬ ምን ይሆነኝ ብለሽ
ጌጤ መድመቂያዬ እራስ ወርቄ አንቺ ነሽ
የኔ በትረ ሙሴ መጥፎሽን አልወድም
ጠምበለል ነሽ ሎጋ ይህንን አልክድም ♪♪

♪♪ ቁመትሽ ሎጋ ነው ሰንደቅ ያሰቅላል
የሰላም የፍቅር ምልክት ያሳያል ♪♪

3) ♪♪ መውደዴን ወደድኩት ♪♪

♪♪ አንቺን መሳይ ቆንጆ ለኔ የሰጠኝን
መውደዴን ወደድኩት ያንቺ ያረገኝን
የኔ ያረገሽን መውደዴን ወደድኩት
ሳስብ ሳሰላስል ቆየሁ ከወሰንኩት ♪♪

♪♪ ሃር ከመሰለው ከጸጉርሽ ጀምሮ
እንከን የሌለብሽ ውብ ነሽ በተፈጥሮ
ትኩስ የፈነዳው ጽጌሬዳ ከንፈር
እስኪ አፍ ያውጣና ውብትሽን ይናገር ♪♪

♪♪ የሐረር መንደሪን የመስከረም አደይ
የሞጆ ብርትኳን የነሐሴ እንጉዳይ
ከንፈርሽ እንጆሪ ቀይ ጽጌሬዳ
ወፍ ጭጭጭ ሳይል ማልዶ የፈነዳ ♪♪

♪♪ አንቺን መሳይ ቆንጆ ለኔ የሰጠኝን
መውደዴን ወደድኩት ያንቺ ያረገኝን
የኔ ያረገሽን መውደዴን ወደድኩት
ሳስብ ሳሰላስል ቆየሁ ከወሰንኩት ♪♪

. . . በመጨረሻም እስቲ እናንተም የምታውቁትን ስራዎቿን ጻፍ ጻፍ አድርጉልኝ… ከዓለም ፀሐይ ጋር ያወጋነው ብዙ ነው… በቀጣይ ደግሞ ከሌላ ብርቅዬ ድምጻዊ ጋር ይዣት እመለሳለሁ… ረጅም እድሜ ላንቺ ዓለም ፀሐይ… ሰላም ለሁላችን!!!

ክብር ለጥበበኞች!
አብዲ ሰዒድ
2005 E.C

 
Leave a comment

Posted by on May 21, 2013 in ስብጥርጥር

 

ወፍዬ በእኔ እይታ

ይህ ጽሁፍ በአበባየሁ መሰለ የተጻፈ ነው… ግጥሙ በገጣሚ ሙሉጌታ ተስፋዬ ስለተጻፈውና ድምጻዊ አበበ ተካ ጥሩ አድርጎ ስለተጫወተው ወፍዬ ዘፈን ይተነትናል… አንብቡትማ!… የምትሉትም ካለ አካፍሉን እስቲ ….

ወፍዬ በእኔ እይታ . . .  
(በአበባየሁ መሰለ (ዶ/ር) )

አብዲ እኔም እንዳንተ በወፍዬ የሰከርኩ የወፍዬ ዘካሪ ነኝ። ወፍዬን ስሰማ አንዲት ጠንካራ ሴት ያለማንም ድጋፍ ራሷን ችላ ኑሮ ቀልሳ ለመኖር የቻለች፤ ደጋፊ እንደሌላት አውቀው፤ ብቸኝነቷን አይተው ጉልበተኞች ያበሳቅሏት፤ በሽታ ላይ የጣሏት፤ ለልጁዋ ኖራ ለልጁዋ ያለፈችን እናት አይበታለሁ። ይህንን እይታዬን ከግጥሙ እየቆነጠርኩ ላስረዳ።

ወፍዬ …

♪♪ ጭራ ጭራ የምታድረው 
ጭራ ለቅማ የምታድረው
እንዲህ አስናቀችኝ 
ቀድማኝ ጎጆ ወጥታ ጎጆ አስተማረችኝ
ጎጆ አቤት ጎጆን ወፍዬ አስቀናችኝ . . .♪♪

እነዚህ ስንኞች የዚህች አናት ቀድማ ጎጆ መውጣቷ፤ ቀድማ ቤት፤ ኑሮ መመስረቷ፤ ለፍታ-ጥራ ግራ መኖሯ ያስቀናው (መልካም ቅናት)፤ የሷን ጥንካሬ ያስመኘው ልጇ የሚለውን ነው የሚነግሩን። ይህች እናት ግጥሙን ገጣሚው ሲጽፈው በሕይወት የለችም የሚል እሳቤ ይዤ ነው የተነሳሁት። ይህ ልጇ “ጎጆ” ብሎ የሚመስለው የምድሩንም የሰማዩንም ቤቷን ነው። ያንቺን ኑሮ በሰጠኝ ብሎ የሚመኘውም አንድም በምድር አንድም በሰማይ መሆኑን በተለያየ መልኩ እንመለከታለን። ይህንን ምኞቱንና ፍልስፍናውን በጥልቀት ከሚቀጥሉት ስንኞች መረዳት ይቻላል።

♪♪ምነው ባደረገኝ የሷ ጋሻ ጃግሬ
እንደምንም ብዬ እኔም ጥሬ ግሬ
ያገዳ ጎጆዬን ባቆምኳት ማግሬ . . . ♪♪

♪♪ አጉል በቃኝ ላይል አይን አይቶ ገምቶ
ወይ ሞልቶ ላይሰላ ጆሮ አይችሉ ሰምቶ
እንዴት ጎጆ ይቅር አርሶና ሸምቶ . . .♪♪

የሚቀጥሉት ስንኞች በተለይ የምድሩንና የሰማይን ኑሮ በሚያምር አገላለጽ ይሉታል።

♪♪ገመና ከታቹ የሳር ቤት ያማረሽ 
ሚስጥረ መለኮት ማነው ያስተማረሽ
ካፈር ክዳን ጎጆ መሬቱን ፈልፍሎ 
ከሰማይ ቤት እጣሽ ማን በሰጠኝ ከፍሎ♪♪

ምልከታዬን በተሻለ መንገድ ለማስረዳት ይረዳኝ ዘንድ በተለይ እነዚህን ስንኞች በቅርበት መመልከት ያስፈልጋል። ብዙዎቻችን እንደምናውቀው በተለይ በገጠር ቤቶች ከሳር ክዳን ነው የሚሰሩት–በተለምዶ “ጎጆ-ቤት”ብለን የምንጠራው ማለት ነው። “ገመና ከታቹን የሳር ቤት ያማረሽ” ሲል የ’ድሃ’ መቃብር አስከሬኑ በኩታና በሰኔል ይጠቀለልና ሳር ተጎዝዩዞበት ይቀበርና አፈር ከተመለሰበት በሃላ ሳር ይጎዘጉዝበታል። የ’ድሃ’ መቃብር ወለሉም ጣራውም ሳር ነው። ስለዚሀ ይህ ስንኝ ቢያንስ ሁለት ተምሳሌቶችን የያዘ ነው ማለት ይቻላል፡ አንደኛው-ምድራዊ ጎጆ ቤትን፤ ሌላኛው ግብአተ መሬትን ማለት ነው። በተለይ የገጣሚው ትኩረት፤ በእነዚህ ስንኞች ማለቴ ነው፤ የሰማዩ ኑሮ ላይ እንደሆነ የሚታየው የቤቷ አሰራር መለኮታዊ ይዘት እንዳለው ይገልጥና “ካፈር ክዳን ጎጆ መሬቱን ፈልፍሎ” “ከሰማይ ቤት እጣሽ ማን በሰጠኝ ከፍሎ” በማለት አንቺ በገባሽበት የአፈር ቤት ውስጥ እኔንም ማን ቢያስገባኝና እሰማይ ብንገናኝ የሚል አይነት አንድምታ ያስይዘዋል። 

እንዲያው ከላይ ብቻ ላነበበው ወፎች አፈር ጭረው ሰማይ ላይ የአፈር ቤት ይሰራሉ ብሎ እሱን ሊነግረን ነው ሊያሰኝ ይችላል። እርግጥ ነው የግጥሙ ተምሳሌት እሱን የተከተለ ነው፤ መዳረሻው ረቂቅ ይሁን እንጂ። የሚከተሉት ስንኞች ውስጥ ደግሞ የበለጠ የሰው ልጅ “ሩቅ ሃሳቢ ቅርብ አዳሪ” እንደሆነ (ብዙ እያሰበ ባጭሩ ሊቀጭ እንደሚችል) ልብ በሚነካ እንጉርጉሮ አይነት ለዛ ይነግሩናል።

♪♪ እኔን እኔን እኔን ይብላኝ
እኔን አይኔን እኔን ይብላኝ
የቀን ሰው ሌት አፈር
ልቤ ሩቅ አሳቢው ቅርብ አድሮ ሲደፈር
ምን ነበር ቢቆጨው ጎጆ አጥቶ ከማፈር . . . ♪♪

የሰውን ልጀ ላፍታ ታይቶ እንደሚጠፋ፤ ይህንንም ሃቅ “የቀን ሰው ሌት አፈር” “ልቤ ሩቅ አሳቢው ቅርብ አድሮ ሲደፈር” ብሎ ባዋቀራቸው ስንኞች እያዋዛ ከታሪኩ ጋር በውበት ይለውሰዋል። 

♪♪ ፈጣሪዋን አምና ያፏን ጥሬ ሰጥታ 
ለጭሮ አዳር ውሎ በዝማሬ ወጥታ
አዳኝ እንዴት ያጥቃት ፍርድና ዳኛ አጥታ . . . ♪♪

♪♪ አጣሁ ነጣሁ ብላ እንደሰው ባይከፋት 
ምፅዋት ባትለምን ተርፎን ባንደግፋት
ጎጆዋ ለቻላት ምን ነበር ባንገፋት . . .♪♪

እነዚህ ስንኞች አሁንም ከላይ ከላይ ላነበባቸው ገጣሚው ወፍ ጭጭጭ እያለች እየዘመረች ሳታርስ ሳታርም በፈጣሪዋ ተማምና ጭራ ልትበላ በጠዋት ወጥታ እረኛ ወይም ሰብል ጠባቂ አጠቃት የሚለን ይመስላል። እርግጥ ነው የግጥሙ አርዕስት “ወፍዬ” ነውና ተምሳሌቱ የወፍ ኑሮ ነው። ነገር ግን ጥቂት ጠለቅ ብለን ብንመለከት፤ ያቺ ከርታታ እናት በጠዋት “ፈጣሪዋን አምና ያፏን ጥሬ ሰጥታ” ይለናል። እሷ በፈጣሪዋ ተማምና ያፏን ጥሬ ሰጥታ–ጾማ–ያላትን ለልጅዋ አጉርሳ..ጭራ ልታድር እያመሰገነች ወጣች። ግና የወደቀ ዛፍ ምሳር ይበዛበታልና ለፍታ ባደረች፤ ጭራ በኖረች ጉልበተኞች አላኖር አሏት፤ ደበደቧት በሽተኛ አደረጓት። 

♪♪ ታማ ትንፋሽ አጥሯት ደክማ ስታጣጥር 
ማን ያቃናት ይሆን ውለታ ሳይቆጥር
ወልዶ ማሳደጉን ብዙ ሰው ቢያውቅበት
ያፉን ማን ይሰጣል የ’ጁ ሲርቅበት . . . ♪♪

ብቸኛ ናትና ደጋፊ የሌላትምና ታማ ስታጣጥር እንኳ ውለታ ሳይቆጥር ውሃ የሚያቀብላት አጣች። እንደዛ እየማቀቀች ወጥታ ጭራ ራሷንና ልጇን መመገብ ተሳናት። እጅ አጠራት፤ አጣች። ቢሆንም ግን እሷ ትራብ እንጂ ልጇን ታጎርሳላች። ይህንን የእናትነትና የመሷዕት ውድነት በመጨረሻዎቹ ሁለት ስንኞች ሙሉጌታ ልብ በሚነካ አይነት ይገልጠዋል። ልብ እንበል አሁንም ስለወፍ አኑኗር ነው የሚነግረን። ወፍ ደግሞ በአፏ ነው የመትበላው በአፏ ነው የምታበላው። “ወልዶ ማሳደጉን ብዙ ሰው ቢያውቅበት” “ያፉን ማን ይሰጣል የ’ጁ ሲርቅበት . . .” ይለናል። ያቺ እናት እጅ አጥሯታል፤ አጥታለች፤ እጇን ዘርግታ መስጠት አልቻለችም፤ የእጇ ራቀባት፤ ከየት ታምጣ? የእጄ ራቀ ብላ ግን ልጇን አላስራበችም። የምትቆርሰው ብታጣ ራሷ ልትጎርሰው ያዘጋጀችውን ካፏ ላይ ወስዳ ልጇን ታበላለች። 

ታዲያ…ማን አለ እንደ ወፍዬ? ይህስ ልጅ አማዬ እዚህ አልተመቸኝም እዚያው ከሰማይቤት እጣሽ ማን በሰጠኝ ከፍሎ ቢል እናቱ ለሱ ምን እንደሆነች ማን ይረዳል? ወፍዬ ድንቅ እናት!

♪♪ ወልዶ ማሳደጉን ብዙ ሰው ቢያውቅበት
ያፉን ማን ይሰጣል የ’ጁ ሲርቅበት . . .???♪♪

ሙሉጌታ ተስፋዬ ተባረክ!

እንግዲህ ይህ የኔ እይታ ነው…እናንተስ ምን ትላላችሁ?

 

Image

 

 
Leave a comment

Posted by on May 18, 2013 in ስብጥርጥር