RSS

Category Archives: ስብጥርጥር

. . . / የግራ ገቡ ደብዳቤ / . . .

ይህ ጽሁፍ አንድ ግራ-ገብ ግለሰብ የጻፈው ነው… ብዙ ነገሮች ግራ ግብት ቢሉት ግራ በተጋባች መጣፊያው ግራ ገብ ጥያቄዎችን ሊያነሳ ወደደ!…

እናንት የገባችሁ ተመራማሪዎች!… እናንት ያልገባችሁ ተደናቋሪዎች!… እናንት ግራ የገባችሁ ተደናባሪዎች ሆይ!…. በየትኛውም አቅጣጫ ቀፍድዶ ከያዘን ጽንፍ አሳብ ነጻ ሁናችሁ የግራ ገቡን አሳብ በመልካምነት ትመለከቱ ዘንድ… ጥያቄዎቹንም በቀናነት ለመመለስ ትሞክሩ ዘንድ ትለመናላችሁ… መመለስ ፈቃዳችሁ ባይሆን እንኳ ለራሳችሁ ብታብሰለስሉት ግራ ገብነትን እንደመጋራት ይቆጠራል….

ልብ በሉ!… ይህ ግለሰብ ግራ የተጋባው የሚያስበው አጥቶ አይደለም!…. የሚጸናበት አቋም የሌለው ዋዣቂ ስለሆነም አይደለም!… ነገሮች የሚደባለለቁበት ቀዥባራ ሆኖም አይደለም!…. ይልቁኑስ ከዚህምም ከዚያም የሚወራወሩትን ቅጥ የለሽ ዘለፋዎችና ውል የለሽ መናቆሮችን አጥርቶ ማወቅ ስለፈለገ እንጂ!… ከመደናቆር መመካከር በሚል መንፈስ ስለተነሳሳ እንጂ!…

ይህን ግራ ገብ ግለሰብ ሃይማኖቱን አትጠይቁት!…. ማንን እንደሚያመልክ አትመርምሩት!…. ከየት እንደመጣ ለማወቅም አትጣሩ!… ዘር ማንዘሩንም ለመቁጠር አትድከሙ!… “እንዲህ የሚያስበው የእንትን ፓርቲ አባል ስለሆነ ነው!… የነእንትና ደጋፊ ስለሆነ ነው!…. እነ እንትናን ስለሚጠላ ነው!”… ምናምን ብላችሁ በራሳችሁ መነጽር ለማየትም አትልፉ!… በመላ ምት ለመደምደምም አትጣደፉ!…

ይህ ሁሉ ኮተት አሳቡን ለመረዳትም ሆነ ጥያቄዎቹን ለመመለስ አያስፈልግም!… ግራ ገብነቱን ቢያባብሱት እንጂ አይቀንሱትምና!…. እናም ዝምምምም ብላችሁ ብቻ ግራ መጋባቱን ተረዱለት!… በቀናነት ሰው የመሆን መንፈስ ብቻ ተሞልታችሁ ጥያቄዎቹን መልሱለት… ልትመልሱ ካልቻላችሁም በባዶ ከመዘባረቅ ዝምታ ወርቅ ነው።

ጥያቄዎቹም ሆነ አሳቦቹ በሰሞኑ ከተነሳው የአቡነ ጴጥሮስ ሐውልት እና ከባቡር መንገድ ዝርጋታው ጋር ይያያዛሉ . . .

ከሐውልቱ መነሳት ጋር ተያይዘው ለተፈጠሩት መነታረኮች… መበጣበጦች… እና ግራ መጋባቶች ዋናው ተጠያቂ መንግስት እንደሆነ ግራ ገቡ ያምናል። ጥርት ያለ መረጃ ቀድሞውኑ በአግባቡ ተዳርሶ ቢሆን… አስፈላጊው ውይይት ከሕብረተሰቡ ጋር ተደርጎ ቢሆን… ቀደም ብሎ ባሳለፈው ታሪክ መንግስት ለታሪክና ለቅርስ ተቆርቋሪነቱን በጽናት አስመስክሮ ቢሆን… ይህ ሁሉ ያለመተማመን… ይህ ሁሉ መደበላለቅ… ይህ ሁሉ መቀበዣዠር ላይኖር ይችላል… በዚያ በኩል ብዙ ነገሮች እያጠፋ እያየን በዚህ በኩል ብዙ ነገሮች ሲያለማ ስናይ አናምንህም ብንለው አይፈረድብንም።

የምንግስት ችግሮች ዘርፈ ብዙ ናቸው… የመንግስት መልካም ስራዎችንም በብዛት እያየን ነው… እነዚህ ሁሉም በየመልካቸው ራሳቸውን የቻሉ መወያያ ጉዳዮች ናቸውና እዚህ አናደበላልቃቸውም።

ይሄ ጉዳይ ሐውልቱን ብቻ ስለሚመለከት እንጂ ሽሽት አይደለም!… አንዱን ችግር ከሌላው መልካም ስራ ጋር ማደባለቁ ግራ ከማጋባት የዘለለ ፋይዳ አይኖረውም!… እዚህ ላይ ግራ ገቡ የሚፈልገው ሙያ ነክ መልሶችን… የጋራ ጥቅምን የተመለከቱ ውይይቶችን እንጂ ከንቱ መደናቆርን አይደለም።

* * *
አቡነ ጴጥሮስ ጳጳስ ነበሩ!… ብጹዕ አቡን ነበሩ!… ሐይማኖታዊ አባት ነበሩ!… ከነዚህም ጋር ተያይዞ የሚኖራቸው ሃይማኖታዊ ስልጣን ወይም ታላቅ የሆነ መለኮታዊ ቦታ ሊኖር ይችላል… ያ!… ሃይማኖታዊ ስለሆነ እዚህ ጋር አናመጣውም። ያ!… እምነቱ ለሚመለከታቸው ሰዎች ብቻ የሚያገለግል እንጂ የመላው ሕዝብ እውነታ አይደለምና ለዚህ ጉዳይ አያስፈልገንም።

አቡነ ጴጥሮስ የነጻነት ታጋይ ነበሩ!… አርበኛ ነበሩ!… ላመኑበት ሕይወታቸውን የገበሩ ባለውለታ ነበሩ!… የኢትዮጵያችን የቁርጥ ቀን ሰው ነበሩ!… የትግል አርማ ነበሩ!… ስንቱ ባንዳ አገሩን ሲሸጥ በአላማቸው ጸንተው ለበርካታ ታጋዮች አርአያ መሆን የቻሉ ታላቅ ሰው ነበሩ!…

“እምቢኝ አልገዛም!… እኔን እንደ አባት አምነው ለሚከተሉኝ ሕዝቦቼ የውድቀት ምሳሌ አልሆንም!” በማለታቸው ነው በግፍ የተገደሉት… ይህ ታሪካቸው ነው ሐውልት እንዲቆምላቸው ያደረገው…. በዚህ አኩሪ ታሪካቸው ማንም ነጻ ኢትዮጵያዊ እንዲያከብራቸው ይገደዳል!…. እዚህ ላይ ብቻ ነው ማተኮር የሚገባን… ለምንሰጠው ማንኛውም አስተያየት ከዚህ እይታ መውጣት ያለብን አይመስለኝም…. ሃይማኖትንና ታሪክን ማደበላለቅ እውነትን ከማጨመላለቅ የዘለለ ፋይዳ አይኖረውምና።

የኚህን ታላቅ ሰው መታሰቢያ ሐውልት እንደማንም ተራ እቃ አንስቶ መጣል ይገባል… መንገድ እንጂ በመንገዱ ላይ በነጻነት እንድንራመድ ያደረጉን ባለታሪኮች ዋጋ የላቸውም…. ብሎ የሚከራከር ቢኖር አሳቡን ይመርምር!… ምልከታውን ይፈትሽ!….

በሌላም በኩል ደግሞ ጉዳዩን ከጽድቅ ጋር አያይዞ የእምነቱ ማራመጃ… የሃይማኖቱ ማካሄጃ… ከፈጣሪው ጋር መማለጃ… የሚያደርግ ስለ ሐውልቱ በተነሳ ቁጥር የማምለክ ያህል የሚጠበብ ቢኖር!…. እርሱም አሳቡን ይፈትሽ…. ምልከታውን ይመርምር….

እንዲሁም መንግስትን እንቃወማለንና…. አስተዳደሩን አንደግፍምና…. በዚህ ታሪካዊም ሐይማኖታዊም መልክ ባለው ሐውልት ተመርኩዘን ተቋውሟችንን እናራግብ… ብለው የሚንቀሳቀሱ ቢኖሩ አገርንና መንግስትን…. ወይም ፓርቲንና እድገትን ይለዩ!…. ራሳቸውንም ይፈትሹ!…. አሳባቸውንም ይመርምሩ!….

. . . ለእኛ ታሪኩም የሃዲድ ዝርጋታውም ያስፈልጉናል . . .

ታሪክ ብቻውን ዳቦ ሆኖ አይበላም!… የጦር ጀብደኝነት ብቻውን ርሃብና እርዛት ላይ ጀብደኛ ለመሆን አያስችልም!… ሃይማኖታዊ አምልኮ ብቻውን የእድገትና የስልጣኔን መና ከሰማይ አያወርድም!… ከጠኔ ለመውጣት ዋናው ጀብዱ ስራ መስራት ነው!…. ከጨለማ አስተሳሰብ ራስን አላቆ ዝም ብሎ መትጋት!… የተስፋ ብርሃን ተሞልቶ… ከጎጠኝነትን ተፋቶ… በጋራ መልፋት!…. ተግቶ የሰራ… በሕብረት የጣረ ሕዝብ የልፋቱን… የጥረቱን ዋጋ እንደሚያገኝ ግራ ገቡ ልቤ ያምናል።

የዛሬ መንገድና ህንጻ ብቻቸውን ቢገነቡ የድሮ ማንነታችንን እየናዱ ታሪክን እያጠፉ ሲሆንም ማደግ አይባልም!…. ማንነቱን የማያውቅ… ታሪኩን የዘነጋ… ባለውላታዎቹ ላይ የተኛ ትውልድ ለታናናሾቹ የሚያወርሰው ማንነት አይኖረውም…. ቢኖረውም የተበጫጨቀ እንጂ ሙሉ አይሆንምና!…. የአገር ማንነት ከትውልድ ትውልድ እየተቀጣጠለ የሚሰራ ብርቱ ሰንሰለት እንጂ በአንድ ቦታ ተወስኖ የሚኖር ግኡዝ የአደራ እቃ አይደለም። እናም ሁላችንም የመቀጣጠል ሃላፊነት አለብን!….

ነገር ግን ታሪክን እንዴት ነው የምናቆየው?…. በምን መልኩ ነው ከትውልድ ትውልድ የሚተላለፍ ህያው የምናደርገው?… ብሎ መጠየቁና መመካከሩ የሚያስፈልግ ይመስለኛል…

ጥንት አያቶቻችን ወይም አባቶቻችን ታሪክን የሚያቆዩበት መንገድና እኛ የምናቆይበት መንገድ ይለያያል… ነገ የሚመጣው ትውልድ ደግሞ በሌላ መንገድ ሊያቆያቸው ይችላል…. ዘመን ሲለዋወጥ ከዘመን ጋር የሚለወጥ… ከትውልድ አስተሳሰብ ጋር አብሮ የሚዘምን ታሪክን የምናቆይበት መንገድ ከሌለን ወይም እንዲኖረን ካልተጋን እንዲሁ እንደተጯጯህን ብዙ ነገሮች እናጣለን… ብዙ ታሪኮችም ይባክናሉ።

“በበኩሌ የሃዲድ ዝርጋታውን አልቃወምም!… ከተማችን ባቡር ቢኖራት አልጠላም!… እድገትን ማን ይጣላል?… ግን ለምን ሐውልቱን እንዳይነካ አልተደረገም?… ካልጠፋ መንገድ በሐውልቱ ላይ ማስኬድ ምን ይባላል?!… ታሪክን ማጥፋት እንጂ!…”

የሚሉና መሰል ጥያቄዎች በተደጋጋሚ ይጠየቃሉ… ምንም አይነት ድምዳሜ ላይ ባልደርስም ጥያቄዎቹን እጋራቸዋለሁ… ለምን በዚያ መንገድ አለፈ?… ወይም ለምን እንዳይነካው አልሆነም?… ለሚለው ጥያቄ ግን ሙያዊ ምላሽ ያስፈልጋል…

በበኩሌ ለመንገድ ዝርጋታም ሆነ ለባቡር መስመር ዝርጋታ ሙያ መሃይም ነኝ። ቅንጣት የሆነች የዲዛይኒንግ ወይም መሰል እውቀትም የለኝም!… ግን ሙያው እጅግ ጥንቃቄ የሚፈልግ እንደሆነ ይሰማኛል!… እናም “ይቻላል!… አይቻልም!” ማለት አይቻለኝም። በዚህ አጋጣሚ ይህችን ጥሁፍ ድንገት የሚያነባት የዘርፉ ባለሙያ ቢኖርና ከየትኛውም ጽንፍ ነጻ ሆኖ ወይም ሆና ሙያዊ ማብራሪያ መስጠት ቢቻል ግራ ገብነትን መታደግ ብቻ ሳይሆን ለከተማችን እድገትም አስተዋጽኦ ማድረግም ነው. . .

ለመሆኑ መንገድ እንዴት ነው የሚቀየሰው?… የባቡር ሃዲድስ እንዴት ነው የሚዘረጋው?… የከተማ ፕላንስ እንዴት ነው የሚሰራው?… ለዘመናት የኖረች ከተማ ስትታደስስስ እንዴት ነው መታደስ ያለባት?… እኚህ ሁሉ የባለሙያን መልስ የሚሹ ጥያቄዎች እንጂ እንዲሁ በዘፈቀደ የሚዘባረቅባቸው ጉዳዮች አይመስሉኝም….

እስከዚያው ግን የሚመላለሱብኝን ጥያቄዎች እጠይቃለሁ…. የማያውቁትን መጠየቅ እውቀትን ከማስጨበጡም በላይ ከንቱ መደናቆርን ይቀንሳል…. እናም ጥያቄዎቹን ብቻ ትመልሱ ዘንድ በድጋሚ ትለመናላችሁ…

. . . 1 . . . ሐውልቱን እንዳይነካው ስንል እንዲቀየስ የምንፈልገው መንገድ የሌላውን መስመር ዝርጋታም የሚያጣምመው ቢሆንስ?

. . . 2 . . . ሐውልቱን እንዳይነካና በሌላ መስመር እንዲዘረጋ ስንፈልግ ፒያሳ የባቡር ሲሳይ እንዳታገኝ የሚያደርጋት ቢሆንስ?

. . . 3 . . . ሐውልቱን እንዳይነካ ስንል የምንከልሰው ፕላን የአዲስ አበባን ከተማ ማስተር ፕላን የሚረብሸው ቢሆንስ?

. . . 4 . . . የአቡነ ጴጥሮስ ሐውልት የቆመበት ቦታ እዛች ቦታ ላይ በግፈኛው የጣልያን ጦር መሪ ትእዛዝ እንዲረሸኑ ስለተደረገ እንጂ ከአዲስ አበባ ከተማ ማስተር ፕላን አንጻር ሲታይ ቦታው የመንገድ እንጂ የሐውልት ማቆሚያ ባይሆንስ?… መንገዱ ይቅርብን ሐውልቱ ይኑልን ልንል ነው?…

. . . 5. ሐውልቱ ለዝርጋታው ተነሳ እንጂ አልፈረሰም አይደል?… አያስፈልግም ተብሎ አልተጣለም አይደል?… እና ምንድነው ችግሩ?… ከዝርጋታው በኋላ መልሶ መትከል እንደማይቻል የሚገልጽ መረጃ አለ?… በመሃል ለተነሳበት ጊዜ ከሆነ መልሶ ሲተከል ለምን ተነስቶ እንደነበረ መጻፍ አይቻልም?….

ደግሞስ ለምንድነው ተመልሶ አይተከልም ብለን ገና ሳይደርስ የምንደመድመው?… በመንግስት ላይ ያለን እምነት በመውረዱ ከሆነ አንድ ነገር ነው… አይ የለም “አይቻልም!” ተብሎ ታስቦ ከሆነ ግን አልስማማም… የተባለው ዝርጋታ በትክክል የሚከወን ከሆነ ምንም የሚከብድ አይመስለኝም!… ምንም እንኳ የዘርፉ ባለሙያ ባልሆን ባጋጣሚ ያየኋቸው ከተሞች ከአንድም ሁለት ሦስት ደረጃ የወረደ የምድር ለምድር ባቡር ከስራቸው እየተምዘገዘገ ላያቸው የደራ ከተማ ነው… አይደለም አንድ መታሰቢያ ሃውልት መመለስ ቀርቶ ከስር ባቡር እየሄደ ከላይ ሕንጻ መገንባት ይቻላል… ያ ስልጣኔ ብርቃችን ቢሆንም!… ስናሳዝን!… 😦 …

እነዚህን ጥያቄዎች የምጠይቀው ግራ ገብነቴን ለማጥራት እንጂ ለሌላ አይደለም.!… እስካሁን ባጋጣሚ የምጠይቀው ሁላ “ይቻላል ለምን አይቻልም!… ክፋት እንጂ!” እያለ ከመፎከር የዘለለ ሙያዊ ማብራሪያ የሰጠኝ አልገጠመኝም…

በቻይና የሆነ መንገድ መሃል አስፓልት ላይ በካሳ ክፍያ አለመስማማት ምክኒያት የተደነቀረ የአረጋዊያንን ቤት… የሆነ በረሃ መሃል ያለች ዛፍን እንዳይነካ የተጣመመን መንገድ…. እና መሰል ምስሎችን ከማሳየት በዘለለ “ይሄ እንደዚህ ነው… መንገድ ሲሰራ እንዲህ ነው!… የባቡር ሃዲድ ሲዘረጋ እንዲህ ነው!…. የአዲስ አበባ ፕላን እንዲህ ነው!… ስለዚህ በዚህ በኩል ቢያልፍ ጥሩ አማራጭ ነበር…” የሚል እውቀትን መሰረት ያደረገ… ማደግን መበልጸግን ከመመኘትና አብሮም ታሪክን ከማቆየት ጋር ያለውን ፋይዳ የሚገልጽ ሰው አልገጠመኝም… እንዲህ ያለ ጽሁፍም አላየሁም!…. ያጋጣምችሁ ካላችሁ ብታካፍሉኝ እጅጉን አመሰግናለሁ . . .

በበኩሌ ይህንን ጉዳይ አበክሬ የማነሳው ከሃይማኖትም ከፖለቲካም አንጻር አይደለም!… ይልቁንም አዲስ አበባዬን ከአንድም ሁለት ሦስቴ ከላይ ወደታች ቁልቁል ሳያት የተሰማኝን የተደበላለቀ ስሜት እያስታወስኩ እንጂ…

ብዙ ነገሯ የተዘበራረቀ!… መንገዷ የተጣመመና የተሽሎከለከ… ህንጻዎቿ አንድ አካባቢ በስርአት ሌላ አካባቢ ደግሞ ያለ ስርአት እዚም እዛም የተተከሉባት… ያን ተከትለው ለዛ የሌላቸው መብራቶች አንድ ቦታ እንደ ችቦ የሚደምቁባት… ሌላ ቦታ እንደ ኩራዝ ጭል ጭል ጭል የሚሉባት… የመኪናውና የእግረኛው መንገድ የማይታወቅባት… የአታክልቱ ስፍራና መኖሪያ ቤቱ የማይለይባት… የልጆች መጫወቻውና የኳስ ሜዳው የማይታወቅባት… ዝም ብላ በዘፈቀደ የምትወናበድ… ዝም ብላ በዘፈቀደ የምትወላገድ ከተማ ሆና ስላገኘኋት ነው።

… የምር ታስጠላለች!… ማስጠላት ብቻ ሳይሆን የከተማ መልክ ስለሌላት ትጨንቃለች!… ለካ ከከፍታ ነው መልክ የሚታይ!… ለካ ከሰማይ ነው ውበት የሚለይ!… ውይይይ አዲስ አበባዬ…

ከሌሎች ከተሞች የሰማይ መልክ ጋር ለማነጻጸር የሚቃጣው የኔ ቢጤ ጀዝባ ካለ ደግሞ ይታመማል!…. በበኩሌ ባጋጣሚ ካየኋቸው ከስቶክሆልም… ከሮም… ከአምስተስተርዳም… ከለንደን ጋር ላመሳስላት ሲቃጣኝ በጅልነቴ እስቃለሁ!… የምር ሰው ብቻ ሳይሆን ከተማም መልክ ያስፈልጋታል…. ታሪኳን ብቻ ሳይሆን… እድገቷን ብቻ ሳይሆን… ዉበቷንም ታሳቢ ያደረገ ውይይት… ውበቷንም ታሳቢ ያደረገ ግንባታ ሊደረግ ይገባል….

አዲስ አበባችን እንዲህ ለዛ ያጣችው… እንደዚህ መልከ ቢስ የሆነችው…. መንገዶችና ህንጻዎች “እንትንን እንዳይነኩ” እየተባለ ሲዘለሉና ተለዋጭ ሲሰራላቸው ስለኖረ እንጂ የከተማዋ ማስተር ፕላን ለዛ ቢስ ሆኖ አይመስለኝም!…. እና እዚህ ጋርም የምንለውጠው የበለጠ የሚያበላሻት ቢሆንስ?… ይህ ሁሉ እንግዲህ የማላውቃቸው ጥያቄዎች ናቸው… በባለሙያ የሚመለሱ!…

በመጨረሻም ታሪክን ለትውልድ ማቆየት የሚቻለው ዘላቂ መፍትሔ የሚያመጣና የዘመን ስልጣኔን መሰረት ያደረገ ውይይት በጋራ ሲካሄድ እንጂ አንድ ጽንፍ ላይ ተንጠልጥሎ ደሞ ከኔ ወዲያ ላገር አሳቢ ብሎ በመፎከር አይደለም እናም ጽንፋችሁን ተዉትና ኑ ስለጋራ ጥቅማችን በጋራ እንነጋገር . . .

ሰላም !
One Love !
_______ // አብዲ ሰዒድ // ________

 

Image

 
 

ትንሽ ማስታወሻ . . .

ቀደም ብሎ ኃይለ ማርያም ይሰኙ የነበሩት በኋላም ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ የተባሉትና በኢትዮጵያ የሰላሌና የዎሎ ጳጳስ የነበሩት የነጻነት ታጋይ አባት ላመኑበትና ለቆረጡበት አላማቸው ሕይወታቸውን የሰዉበትን የጀብዱ ታሪክ ለመዘከር ብሎም በነዚያ አምስት ዓመታት (በኢትዮጵያ አቆጣጠር ከ1928-1933) የጣልያን ቆይታ ኢትዮጵያችን ያለፈችበትን ውጥንቅጥ… የባንዳና ያገር ወዳድ ምጥ… የሻጭና ያሻሻጭ እሽቅብጥብጥ… የሃቀኛና የእውነተኛን መንጓጠጥ… ከ5 ዓመት የግዞት ኑሮ መልስ በኃላ የነበረውን የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መልመጥመጥና መቁረጥረጥ… ብሎም ብዙ መሰል ታሪኮችን ሲያስታውሰን የኖረው የአቡነ ጴጥሮስ መታሰቢያ ሐውልት ተነሳ… (ፈረሰ አላልኩም!… መነሳትና መፍረስ በጣም የተለያዩ ናቸው።)

እናም ትንሽ ምልልስ ከጸጋዬ ገብረ መድህኅን “ጴጥሮስ ያቺን ሰዓት” ከተሰኘ ተውኔት ላይ ብንቆነጣጥርስ… ይህ ምልልስ በእስር ላይ የሚገኙት አቡነ ጴጥሮስና ለጣሊያን አድሮ እጃቸውን እንዲሰጡ የሚያግባባቸው ግርሻ የሚያደርጉት ነው።

ልብ በሉ እኔ እንደመሰጠኝ ቆነጣጠርኩት እንጂ ምልልሱ ሙሉ አይደለም… እናም ሙሉ ታሪኩን ትረዱት ዘንድ ”ጴጥሮስ ያቺን” ሰዓት የተሰኘውን ተውኔት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ በኢትዮጵያ አቆጣጠር በ2003 ከታተመው የጸጋዬ ገብረ መድኅን ታሪካዊ ተውኔቶች መጽሐፍ ላይ እንድታነቡ ይመከራል።

ኃይሉ:
. . . ስለዚህ ልጄ ካንተም ሆነ ያገር አዛውንት ካልካቸው ጋር ያው እንደግራዚያኒ መቸጋገር እንጂ መመካከር አይኖረንምና ፍቃድህ ሆኖ የመጨረሻ ሰዓቴን በግል እንዳሳልፋት ለጊዜው ብቻዬን ተወኝ።

ግርሻ:
አባቲላ ለምን ቸኰሉ? ገና ለዘለዓለሙ ዓለም ብቻዎን ይሆኑ የለም?

ኃይሉ:
እሱንም ቢሆን እናንተ ወስናችሁልኝ ሳይሆን እኔ መርጨ ነው ልጄ።

ግርሻ:
ለርስዎ እንጂ ለሌላውማ እንዳይመርጡ አቅም የለዎትም።

ኃይሉ:
ለራሱ ለመምረጥ አቅም ያጣ እንኳን ተስፋ የተስፋ ጭላንጭል አይኖረውም። መሳሪያነቱ እንኳን ጭለማ እንጂ ብርሃንነት የማይኖረው፣ ጨዋ ወገኑን እንስሳ በማስደረግና፣ የተስፋቸው ጮራ ፍንጣቂ መሆኑ ቀርቶ፣ የተስፋቸው አሽቃባጭ ጥንብ-አንሳነት ብቻ ነው እሚተርፈው።

ግርሻ:
እኔስ በጄ፣ ለኔስ በጄ እንደምንም፣ እንደማናቸውም ለራሴ ልኑርለት፣ ከሞት ማዶ ያለ ተሥፋ የራዕይ ወይም የባለመለኰት ጠባይ ነውና ራሴን አላመጻድቅም።

ኃይሉ:
ትህትናህ ከግብዝነት እንጂ ከመንፈሣዊነት እንዳልፈለቀ ላንተ እንደሚታወቅህ እኔንም ያጠራጥረኛል። ይሁንና ከሞት ማዶ ያለ ተስፋ የራዕይነት ብቻ ሳይሆን የህይወትነትም፣ የሥጋዊነትም ጠባይ አለው ልጄ፣ ድፍን በድፍን እንቁላል ካልተፈረከሰ በዉስጡ ያለው አዲስ ህይወት ብር ትር ብሎ አይበርም። የስንዴ ፍሬ ወድቃ ካልበሰበሰች በቀር አታፈራም፣ አትበዛም። መውደቅና መሞት የሚያስተላልፈውን፣ የሚያፈራውን የተሥፋ አይነት መች አጣኸው?
የንፍገትና የስስት ኑሮህን እምታባብልበት ዘዴ፣ የምታሸንፍበት ልቦና አጥሮብህ ነው እንጂ።

ግርሻ:
ሞትማ ተሥፋ ከሆነ፣ ስንቱ ሽፍታ ሞቶ የለ፤
ተሥፋ ያለ በመግባባት ነው፣ በሕይወት ነው ተሥፋ ያለ።

ኃይሉ:
ያንተ ብጤው ሕይወት ለሕዝብ ተሥፋ የሞትነት መሣሪያ ነው።
የነሱ ብጤው ሞት ለሕዝቡ ተሥፋ የሕይወትነት መሣሪያ ነው።
ባላንጣን በተሥፋና በጦር መሣሪያነት እንጂ በልምምጥ፣ በእምባ ያሸነፈ የለም።

ግርሻ:
አቅም ያጣ ቢለማመጥ ተግባባ፣ ተመካከረ ነው እንጂ ባነባ ተለማመጠ አይደለም እሚባል። መግባባት የደከመ ወገን ውል ነው።

ኃይሉ:
ባሪያን በፈንጋዩ መሃል ደፍቶ መግዛትና መገዛት እንጂ ሌላ ምን ውል ሊኖር?

ግርሻ:
ትርጉም ሁሉ እንየአስተያየቱ ነው እሚራባ አባቴ። በቃል ኪዳንና በውል የሠፈረ ፊርማ ግን በሕግ የጸደቀ የተረጋገጠ የእውነት ፍሬ ነው።

ኃይሉ:
የተረጋገጠ የእውነት ፍሬ ቃል-ኪዳን? የማን እውነት? የማን ቃል-ኪዳን? ያንተ እውነት? ወይስ የኔ እውነት?

ግርሻ:
የጋራችን እውነት። የውላችን እውነት።

ኃይሉ:
ጠፊ ካጥፊው ከተዋዋለ መጥፊያውን አፀደቀ እንጂ ተዋዋለ አይባልም።

.
.
.

/ጥሩምባ/

. . . አቡነ ጴጥሮስ የተባሉት፣ በገናናው የኢጣሊያ መንግሥት ላይ ስለሸፈቱ፣ በሞት ይቀጣሉና ነገ ጠዋት ባምስት ሰዓት፣ አራዳ ጊዮርጊስ ቤተስኪያን አጠገብ እንትሰበሰቡ ተብላችኋል። . . .

.
.
.
/ጥሩምባ/
. . . አቡነ ጴጥሮስ የተባሉት፣ . . .
.
.
.

ምንጭ:
ታሪካዊ ተውኔቶች፣ ጸጋዬ ገብረ መድኅን
አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ፣ 2003 E.C

Image

 
 

ያገለገሉ ፓንቶች ሽቀላ . . .

እዚህ እኔ ያለሁበት አገር አገልግሎት የሰጡና የተጣሉ ፓንቶች ይነገዳሉ!… ይሸጣሉ!… ይለወጣሉ!… ገንዘብ ያመጣሉ!… ቀልድ እንዳይመስላችሁ የምር ነው!… ንግድ ፈቃድ ማውጣት ሳያስፈልገው… ግብር እንዲከፍል ሳይገደድበት… የስራ ቦታ ማደራጀት ግድ ሳይለው በቀላሉ ገንዘብ ማግኘት የፈለገ የትኛውም ግለሰብ ያለማንም ከልካይ ወደ ፓንት ሽቀላ ስራ ሊሰማራ ይችላል… 

ለዚህ ስራ የሚያስፈልገው ነገር ቢኖር ቆራጥነት ብቻ ነው!… በየጎዳናው የሚገኙ የሕዝብ ቆሻሻ መጣያ ሳጥኖችን እየከፈቱ ፓንት ለመፈልግ የሚያስችል ቆራጥነት… ከየቆሻሻ ዉስጥ የሰበሰቧቸውን ፓንቶች በፌስታል፣ በቦርሳ አልያም ባመቸ ነገር ቋጠር አድርጎ ለመንቀሳቀስ የሚያስችል ቆራጥነት… በየገበያ ማዕከሉ በተተከሉ የፓንት መግዣ ማሽኖች ፓንቶቹን አንድ በአንድ እየደመሩ ለመክተትና ደረሰኝ ለመቀበል የሚያስችል ቆራጥነት… ምናልባት ማሽን የተፋቸውና ቃርዳ የወጡ ፓንቶች ቢኖሩ አሊያም ፓንት ሳይሆኑ ከፓንት ጋር ተደባልቀው የተሰበሰቡ ቢያጋጥሙ እነሱን በአግባቡ ወደቆሻሻ ማስወገጃ ሳጥኖች ለመጣል የሚያስችል ቆራጥነት… 

እንግዲህ ይህ ቆራጥነት ያለው ማንኛውም ሰው ዛሬዉኑ የፓንት ስራን መጀመርና ሽቀላውን ማጧጧፍ ምርጫው ነው… ለበለጠ ውጤታማነት በሳይክል አሊያም መሰል ተሽከርካሪ መንቀሳቀስ ይመከራል… የበዙ የቆሻሻ መጣያ ሳጥኖችን ለማዳረስ ከማስቻሉም በላይ ፓንቶቹን በቀላሉ ለመያዝ ያመቻልና … 

“አበስኩ ገበርኩ ጌታዬ!… ምኑን ታሰማኛለህ!”… “የተጣሉ ፓንቶች ንግድ?!… ፓንትም ደግሞ ሊለበስ?!”… “ሆሆ ጆሮ አይሰማው የለ መቼም!”… “ወይ ጉድ!… ጉድ እኮ ነው!”… “አኡዙቢላሂ!… ኧረ ይሄስ ስራ ተብሎ አይወራም!”… “አቦ ንካው እንዲህ አይነት ሂራር አታውራብን!… ወላ ሳይሰራ ቢቀርስ!”… እና መሰል ግርምቶች እየተባሉ ሊሆን ይችላል… ግን ስራ ነው!… ፈረንካው ይሸቀልበታል… 

ባንግላዴሹ… ፓኪስታኑ… ህንዱ… ካሜሮኑ.. ጋናው… ናይጄሪያው… ታይላንዱ… ፖላንዱ… ፊንላንዱ… ስፓኞሉ… ስውዲኑ… ኖርዌዩ… ቱርኪው… እና ሌሎች በርካቶች ፈታ ዘና ብለው ለቀማቸውን በጠራራ ጸሃይ ሲያቀላጥፉት ቀብራራው የሃበሻ ልጅ ግን እምብዛም አይደፍረውም…. ታጥቦ ታጥኖ ደጁ ላይ የተከመረው ቆሻሻ ልብሱን እንዳያበላሽበት እየዘለላት ያደገው ኩሩው የኢትዮጵያ ልጅ ግን ይህችን ይህችን አይነት ስራ ንክችም አያደርጋት!… እንደው አልፎ አልፎ አፈንጋጭ ካልተገኘ በስተቀር!…

“ዘ ይግረም ነገር እኮ ነው!”…. “አጃኢበ ረቢ!”… ምናምን ብላችሁ ሳትጨርሱ ካፋችሁ ልንጠቃችሁና ልቀጥል… 

ፓንት ሲባል እኛ በለመድነው እና በምናውቀው አማርኛችን እንደሚገባን የውስጥ አልባስትን የሚገልጽ ቃል አይደለም… ፓንት ባገርኛው ቋንቋ የታሸጉ መጠጦች ከተሸጡና ከተጠጡ በኋላ እቃዎቹ ለዳግም አገልግሎት ይውሉ ዘንድ ያላቸው ዋጋ ማለት ነው… 

ባብዛኛው የታሸጉ መጠጦች የዳግም አገልግሎት ዋጋ አላቸው… የተለያዩ አይነት ለስላሳ መጠጦች… ቢራዎች… ዉሃዎች… ቫይታሚኖች… ጁሶች… ኢነርጂዎች… እና መሰል መጠጦች እሽጋቸው ላይ የፓንት ዋጋቸው ተጽፏል… እንደው ለምሳሌ ብንወስድ አንድ ባለ ሁለት ሌትር ኮካ ኮላ ገዝተን ከተጠቀምን በኋላ ኮካውን ይዞ የነበረው ፕላስቲክ ማሸጊያ በሁለት የስውዲን ክሮኖር (ወደ 6 ብር ገደማ) ይሸጣል… እና ይህ ነው ፓንት ማለት… የተጠቀሙበት ማሸጊያ ላይ PANT የሚል ጽሁፍ ከዋጋ ጋር ከተለጠፈበት ይሸጣል…. ወደ ገንዘብ ይለወጣል… ፕላስቲክም… ቆርቆሮም… ጠርሙስም ሊሆን ይችላል… 

የኔ ቢጤ ቋጣሪ የሆነ ሰው የጠጣባትን እቃ እቤቱ እያጠራቀመ ሰብሰብ አድርጎ ይሸጥና አስቤዛውን ሊሸማምትበት ይችላል… እንዴ ገንዘብ ነዋ!… መጀመሪያ ተከፍሎበታላ!… ገንዘብ እንዴት ይጣላል?… ወላሂ ሃራም ነው!… እንዲህ የማጠራቀም ትግስቱም ፍላጎቱም የሌለውና በየአጋጣሚው መንገድ ላይ ገዝቶ የሚጠቀመው ግን በየቆሻሻ መጣያው ይጥላቸዋል … ፓንት ሸቃዩ ደግሞ እያሳደደ ይለቅማቸዋል… ከዚያም ወደ ማሽኑ ያስገባቸዋል… ማሽኑም ደረሰኝ ይተፋለታል… በደረሰኙ ያሻውን መግዛት አልያም ፈረንካውን መቀበል ምርጫው ነው… 

በነገራችን ላይ ማሽኑ የእርዳታ አማራጭም አለው… የፓንቱን ገንዘብ መውሰድ የማይፈልግ ፓንቶቹን አምጥቶ ማሽን ውስጥ የሚጨምራቸው እቃው ለዳግም አገልግሎት ይውል ዘንድ ያለበትን ሃላፊነት ለመወጣት እንጂ ለገንዘብ ሽቀላ ካልሆነ… ለተራቡ… ለተጠሙ… እና ለተቸገሩ ህጻናት መርጃ ይውል ዘንድ ማበርከት ይችላል… ፓንቶቹን አስገብቶ ሲጨርስ የቢጫዋን በተን መጫን ብቻ ነው የሚጠበቅበት!… የረዳውን የብር መጠን የሚገልጽ የምስጋና ደረሰኝ እጁ ላይ ይወድቅለታል…. ግለሰቡም አከባቢውን ከቆሻሻ ታድጎ እግረ መንገዱንም የተቸገረን ህጻን ረድቶ ይመለሳል…. 

ዋናው ጉዳይ ለሸቃዩ የሚያስገኘው ገንዘብ ብቻ አይደለም!… ከአካባቢ ብክለት የጸዳች ከተማን ለመስራት ያለው አስተዋጽኦም ጭምር እንጂ!… ቸልተኛው ቢጥለው ገንዘብ ፈላጊው ያነሳዋል… በአግባቡም ለዳግም አገልግሎት እንዲውል ያደርገዋል… ከዚያም ለዚህ ጉዳይ በተሰማሩ ባለሙያዎችና ማሽኖች ታግዞ ይጨፈለቃል… ይቀጠቀጣል… ዳግም ይሰራል!… ጠርሙስ፣ ፕላስቲክና ቆርቆሮ ነክ በሆኑ ቆሻሻዎች የበከተች ከተማ ማየትም ብርቅ ይሆናል… የሰለጠነ ቆራሊዮ ይሏል ይህ ነው!… 

ውይ ውይ አዲስ አበባዬ… ውይ ውይ መርካቶዬ… ውይ ውይ ፒያሳዬ… ውይ ውይ ካዛንቺሴ… ውይ ውይ ኢትዮጵያዬ!…. እናንተስ መች ይሆን እንዲህ ያለው ወግ ደርሷችሁ የማየው ስትል የግድህን ትጠይቃለህ… 

አቦ እንዲህ ሰልጠን ያሉ ቆራሊዮዎች ይኑሩን… ይምጡልን… ድንገት የማናውቃቸው ካሉም ይታወቁ… ይንቀሳቀሱልን… አካባቢያችንን ከብክለት… ከተማችንንም ከቆሻሻ ይታደጓታልና!
Image

ሰላም! 
አብዲ ሰዒድ

 
Leave a comment

Posted by on April 28, 2013 in ስብጥርጥር

 

ውቢቱ ጎጃሜ . . .

peace

♪♪ ውቢቱ ጎጃሜ 

. . . ውቢቱ ጎጃሜ
ትመጫለሽ በህልሜ ♪♪ 

♪♪ ዓለም ዓለምዬ 
ዓለም ዓለምዬ . . . 

እስቲ ዝምድናሽን ቆጥረሽ ንገሪኝ፤
ከእህት ከወንድሜ የበለጥሽብኝ።

እመጣለሁ ብለሽ መቅረትሽ ምነው? 
የነማንን ጸባይ ልታመጭብኝ ነው?!

ትሁኔ . . . ትሁኔ . . . 
አንቺ አትመላልሽ እምጠለሁ እኔ። ♪♪ 

. . . ከአሶሳ ማዶ ያለች ትንሽዬ መንደር ውስጥ ያንጎራጉራል… እንደወጣች ቀርታ… እንደዋዛ ጠፍታ ከቀዬዋ የተሰወረችበት የጎጃም ኮረዳ ስትናፍቀው ይተካክዛል… ተስፋዬ ወርቅነህ የተባለ ዘፋኝ ለሱ ብቻ የዘፈነለት ይመስለዋል… በዚያ በሩቅ አገር በመሃል አዲስ አበባ… በስም ብቻ በሚያውቀው ጎጃም በረንዳ ላይ ክርትት ብሎ የተከተተውን ይህን ቅን ዘፋኝ ፈጣሪ ነፍሱን ከደጋጎች ተርታ እንዲያሰልፍለት እየተመኘ ይቀጥላል…

“እውን ግን ተስፋዬ እጅግ ድንቅ የሆነ ድምጻዊ አይደለምን?… ድምጹ?… ግጥሙ?… ዜማው?…” እያለ ሊተነትን ይቃጣዋል… እራሱ ጠያቂ እራሱ መላሽ ይሆንና ሙዚቃ እናውቃለን የሚሉ ተንታኞች ስለዚህ ዘፋኝ ሲተነትኑ ሰምቶ ባለማወቁ ይንቃቸዋል… “አያውቁማ!… ሙዚቃ የት ያውቃሉ?… ዝም ብለው በመንጋ ወደነፈሰበት ያጨበጭባሉ እንጂ!” ይሳደባል… 

ምንም እንኳን ከአሶሳ ማዶ ቢኖር ስለ ወሎ፣ ስለ ጎንደር፣ ስለ ጎጃም፣ ስለ ትግሬ፣ ስለ ኦሮሞ፣ ስለ ደቡብ ህዝቦች የተዘፈኑ ዘፈኖችን አዘውትሮ ያደምጣል… ያቺን ውብ ጎጃሜ ከወደደ ወዲህ ደግሞ ጎጃም ጎጃም ማለቱ ብሶበታል… አሁን ግን ካጠገቡ የለችም!… ስትናፍቀው… ባይኑ ላይ ስትመላለስበት… ይይዘው ይጨብጠው ሲያጣ… ከአሶሳ ማዶ አያመጣት ነገር መላው ሲጠፋበት… ጠቅልሎ አይሄድ ነገር አቅሙም ጉልበቱም ሲያንሰው…. ዝምምም ብሎ ያንጎራጉራል… ምስጋና ለተስፋዬ ወርቅነህ… 

♪♪ አስደግመሽብኝ አለቃ ፈንቴን 
ሳር ቅጠሉ ሁሉ መሰለኝ አንቺን 
አስተብትበሽብኝ የኔ ኩንስንስ 
ወገቤ ያላንቺ አይንቀሳቀስ …

ትሁኔ . . . ትሁኔ . . . 
አንቺ አትመላልሽ እምጠለሁ እኔ። ♪♪ 

. . . እሷ ብቻ ሳትሆን የማያውቃቸው አለቃ ፈንቴ ይናፍቁታል… “ምነው ለኔም መተው በደገሙልኝ… ምነው በደገሙብኝ… ምነው በዚህ ሕዝብ ላይ ሁሉ የፍቅር፣ የሰላም፣ አብሮ የመኖር ድግምታቸውን በተበተቡበት… ምናለ ፍቅር በፍቅር ቢያንበሸብሹንና ያለ ፍቅር መንቀሳቀስ ቢሳነን” … … “አይ አለቃ ፈንቴ!… ይበሉ እስቲ!… ወይ እሷን ያምጧት ወይ እኔን ይውሰዱኝ… እስቲ እንዮት!… ይድገሙ!… እስቲ ይሄ እንጉርጉሮዬ እውን እንዲሆን ይተብትቡ!”… የቀትር ጸሃዩ እንደወረደበት በትዝታ ይንከላወሳል ተስፋዬም ያስታምመዋል…

♪♪ እናናንዬ … እናናኔዋ …
እናናንዬ … እናናኔዋ … 

ሰባት ሰዓት ሲሆን ከብት ውሃ ሲጠጣ፤
ደግሞ አገረሸብኝ ትዝታዬ መጣ።

አቤት ያንቺ ጸባይ ለፍቅር ሲመች፤ 
ድፍን የጎጃም ልጅ አለ ወይ እንዳንቺ። ♪♪ 

♪♪ እናናይ ነይ ነይ …
እናናይ ነይ ነይ …

ሃብትና ንብረትሽ ምን ያደርግልኛል?
ካንቺ ጋር አድሬ ብሞት ይሻለኛል። 

ጨረቃ ስትወጣ ስትንቀለቀል፤
ላርግሽ ከደሬት እንደብር መስቀል።

እናናይ ነይ ነይ … 
እናናይ ነይ ነይ … ♪♪ 

. . . እናና እያሉ የሚጠሯት እናቷ ሳይቀሩ ትዝ ይሉታል… ግልምጫቸው… ቁጣቸው… ኩርፊያቸው… አሽሙራቸው… ተረታቸው ሳይቀር እየተፈራረቀ ይመላለስበታል… ይህ የተፈጠረ ከንቱ እንቶ ፈንቶ… ይህ የተንሰራፋ አጓጉል ድንቁርና ወደሚሄድበት ሄዶ… ያመጣው ጋኔል በሚወጣበት ምሱ ወጥቶ… ዳግም ጎጃሚትን ሊቀበላት ይጓጓል… እንደሚሆን ደግሞ ጥርጥር የለውም!… ፍቅር ጥግ የለውማ!… ፍቅር አሸናፊ ነዋ!… ልክ ባለፈው እንደሆነው ተሰብስበው ሲመጡ ተሰብስቦ ሊቀበላቸው ይጓጓል… አበባ ይዞ ወደቀዬዋ ሲያደርሳት ይታየዋል… 

♪♪ ደሞ አለው አበባ 
ደሞ አለው አበባ
ጎጃሜው ሲገባ ♪♪

♪♪ ደሞ አለው አበባ 
ደሞ አለው አበባ
ጎንደሬው ሲገባ ♪♪ 

♪♪ ደሞ አለው አበባ
ደሞ አለው አበባ
ወለዬው ሲገባ ♪♪ 

♪♪ ደሞ አለው ደስ ደስ
ደሞ አለው ደስ ደስ 
አዲስ ላይ ስንደርስ ♪♪ 

. . . አዲስ መሄድ ያምረዋል… እዚህ እሷ የሌለችበት መንደር ውስጥ በትዝታ ከሚያላዝን የማንም ባልሆነችው ሸገር ላይ በባዱ ኪሱ መንሸራሸር ያምረዋል… “አፈር ምን ያደርጋል?… እርሻ ምን ይሰራል?… ንግድስ ምን ፋይዳ አለው?.. እኚህ ሁሉ ጥቅማቸው ትርጉም የሚኖረው በፍቅር ውስጥ አይደል እንዴ?!… ፍቅር ከሌለ ሁሉም የለም!… አለቀ… ደቀቀ!” ሊፈላሰፍ ይቃጣዋል… “ምድሪቷን የሰሯት ይመስል የኔ የኔ እየተባባሉ ይፋጃሉ… ከንቱዎች!… ይሄን ከንቱ ኮተታቸውን ወስደው ፍቅሬን በመለሱልኝ… ውቢቷ ጎጃሜን!… ድህነቴን የምታስረሳኝን ውዴን!” … 

♪♪ ዓለም ዓለምዬ 
ዓለም ዓለምዬ . . . 

ሰላሌ ራስ ካሳ ቢያስፈልጉ አጡሽ 
ጎንደር አጼ ፋሲል ቢያስፈልጉ አጡሽ
ጎጃም ራስ ኅይሉ ቢያስፈልጉ አጡሽ
ደቡብ ንጉስ ጦና ቢያስፈልጉ አጡሽ
የሸዋው ምኒሊክ ቢያስፈልጉ አጡሽ 
ደሃ ቁርጠኛ ነው እኔ አገኘሁሽ ♪♪ 

. . . ቁርጠኛነቱን የሰለቡበትን… ተስፋውን ያደበዘዙበትን ሁሉ ይራገማል!… በፍቅራቸው ላይ የተጋረጠውን ጋሬጣ ከመፍታት ይልቅ “ውሻ በቀደደው ምን ይገባበታል” እንደሚባለው አይነት አጋጣሚውን ተጠቅመው የነፍሳቸውን ከንቱ መሻት እየፈተፈቱ የበለጠ ሊያቆራርጧቸው የሚማስኑትን ሁሉ የበለጠ ይራገማል… ከንቱዎች! 

ልክ እሱ እዚህ ውቢቱ ጎጃሜን እንደሚያንጎራጉረው ሁሉ እሷም ፍኖተ ሰላም ላይ የምጽዋት ስንዴ እየተሰፈረላትም ቢሆን ዙምባራን እየዘፈነች እሱን እየናፈቀች እንደሚሆን ቅንጣት አይጠራጠረም… የዙምባራ ጭፈራዋ ሁሉ ይታየዋል . . . 

♪♪ ይኸው ተነሳሁ 
. . . ልሄድ አሶሳ 
__ ሲኞር ከተማ ማማይ …

ዙምባ በሉማ … ዙምባ በሉማ …
ዙምባ በሉማ … ዙምባ ዙምባ …

ሸኙኝ ወደዛ 
ትዝታው በዛ 
__ ሲኞር ከተማ ማማይ ..

ዙምባ በሉማ … ዙምባ በሉማ … 
ዙምባ በሉማ … ዙምባ ዙምባ …
.
.
.

ዙምባራ… ዙምባራ… ዙምባራ… ዙምባ… ዙምባ… 
ዙምባራ… ዙምባራ… ዙምባራ… ዙምባ… ዙምባ… 

ቤኒ… ቤኒ… ቤንሻጉል!…
ቤኒ… ቤኒ… ቤንሻንጉል!… ♪♪ 

ትታየዋለች!… ስትዘፍን… ስትጨፍር… ደግሞም የዘመን ኮተት ሲያስቆዝማት!… ይተካክዛል ተስፋው ግን አይደበዝዝም… የሱ አገር የሱ መንደር… ልቦናው ውስጥ ያለችው ፍቅር ናትና! . . . 

. . . 
ዙምባራና ጎጃም አንድም ሁለት ናቸው
የፍቅር ሰንሰለት ያስተሳሰራቸው
ማነው የሚበጥስ የልብን ቋጠሮ
ከአገር ይሰፋል ፍቅር እኮ ውሎ አድሮ:: 
. . . 

______ // አብዲ ሰዒድ // _____

 
Leave a comment

Posted by on April 7, 2013 in ስብጥርጥር

 

ኮኤ ፉሺ ! . . . ሃኮ ፉሺ ! . . .

Image Picture source: google search!

በሲዳማ ዞን አርቤጎና ውስጥ በአገር ሽማግሌዎች የተከወነ የፍትሃዊ ምርጫ ሂደት ተመክሮ እንካችሁ…

ምርጫው ሊካሄድ ሁሉም ነገር ተዘጋጅቷል… አስመራጮች… ታዛቢዎች… ጸጥታ አስከባሪዎች… ሽማግሌዎችና ሌሎች የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ ቦታ ቦታቸውን ይዘዋል…. መራጩ ህዝብም የምርጫ ካርዱን እንደያዘ ተሰልፎ ይጠባበቃል… ምርጫው ይጭበረበራል፣ ኮሮጆው ሊቀየር ይችላል ብለው የሰጉት የአገር ሽማግሌዎች የራሳቸውን የፍትሃዊ ምርጫ መላ ዘይደዋል… ሁሉም ነገር መጠናቀቁን ሲያረጋግጡም ተነሱ…

ለጸጥታ አስከባሪዎችም አሏቸው: ”ቴኔ ኮሮጆ ሃዺ !” … በደምሳሳው ሲተረጎም ”ይህን ኮሮጆ ወዲያ አንሱት!”… ”ኮሮጆውን ውሰዱት!” እንደማለት ሊሆን ይችላል…

በመቀጠልም የለበሷቸውን ረጃጅም ቡሉኮዎች (ጋቢዎች) ለሁሉም ግልጽ በሆነ መሃል ቦታ ላይ አነጠፏቸው… ለፍትህና ለሃቅ ቆሙ… ለመራጩ ህዝብም አሉት…

”ኮኤ ፉሺ !…”
”ሃኮ ፉሺ !…”

በግርድፉ ሲተረጎምም :

” እዚህ አድርግ! … እዚችው ጣል !”
” እዚህ አስቀምጥ! … እዚችው ቁጭ አድርግ !” … እንደማለት ሊሆን ይችላል …

ሕዝቡ በሽማግሌዎቹ እምነት አለውና አላንገራገረም!… የፓርቲዎች አርማ ያለበትን ወረቀት ወስዶ… ሚስጥራዊ ክፍሏ ውስጥ ገብቶ… የሚመርጠው ምልክት ላይ የ X ምልክቱን አኑሮ… ወረቀቱን እያጣጠፈ ወደ ውጭ ይወጣል… ወደ ተዘረጋው ቡልኮ ላይ ሁሉም እያዩት ወርውሮ ይሄዳል… ሽማግሌዎቹም በንቃት ይጠባበቃሉ… ድንገት የሚያንገራግር… ከሂደቱ የሚያፈነግጥ ሲገኝም ሽማግሌዎቹ ይገስጹታል…

”ኮኤ ፉሺ !…”
”ሃኮ ፉሺ !…” … ይሉታል… ”እዚህ አድርግ! … እዚችው ጣል!” … ወይ ፍንክች!… እያሉ ይመልሱታል…

እንዲሁ ቀኑን ሙሉ ”ኮኤ ፉሺ !… ”ሃኮ ፉሺ !…” እንዳሉ ይውሉና ምርጫው ይጠናቀቃል… የድምጽ ቆጠራውም በሽማግሌዎቹ ዳኝነት ይከወናል… ኮሮጆ የሚባል ነገር ለምርጫው ቅንጣት አስተዋጽኦ ሳያደርግ ይውላል… ለማጭበርበር የተዘጋጁ ኮሮጆዎች ከነበሩም ውሃ በላቸው… በውጤቱም ባለ ዶሮ ምልክቱ የተቃዋሚ ፓርቲ ሲአን (ሲዳማ አርነት ንቅናቄ) አሸነፈ… ባለ ንብ ምልክቱ ተፎካካሪም ሽንፈቱን አምኖ ተቀበለ… ምንም መፈናፈኛ የለማ!…

መራጩ ሕዝብም አለ:

”ቢኒቾ ኢሽ !…”
”ሉኪቾ ሊሽ !…”

ሲተረጎምም…

”ንቧን ወደዚያ !…
ዶሮዋን ወደዚህ !…

እንደማለት ይሆናል… ንብ በሲዳምኛ ቢኒቾ ሲሆን ዶሮ ደግሞ ሉኪቾ ነው… ቋንቋውን በደንብ የምታውቁ ትርጓሜውን ብታርሙኝ ደስታዬ ነው …

”ኮኤ ፉሺ !…”
”ሃኮ ፉሺ !…” የሚሉ ሃቀኛ ዳኞች አያሳጣን አቦ!…

ሽማግሌዎቻችንን እድሜያቸውን ያርዝምልን !!!

”ቢኒቾ ኢሽ !…”
”ሉኪቾ ሊሽ !…”

በሰላም የተሞላ የሳምንት መጨረሻ ይሁንላችሁ!

አብዲ ሰዒድ 

 
Leave a comment

Posted by on March 30, 2013 in ስብጥርጥር

 

*** የጸጥታ ያለህ ?! ***

Image
ባለፈው ”በዣንዣድ ሰላም ሲናድ” ስል የዴርቶጋዳው ደራሲ በሐዋሳ ከተማ ስለከፈተው ”ዣንዣድ ባርና ሬስቶራንት” የቸከቸኳት ሚጢጢዬ ትዝብት ብዙ ሙገሳዎች እንዲሁም ድቆሳዎች አስነስታለች… እሰይ እንኳን አስነሳች!… ሙገሳውም ትንኮሳውም በቀና ልቦና እስከተንሸራሸረ ድረስ ለሚፈለገው ለውጥ የበኩሉን አስተዋጽኦ ያበረክታልና! 

በበኩሌ ይስማዕከ ደራሲ ነውና አይነግድ!… ደራሲ የሆነ ሰው ከወረቀትና ከእስክሪብቶ በቀር ሃብት ሊኖረው አይገባም!… የህዝብ ልጅ ነውና ሲታመም በልመና ይታከም!… ሲሞትም ለቀብሩ ማስፈጸሚያ እርዳታ ይሰብሰብለት!… ደራሲ ነውና በድህነት ይፎክት!… ስለምን ይነግዳል?!… ስለምንስ ራሱን በሃብት ያበለጽጋል?!… አላልኩም!… አልወጣኝም!… ይቺው ሚጢጢዬ የሰውነት ልኬም እንደሱ እንድል አትፈቅድልኝም!… በፍጹም!

የጥበብ ሰው ሲነግድና ሲያስነግድ… ወደ ተሻለ የኑሮ ደረጃ ሲሸጋገር… ጸሃፊያንን ያበረታል፣ ለዘርፉ መበልጸግም አዎንታዊ አስተዋጽኦ ያበረክታልና ወደ ንግድ ስራ ጎራ በማለቱ ልባዊ የሆነ ድጋፍ እንጂ ተቃውሞ የለኝም!… ነገር ግን ምንድነው የሚነግደው?… እንዴት ነው የሚነግደው?… የት ነው የሚነግደው?… የሚሉትን ጥያቄዎች ከሌላው ሰው በተለየ በትኩረት እጠይቃለሁ!… ምክኒያቱም ጥፋቱንም ልማቱንም የሚከተሉ ብዙ ተከታዮች አሉትና!… 

”ዣንዣድ ባርና ሬስቶራንት” የተከፈተው ፍጹም ሰላማዊ የሆነ መኖሪያ መንደር ውስጥ ነው… የአካባቢውን ሰው ሰላም እየረበሸ ነውና ተገቢ አይደለም!… ይህ አይነቱ ሰላምን የመንሳት ተግባር ደራሲ በሆነ ግለሰብ ሲፈጸም ደግሞ የበለጠ ያማል!… እናም የእርምት እርምጃ ሊወሰድበት ይገባል… ለዚህ ጉዳይ ቦታውን የሚፈቅዱ የስራ አስፈጻሚዎችም ሊያስቡበት መንግስትም ለድምጽ ብክለት ችግር አበክሮ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል ነው የኔ ሃሳብ!… አራት ነጥብ!

”ምነው መኖሪያ መንደር ውስጥ ጭፈራ ቤት ሲከፈት ብርቅ ነው እንዴ?… እኛ ያደግነውስ ከግድግዳችን ጎን እየተጨፈረብን አይደለም እንዴ?… ምነው እስከዛሬ አላንገበገበህም?… ምነው በሌሎቹ ላይ አልተነሳህም?… ምን ደርሶ ለአካባቢ ሰላም ተቆርቋሪ ይመስል የግል ጥላቻህን ትቀባጥርብናለህ?!”… ጃስ ገለመሌ ላላችሁኝ ሁሉ… … 

“እኛ የምንፈልገው የተዛመተን እኩይ ተግባር የሚቀንስ፣ ለተሻለ ለውጥ የሚያተጋን እንጂ የሚያባብስ አውቆ አጥፊን አይደለም ነው መልሴ!… እንደ ወረርሽኝ የተዛመተ አጉል ተግባር ሁሉ ሃይ የሚል እስካልተገኘ ድረስ ልክ ነው ማለትም አይደለም!… ኧረ በህግ ልንላቸው ይገባል (ህጉ ባይኖርም!… ህጉ ባይተገበርም!…)” 

በየሰፈሩ የነዋሪን ሰላም የሚነሱ ተግባሮች ሞልተዋል… በሃይማኖታዊ ትምህርት… በንግድ እንቅስቃሴ… በፖለቲካ ቅስቀሳ እና በሌሎች በተለያዩ አጋጣሚዎች እየተሳበቡ የሚካሄዱ ረብሻዎች ልክ የላቸውም!… ለድምጽ ብክለት ያለን ምልከታ እጅግ አናሳ ከመሆኑ የተነሳ የየእለት ኑሯችን መደናቆር የበዛበት እንደሆነም አያጠያይቅም!… 

እናም እነዚህን የጤና ጠንቅ የሆኑ የመደማቆር ድርጊቶች ልናወግዛቸው ይገባል!… ባወገዝናቸው ልክ ወደ ሰላማዊ ኑሯችን እንጠጋለን… ሰባኪውም ያለ ብክለት ይሰብካል!… ነጋዴውም ያለ ብክለት ይነግዳል!… ተራማጁም ያለ ብክለት ይራመዳል!… ከድምጽ ብክለት የጸዱ ከተሞቻችንም ይበዛሉ!… ያብዛልን አቦ… 

ይህ ማለት ግን ትችቶች ሁሉ ስርአት በጎደለው መልኩ የግለሰብን ግላዊ ህይወት በሚያብጠለጥል ሁኔታ ይካሄዱ ማለት አይደለም… ደራሲውን በተመለከተም ምናልባት ስሜታዊ ሆኜ ስድብ ነገር ተጠቅሜ ከሆነ ከመናደድ የመነጨ ነውና ይቅርታ!… እታረማለሁ!… የጻፉኩት በሙሉ ግን ያየሁትን አንዳች ነገር ከራሴ አልጨመርኩም!… እታረማለሁ ስል ለስሜታዊነቱ ብቻ ነው!

ያነሳሁትን ጉዳይ ግን አሁንም ደግሜ አነሳለሁ… የሰፈር ሰላም ሊነሳ ፈጽሞ አይገባም!… ይህ አይነቱን የግዴለሽነት ተግባር ከደራሲ አልጠብቅም!… እናም ወይ ድርጅቱን ያስተካክል አልያም ለጫጫታና ለዳንኪራ በሚመቸው ሰፈር ወስዶ ይክፈተው… 

የሆነው ሆኖ ሃላፊነት የሚሰማው አስተዳደር ባይኖር እንኳ በሃላፊነት መነገድ የባለ ህሊና ግዴታ ይመስለኛል!… እናም ለድምጻችን ለከት እናብጅለት… 

መልካም ቅዳሜ!

አብዲ ሰዒድ

 
1 Comment

Posted by on March 30, 2013 in ስብጥርጥር

 

በ – ዣ – ን – ዣ – ድ . . . ሰላም ሲናድ …!

terre22
እግር ጥሎኝ… ውበትና ተፈጥሮን አድሎኝ… በፍቅርና በሃሴት ተፍነክነክ ብሎኝ… ደልቶኝ… ሞቆኝ… ምችት፣ ምችትችት ብሎኝ… የሐዋሳ ሰማይ ስር ከርሜ ነበር:: ሐዋሳ ፍቅር እንደሆነች ባየኋት ልክ የምታስደስተኝ… በኖርኩባት ልክ የምትናፍቀኝ… በሸሸኋት ልክ የምታስጨንቀኝ… መሽቶ በነጋ ቁጥር ነገን የምታስመኘኝ የስስት ከተማዬ ናት::

አይደለም አሁን እንዲህ በአስፋልትና በውስጥ ለውስጥ የኮብል ስቶን ንጣፍ አሸብርቃ ይቅርና አቧራ እየለበስን፣ በጠራራ ፀሃይ እየተጠበስን፣ የሞላልን ቀን በጋሪ፣ ያልሞላልን ቀን በኮቴ አሸዋውን በሲሊፐራችን እየዛቅን ስናዘግም እንኳ ለፍቅሯ ጥግ አልነበረኝም… ያን ደማቅ ሰማያዊ የታቦር ሃይስኩል ዩኒፎርም ራሳችን ላይ ጣል እንዳደረግን ጀላቲ እየመጠጥን… አሊያም ሸንኮራ እየጋጥን… ሲደላንም የማዘር ቤትን የ60 ሳንቲም አምባሻ እየጎመጥን… በላዩ ውሃችንን አንዳንዴም ʿሴሏችንንʾ እየጨለጥን ጎዳናውን ስንሸከሽከው እንኳ ለፍቅሯ ልክ አልነበረኝም…

እንዲህ እንደዛሬው በባጃጅ ሽር በሚባልበት ወቅት ይቅርና የጡረታ ዘመኗ ባለፈባት ድክሞ ሳይክል SOSን አልፌ ጥቁር ዉሃ ድረስ ስንተፋተፍ እንኳ ለፍቅሯ የሚያህላት አልነበረኝም!… ዛሬም የሰላምና የደስታ ጥጌ ሐዋሳ ናት!… ሐዋሳ ሰላም… ሐዋሳ ፍቅር!…

እናም የሲዳማን የቆጮ ምግቦችና የወተት አይነቶች እያጣጣምኩ፣ የቶኪቻውን (የዮሐንስ በቀለን) ጫምባላላ እየዘፈንኩ ሐዋሳ ከርሜ ነበር… ምንም እንኳ በዛ ያሉ የጭፈራ ዘፈኖች ቢኖሩም ጫምባላላን ግን እጅግ እወደዋለሁ… ከባህል አንፃር ደህና ትርጉም ስላለው ይሆን?!…ነሸጥ ስለሚያደርገኝ ይሆን?!… እንጃ ብቻ!… “አይዴ ጫምባላላ” … “አይዴ ጫምባላላ” … ማለት እጅጉን ያስደስተኛል …

♫… ሻፌቱ ሺቄና ጊሩ ማሲሬና
አይዴ ጫምባላላ ኢሌ ኢሌ… ♫

♫… ሲዳማ ጎባያ ሲዳማ አዋሳ
ስንቅ ይዤልሻለሁ ስምሽ እንዲነሳ
ቡርሳሜ ናፍቆኝ ስመለስ ሲዳማ
በሩቅ እየታየኝ የታቦሩ ግርማ… ♫

♫… ሌምቦ … ሌምቦ …
ሌምቦ ሌላ ሌምቦ …
ሌምቦ … ሌምቦ …
ሌምቦ ሌላ ሌምቦ… ♫

♫… አይዴ ጫምባላላ
አይዴ ጫምባላላ… ♫

ጫምባላላ የሲዳማ ብሔር የዘመን መለወጫ በዓል በሆነው በፊቼ በዓል ማግስት የሚከበር እለት ሲሆን እለቱ ልጆች ˝አይዴ ጫምባላላ”… ˝አይዴ ጫምባላላ”… እያሉ በየቤቱ በመዞር የሚዘፍኑበት… የተዘጋጀላቸውን ባህላዊ ምግብ የሚመገቡበት… ከማንኛውም ስራ ነፃ የሚሆኑበት፣ የሚመረቁበትና የሚከበሩበት ዕለት ነው… በነገራችን ላይ የሲዳማ ብሔር የጨረቃን ኡደት መሰረት ያደረገ የራሱ የሆነ የዘመን አቆጣጠር አለው… ፊቼ እና ጫምባላላም ከዚሁ ዘመን አቆጣጠር ጋር የሚያያዙ የዘመን መለወጫ ክብረ በዓሎች ናቸው… በየአመቱ የፊቼ በዓል ሲሆንም በሐዋሳ ከተማ ወደ አሞራ ገደል በሚወስደው መንገድ ጀርባ ሃይቅ ዳር በተዘጋጀ ቦታ ላይ በዓሉ ይከበራል… እኛም ታድመን ኮምኩመነው ነበር… አቤት ደስ ሲሲሲልልል….!

እንዲያው እግረመንገዴን አነሳሁት እንጂ የተነሳሁትስ ስለ ሲዳማ ባህልም ሆነ ስለ ፊቼ ዘመን መለወጫ በዓል አከባበር ለማውራት አይደለም!… ይልቁንም ወደ አሞራ ገደል በሚወስደውና የአካባቢው ድባብ ሰላምን በሚያድሰው ጎዳና… የፊቼ በዓል በጀርባው በሚከበርበት ጎዳና… ሰላማዊ ውሎ ብሎም ነፍስን በሃሴት የሚሞላ ፀጥታ የሚፈልግ ማንኛውም ግለሰብ ዘና ብሎ የእግር ጉዞ በሚያደርግበት ጎዳና… ፀጥ እረጭ ያለ የሰከነ ኑሮ የሚፈልግ ሰው ቤት ኪራይ በሚፈልግበት ጎዳና… በአካባቢው መኖሪያ ቤት ያለው ሰው ረጋ ብሎ አትክልቶቹ ዙሪያ ተቀምጦ ስሜቱን በሚያዳምጥበት ጎዳና… ማንም አካባቢውን የሚያውቀው ግለሰብ ስለፀጥታው ሰላማዊነት በሚመሰክርበት በአሞራ ገደል ጎዳና ላይ በዴርቶጋዳው ደራሲ በፊታውራሪ ይስማዕከ ወርቁ አማካኝነት ስለተከፈተው ዣንዣድ ባርና ሬስቶራንት ላወራ እንጂ …

ዣ – ን – ዣ – ድ … ባ – ር . . .

ስለ ዣንዣድ ባር ከሰማሁበት እለት ጀምሮ ልጎበኘው እጅጉን እፈልግ ነበር… በየጥጋጥጉ ጭፈራና መሸታ ቤት በበዛባት አገራችን ቢያንስ ደራሲ የሆነ ሰው የሚከፍተው ባር ነፍስን የሚያድስ… በሙዚቃ ምርጫው መንፈስን የሚያረካ… የንባብ ባህልን የሚያበረታታ… የህብረተሰብን ንቃተ ህሊና የሚያጎለብት እንደሚሆንም ቅንጣት ጥርጥር አልነበረኝም!… ብቻ ልጎብኘው እንጂ ያለኝን አክብሮትማ እገልጽለታለሁ ስልም አስቤ ነበር… 

“… ዴርቶጋዳ … ዴርቶጋዳ
እንነጠቃለን ከተጫነን ፍዳ
ማንም ሰው ላይመጣ እኛን ለመለወጥ
አናፈገፍግም አናቅማማም ለለውጥ
ያቀረቀርክበት አንገት ያስደፋህ ቀን
ነግቷል ብለህ ተነስ ፍዳና ሰቀቀን …”

እኒህንና መሰል የለውጥ ግጥሞችን የጻፈ ገጣሚ… የወጣቱ መለወጥ የሚያንገበግበው ደራሲ… የከፈተው ባርማ በእርግጥም የሚበረታታ እንደሚሆን ለመገመት አላንገራገርኩም!… ነገሩ ግራ የገባኝና የተገላቢጦሽ የሆነብኝ ግን ገና ዣንዣድ የተባለውን ባር በራፍ ስረግጥ ነው …

ዣንዣድን የጎበኘሁት በማታ ነበር… በግምት ከምሽቱ 2 ሰዓት ገደማ ይሆናል… ከአንዲት ሐዋሳ ከምትኖር ወዳጄ ጋር ነበርኩኝ… ገና ወደ ውስጥ እንደዘለቅኩ የዋት መጠኑ በውል ከማይታወቅ ʿትልቅ ሞንታርቦ እስፒከርʾ የሚለቀቅና የጆሮን ታምቡር የሚበጥስ ለዛ የሌለው ሙዚቃ ከሚሰነፍጥ ትንፋግ ጋር ተቀበለኝ… እንደምንም መቀመጫ አግኝተን እንደተቀመጥን…

እኔ: ˝እርግጠኛ ነሽ ግን ዣንዣድ ባር ይሄ ነው?!˝ ስል ወዳጄን በጥያቄ አጣድፋት ገባሁ… እስፒከሩ ሲያምባርቅብኝ የሳልኩት ዣንዣድ አፈር ከዲሜ ሲግጥብኝ ይሰማኛል …

ወዳጄ: “እንዴ አዎ ተረጋጋና በደንብ ተመልከተው እንጂ!”… ʿገና ምን አይተህ!… እኛም እንዲህ ነው የተሸወድነውʾ በሚል ቅላጼ!…

የወዳጄን ንግግር ተቀብዬ ዙሪያዬን ስቃኝ… መጽሃፍ ይዞ የቆመ ቅርጽ… የተለያዩ ደራሲዎችና ፈላስፎች ፎቶ… በቅርጽ የተሰራ ጣራ… አንዳች ነገር የተለበጠበት ግድግዳ… ድንግዝግዝ ያለ ክፍል… ብልጭ ድርግም የሚሉና የውስጥን ሰላም የሚያውኩ መብራቶች… ልጅነታቸው የሚያሳሳ ቢጢቆ ጉርድ የለበሱ ጨቅላ ሴት አስተናጋጆች (የትምህርት ቤት ዩኒፎርም የለበሱ የሚመስሉ)… ቅርጻ ቅርጾች… እና ወዘተ…. ነገሮችን ተመለከትኩኝ…

በʽርግጥ ቤቱ ያምራል… ለቤቱ ውበት የተሰጠው ግምትም ደስ ይላል… ብልጭ ድርግም የሚለው መብራትም የሆነ ቅርጽ እንዲሰራ የተፈለገ እንደሆነ ያስታውቃል… ምን አይነት ቅርጽ እንደሆነ የማይበትና የማገናዝብበት ትዕግስት ግን አልነበረኝም… ዴር33 ይሁን?!… ብቻ እንጃ!… በውስጠኛው ክፍል ያለማቋረጥ ብልጭ ድርግም ሲል ይታየኛል…

ወደ ውስጠኛው ክፍል ዘለቅኩ… ገና ስገባ የረበሸኝን አይነት ሁለተኛ ስፒከር እዚህም ከጣራ በላይ ያምባርቃል… እዚህም እዛም ወጣቶች ይደንሳሉ… ባንኮኒውን ከበው የሚጠጡም አሉ… የሚተሻሹ፣ የሚደባበሱ ጥንዶችም ይታዩኛል… መቀመጫ እንደሚልግ ዘወርወር አልኩና ወደነበርኩበት ወደ ሳሎኑ… ወደ ሶፋ መቀመጫዬ ተመለስኩ … ስቀመጥ ከበላዬ የጋሽ ስብሓት ምስል ይታየኛል…
ስሜቴ ተደበላለቀብኝ… የቤቱ ሁሉ ነገር አስጠላኝ… በዚህ ጥግ ካሸር… በዚያ ጥግ አልኮል ቀጂ… በሌላኛው ጥግ የጄኔሬተር ቤት… በአራተኛው ጥግ ሰላም የሚነሳ ስፒከር… በሌላኛው ክፍል ደሞ ሌላ ስፒከር… ደሞ ሌላ ረብሻ… ደሞ ሌላ መደነሻ… የሚያሳሱ አስተናጋጆች ብቻ ስብሰከሰክ የታዘዘችን አስተናጋጅ ምግቡንና መጠጡን እያቀራረበችልን ነበር… ጥያቄዬን አግተለተልኩላት…

እኔ: እኔ ምልሽ እናት በየት በኩል ነው ቤተ መጽሃፍቱ?
አሷ: እ…እ?!… እሱ እዚህ አይደለም ሌላ ቦታ ነው…
እኔ: ሌላ ቦታ?… የት?… (ሌላም ባር አለው ይሆን እያሰብኩ)…
እሷ: እ…እ? እኔጃ ግን አለ…
እኔ: እሺ እሺ … እዚህ ቤት ምንም የሚነበብ ነገር የለም?
እሷ: እ…እ?… የለም!…
እኔ: ሁሌም እንዲህ አይነት ሙዚቃ ነው የምትከፍቱት?
እሷ: እ…እ…?! አዎ!… ምነው ጥሩ አይደለም?… ዘፈን ላስቀይር?
እኔ: አይይ ትንሽ ድምፁ በዛ ብዬ ነው… እስቲ ቤቱ ምን የተለየ ነገር አለው?… አስጎብኚን?
እሷ: እ?… ዋሻውን አይታችሁታል?… በውስጥ በኩልʿኮ ዋሻ አለ…
እኔ: አይ አላየነውም… ዋሻው ውስጥ መቀመጥ ይቻላል?
እሷ: አዎ!… እዛም ልትዝናኑ ትችላላችሁ… አሁን ግን ጨለማ ነው… (በድንገት መብራት ጠፍቶ ጄኔሬተሩ እያምባረቀብን ነበር)
እሺ: እሺ እናመሰግናለን . . . 

የተባለውን ዋሻ ላየው ብፈልግም ወደ ውስጥ መዝለቁ አስጠላኝ… ከቤቱ ድባብ ስነሳ ባየውም የተለየ ነገር ጠብ የሚልልኝ አልመስልህ አለኝ… ደግሞም የአስተናጋጇ ˝ልትዝናኑ ትችላላችሁ˝ አባባል አላስደሰተኝም… ደሞ ሌላ ብስጭት ራሴ ላይ መጨመር አልፈለግኩም… እናም ያለማቋረጥ በሚያባርቀው ሙዚቃ እየተደናቆርን ከወዳጄ ጋር መደማመጥ እስኪያቅተን እየተጯጯህን ማውራታችንን፣ መብላት መጠጣታችንን ቀጠልን… ሙዚቃውም ያለማቋረጥ ማንባረቁን ቀጠሏል… ትዝ ከሚሉኝ ዘፈኖች መካከል የሚከተሉት ቁርጥራጭ ግጥሞ ች ይገኙበታል . . .

111 …
♫… ኤሶ … ኤሶ
ኤሶ ኤሶ ጦና ናታ ወላይታ

ዱርሳ ዱርሳ … ወላይታ…♫ 
ዱርሳ ዱርሳ … ወላይታ …♫

♫… ኪኪያ ዳሞታ
አዋንዳይ አዋንዳይ… ♫

222 …
♫… ትብላው ብሬን
ትብላው ብሬን
ለኔስ ግድ የለም
ትብላው ብሬን… ♫ 

♫… Chop my money
… Chop my money
… Cuz I dont care…
… I don’t care… ♫
… I don’t care… ♫

333 …
♫… ሻላዬ ሻላዬ ዮ
… ቴ ሻላዬ
… ሻላይቱ ገላ ዮ
… ቴ ሻላይ …♫

♫ … ዲላ ላይ… ዲላ ላይ… ዲላ ላይ…
… ዲላ ላይ… ዲላ ላይ… ዲላ ላይ… ♫

♫… ኤ አና ዴስኮ
ኤ አና ዴስኮ… ♫

እኚህንና መሰል የጭፈራ ዘፈኖችን እየከፈቱ ለማደናቆር ለምን ያን የመሰለ ሰላማዊ መንደር እንደተመረጠ ሊከሰትልኝ አልቻለም… ለዚህ ለዚህማ እነ ከላይ… እነ ቁልቢ… እነ ፍቅረ ሰላም… እና ሌሎች መሰል ጭፈራ ቤቶች የተኮለኮሉበት በተለምዶ ቤርሙዳ ሰፈር የሚባለው የሐዋሳ የጭፈራ መንደር አይሻለውም ነበርን?!… የሰፈር ሰላም መንሳት ምን ይባላል?!… ድንቄም ደራሲ እቴ!… እንዲህም አድርጎ ለወገን ተቆርቋሪነት የለ!… ቆሽቴ እርር ድብን አለብኝ…

ሂሳባችንን ከፍለን ለመውጣት ተጣራሁ… ያቺው አንድ ፍሬ ልጅ የልጅ ፈገግታዋን ይዛ ከች አለች… ጥቂት ላወራት ፈለግኩ…

እኔ: እናመሰግናለን… እንደው በቀን ብንመጣስ ምን ምን አላችሁ?!
እሷ: ሁሉም ነገር አለን…
እኔ: ቆንጆ ቡና አላችሁ?
እሷ: ውይይ ትኩስ ነገር የለንም…
እኔ: እንዴ ለምን?! … ”ይሄኔ ነው መሸሽ”… 
እሷ: አይ ለጊዜው ማሽናችን ተበላሽቶ ነው ይኖረናል…
እኔ: እሺ እንደው መልዕክት ብነግርሽ ለደራሲውና ለቤቱ ባለቤት ታደርሺልኛለሽ?
እሷ: ኧረ አዎ
እኔ: አረቄ ቤት ለመክፈት ደራሲ መሆን አያስፈልግም!… የመንደር ሰላም ለመረበሽ መጽሃፍ መቸርቸር አያስፈልግም!… ድርጅትህን የደራሲ የደራሲ ልታደርገው የማትችል ከሆነ ዝጋው!… ለወገን በቃላት ጋጋታ ያሰቡ ከመምሰል በፊት በተግባር ማሳየቱ ይቀድማል… በይልኝ አደራ!… ትነግሪዋለሽ ግን?…
እሷ: እንዴ አዎ!… እንዲሻሻል አይደል እንዴ?!… ሂሳቧን እየተቀበለችን… በክብር እየተሰናበተችን… አሳሳችኝ… በግምት 20 ዓመት የማይበልጣት እምቡጥ ናት… የልጅነት ወዟን በከንቱ ስማቸውና ገንዘባቸው አሳስተው ከሚቀራመቷት ክፉ አይኖች አንድዬ እንዲጠብቃት እየተመኘሁ ወጣሁ… መልካም ይግጠምሽ የኔ እህት!!!


ከወዳጄ ጋር እያወጋን ተመለስን… እሷም እንደኔው የጠበቀችውና የገጠማት አልጣጣም ብሏት ከምርቃቱ ጊዜ ወዲህ ዝር ብላ እንደማታውቅ ነገረችኝ… ˝ዛሬም ያንተን ስሜት ማወቅ ስለፈልግኩ እንጂ ባልመጣ ደስታዬ ነበር˝… ስትል ብስጭቷን አጠናከረችልኝ 
እንደተብሰለሰልኩ አደርኩ… ግን ቆይ ምን አግብቶኝ ነው የምቃጠለው?! ታዋቂ ሆነ!… ዝናውን ቢዝነስ ማድረግ ፈለገ!… እናም ጠጪ እስካገኘ ድረስ… ከልካይ እስካልገጠመው ድረስ… ያሻውን እያደረገ የቻለውን ያህል ገንዘብ ቢያግበሰብስስ?!… ስል አሰብኩ… ብሽቅ ደራሲ!… በበኩሌ ከመጀመሪያው ዴርቶጋዳ በቀር ሌሎቹ የ ”ቶ” ዲስኩሮች ባዶ እንቶፈንቶ እንደሆኑብኝ ሳስብ የበለጠ አበገነኝ… በተለይ ዣንቶዣራ የተባለው ቁጥር 3 ዴርቶጋዳ ለአንባቢውም ሆነ ለጥበብ ያለውን ንቀት ደህና አድርጎ ያሳየበት የልጅ ጨዋታ እንደሆነ ሲታወሰኝ ˝ድሮም ልጅ ያቦካው ለራት አይበቃም!˝ የምትለኝ አያቴ ታወሰችኝ… እናም በጥበብ እንዲያድግና የተሻለ ነገር እንዲሰራልን ብሎም የሰፈር ሰላም የነሳበትን ባር ተብዬ የሰፈሩንም የደራሲንም ክብር በሚመጥን የተሻለ ቤት ይለውጥልን ዘንድ ልቦና እንዲሰጠው ዱዓ አደረግኩለት…

ለቁርስ ወደቀጠረኝና የህግ ባለሙያ ወደሆነው ወዳጄም ተጣደፍኩ… ስለ ዣንዣድ የታዘብኩትን እና የበገንኩበትን አወጋሁት… እህህ ብሎ ካደመጠኝ በኋላ አንገት የሚያስደፋ ነገር ጨመረልኝ…

እሱ: ቀድመህ ብትነግረኝ ኖሮ ድርሽ እንዳትል እነግርህ ነበር… የክስ መዝገቡ እኮ ገና አልተዘጋም!… አለኝ
እኔ: እንዴ የምን ክስ?!
እሱ: ያካባቢው ሰዎች የመንደራችንን ሰላም ረበሸ… በሰላም መተኛት አልቻልንም… ኧረ በህግ!… አንድ በሉን… በምሽት ያለቅጥ የሚከፍተውን ሙዚቃ ይቀንስልን… አልያም ድርጅቱን ይዝጋልን… ሲሉ የከሰሱበት መዝገብ ነዋ!… ባክህ ልጁ ዝናና ገንዘብ እንዳያስብ ሳያደርጉት አልቀሩም … ያሳፍራል!

የምሬን አፈርኩ!!!… አዘንኩ!… አቀረቀርኩ!… በዝና አልያም በንዋይ ፍቅር ደንቁረው ከሚያደነቁሩን ይታደገን ዘንዳም ጸለይኩ!!!…

“ቱ በል!… ቱ!…
አለችው እናቱ …”
ብሎ እንዳለኝ ጸሃፊ
እንዳስተማረኝ ያ ገጣሚ
እውነት ጥበብን አታሚ
ህጸጽን በወግ ኮርኳሚ…

˝ቶ!…˝ በል እስቲ አንተ ሎጋ
˝ቶ!…˝ ባለ ነው ያኛው ለጋ
አገር ምድሩን ያንጋጋ
ከልሒቅ ተርታ የተጠጋ
የሰፈር ሰላም ያናጋ …

እናም ˝ቶ!˝ በል እስቲ …

ቶ ፊደል ነው የቃል አቻ
የቅንጣት ሚስጥር መፍቻ
የረቂቅ ጥበብ መግቻ
የዝና ጥማት ስልቻ
የንዋይ ማቆር ዘመቻ …

ቻ ቻ ቻ
ቻ ቻ ቻ
ከንቱ ከበር ቻቻ
ባዶ ወሬ ብቻ . . .
ልብ አይንሳው ብቻ !!!

_________//_________
አብዲ ሰዒድ

 
4 Comments

Posted by on March 25, 2013 in ስብጥርጥር

 

እግር ኳሳችን . . .

እኛና ተሳትፎ . . .  budinachen

ኢትዮጵያችን በአፍሪካ ዋንጫ ውድድር የመጨረሻዋን ተሳትፎ ያደረገቸው በ1982 (እ. አ. አ) በሊቢያ ተካሂዶ በነበረው 13ኛው የአፍሪቃ ዋንጫ ውድድር እንደነበር ሰምተናል… እነሆ ከ31 አመት በኋላም ክብራችንን ለመለሱልን ዋልያዎቹ የላቀ ፍቅርና ምስጋናችንን እያዥጎደጎድን እንገኛለን… ከዚህም በላይ ይገባቸዋል!… የሽንፈት ከራማችንን እንደገፈፋችሁት በክፉ የሚያያችሁ ከራማው ይገፈፍ አቦ!… 

መሃመድ አሊ ሸዳድ . . . 

ኢትዮጵያችን ከተሳተፈች 31 አመታት ይቆጠሩ እንጂ በአፍሪካ ዋንጫ ውድድር ላይ ግብ ካስቆጠረች 37 አመታትን ቆርጥማለች… የመጨረሻ ጎሏን ያስቆጠረችው በ1976 (እ. አ. አ) አዲስ አበባ ላይ በኢትዮጵያ አዘጋጅነት ተካሂዶ በነበረው 10ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ውድድር ላይ ነበር… ይህች የመሃመድ አሊ (ሸዳድ) ጎል በወቅቱ ኢትዮጵያን ከግብጽ ጋር 1 ለ 1 በሆነ አቻ ውጤት እንዲለያዩ ያስቻለች ነበረች… 

አዳነ ግርማ . . . 

አገራችን ለመጨረሻ ጊዜ ባፍሪካ ዋንጫ ጎል ስታስቆጥር አዳነ ግርማ አልተወለደም ነበር… ኧረ ገና አልታሰበም!… እየተሰቃየንበት የከረምንበትን የጎል ረሃብ፣ የጎል ጥማት፣ የጎል ድርቅ ድራሹን ስላጠፋልን… ታሪካችንን ስለቀየረልን… በ’ርግጥ የትኛውም አይነት ሙገሳ ይገባዋል… ከንግዲህ የሸዳድ ጎል ቅርስ ብቻ ተደርጋ መወራቷ አብቅቷል… ከ’ንግዲህ በእግር ኳስ ተስፋ የራቃት ኢትዮጵያ እየጠፋች ነው… ከ’ንግዲህ የኳስ ተስፋዋ እየለመለመ ነው… 

በየሰፈሩ የኳስ ፍቅር ያላቸው ታዳጊ ልጆች በወኔ ኳስ እያንከባለሉ እንደሆነ እናምናለን… እንደ አዳነ፣ እንደ ሰለሃዲን፣ እንደ ጌታነህ፣ ባጠቃላይ እንደ ዋሊያዎቹ ዝናቸው እንዲወራ እየተመኙ እንደሆነ ጥርጥር የለኝም!… እነዚህን ልጆች አቅማቸውን ተረድቶ የሚደግፋቸው… በአግባቡ የሚንከባከባቸው እስካለ ድረስ ገና ብዙ ታሪክ ይሰራል!… 

መሃመድ ኡስማን (ሚግ) . . . 

መሃመድ ኡስማን (ሚግ)… 😦 … ልክ የዛሬ 31 አመት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የጊኒን ብሔራዊ ቡድን አሸንፎ ለአፍሪካ ዋንጫ እንዲያልፍ ያስቻለ ሰው ነበር (ነፍሱን አላህ በጀነት ያኑርልንና)… ይህ ከድሬዳዋ የተገኘ ምርጥ የእግር ኳስ ተጫዋች በጣም ፈጣን ከመሆኑ የተነሳ ሚግ በሚለው ቅጽል ስሙ ይታወቃል… እነሆ ከ’ሱ በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫ ሊያስገባን የሚችል ጎል ማስቆጠር ተስኖን 31 አመታት ጠብቀናል… ስለምን ግን 31 አመታት ፈጀብን?… እውን የጥንቶቹን ያህል ተጫዋቾች ማፍራት አቅቶን ነበርን?!… ብለን ብንጠይቅ የዚህ ሰው ታሪክ በከፊል ጥያቄያችንን ይመልስልናል… 

ይህ ለአገር ታላቅ ውለታ የሰራ ሰው ህይወቱ ያለፈው የመከራን ጽዋ እንደተጋተ ነበር… ለዚህ አኩሪ ታሪኩ ኢትዮጵያችን የከፈለችው እስር… ርሃብ… እርዛት…. መገፋት… እና ጎዳና ላይ ማደርን ነበር… ኢትዮጵያን የምታህል ታላቅ አገር ለአፍሪካ ዋንጫ ውድድር ያበቃ ሰው በረንዳ እያደረ በረንዳ ላይ ሲሞት እያየ የትኛው ትውልድ ይሆን በተነሳሽነት ኳስ ሊጫወት የሚችለው?!…. ከቶም አይታሰብም!… ታሪክ መስራት የፈለገ ታሪክ ሰሪዎቹን ያከብራል!… አይከኖቹን ያልቃል!… 

ከሁለት ወይም ከሦስት አመት በፊት የስፖርት ጋዜጠኛው ሰኢድ ኪያር ለዚህ ድንቅ የኢትዮጵያ ልጅ እናትና ቤተሰቦች የተደረገን የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት አስቃኝቶን ነበር (በነገራችን ላይ ጋዜጠኛ ሰኢድ ኪያር ታላላቅ ስፖርተኛቻችንን እንድናውቃቸው በምታደርገው ጥርት በበኩሌ እጅግ አድርጌ አመሰግንሃለሁ) እናም የተመለከትነው የቤተሰቦቹ የኑሮ ደረጃ በ’ርግጥም ያማል!…

እስቲ እሰቡት ከወራት በፊት ላፍሪካ ዋንጫ እንድናልፍ ያስቻሉንን ጎሎች ያስቀጠሩትና እንዲያ ያስቦረቁን… ዛሬም ያስፈነደቁን… ሳላሃዲን ሰኢድ ወይም አዳነ ግርማ ወይም ሌላ የቡድኑ ተጫዋች ተጎሳቁለው ጎዳና ወድቀው ቢታዩ በርግጥ ኢትዮጵያችን አትጎሳቆልምን?… ኧረ ክፉ አይንካቸው!…

እናም እላለሁ አሁን ያገኘነው ክብር ይቀጥል ብሎም የተሻለ ስኬት በዘላቂነት እናስመዘግብ ዘንድ ባለታሪኮቻችንን እናክብር … ታላቁን ያወቀ… የታላቁን ስራ ያከበረ… ከታላቁ ስህተት የተማረ… በ’ርግጥም ታላቅ ነገር መስራት ይቻለዋልና!… መሃመድ ኡስማን ከ 8 አመት በፊት እንዳዘነብን፣ እንደተከፋብን፣ በረሃብና በእርዛት አልፏል!… እሱን ማክበር እስከፈለግን ድረስ ግን ዛሬም ልናስበው እንችላለን…

በየተሰማሩበት የሙያ ዘርፍ ብርቱ ስራ የሰሩ ክብር ብሎም የተሻለ ኑሮ የሚገባቸው ብዙ ሰዎች ዛሬም አሉን… እናም አይናችንን ገልጠን እንመልከታቸው… እናመሰግናለን… እናከብራችኋለን… እንወዳችኋለን…. እንበላቸው!… እነሱን ስናከብር ኢትዮጵያችንን ትከብራለችና!… 

“ምን በደስታ ሰዓት ያላዝንብናል?”… የሚለኝ ቢኖር ልክ ነው!… ጊዜው የደስታ እንጂ የማስለቀሻ እና የችግር ወሬ የመዘብዘቢያ አይደለምና!… በደስታው ወቅት ደስታውን እንዴት ማስቀጠልና እንዴት ተደጋጋሚ ደስታን ማጣጣም እንደሚችል የሚያውጠነጥን ግን በ’ርግጥ ነገም ደስተኛ ይሆናል!… 

እንደው ተምሳሌት ስለ ሆኑ ሰዎች ካወራን አይቀር በነካ እጃችን የሙዚቃችንን ባለውለታ የሆነውን Abebe Melesse-አበበ መለሰንም እናስበው እስቲ!… ሁለቱም ኩላሊቶቹ ታመው ድጋፍ ፍለጋ ላይ ነው… ሁለት ብር ለሁለት ኩላሊቶቹ!… ሞባይሎን 832 ላይ ይጫኑ ከዚያም Z የሚል መልዕክት ይጻፉ… አቤን ያድኑ… በሙዚቃው ይዝናኑ… 

ክብር ለዋሊያዎቹ!… 
ዘላቂ እድገት ለእግር ኳሳችን!…. 
ብርቱ ጥንካሬና መልካም ውጤት ካናንተ ጋር ይሆን!

አብዲ ሰዒድ

 
1 Comment

Posted by on January 24, 2013 in ስብጥርጥር

 

ሰውና መኪና . . .

♫… ይላል ዶጁdodg
ይላል ዶጁ
ፏ!… ፏ!… ይላል ዶጁ
ደስ የሚለኝ ሾፌር መልከመልካም ልጁ
እኔስ እህቱ ነኝ ይብላኝ ለወዳጁ
ፏ!… ፏ!… ይላል ዶጁ
ፏ!… ፏ!… ይላል ዶጁ …

ይላል ዶጁ …
ፈገግታውን ጋብዞ … አንዴ ቢያናግረኝ
ይህም አለ ለካ … መውደዱ ጀመረኝ
ልክ እንደመኪናው … እያሽከረከረ
ሹፌር ነው የኔ ፍቅር … ልቤን ያበረረ … ♫

መቼም ይህ የነጻነት መለሰ ዘፈን ቆየት ባለው ጊዜ ሹፌር እና ለፍቅር ተመራጭነት ያላቸውን ዝምድና እንድታብሰለስል ያደርግሃል… አንድ ትንሽ እድሜው ገፋ ያለ ጎልማሳ አግኝተህ “እንደው ግን ሾፌር እንዲህ ተወዳጅ ነበር እንዴ? ነው ወይስ ዶጅ የሚባለው አሜሪካን ሰራሽ መኪና ለኢትዮጵያ አዲስ ስለነበረ ነው?” ብለህ ብትጠይቀው… “እንዴ ምን ነካህ?!… ያኔ’ኮ ሹፍርና ማንም ዘሎ ያልጠገበ ወጠጤ ዘው ብሎ የሚገባበት ሙያ አይደለም!… ረጋ፣ ሰከን!… ኮራ፣ ቀብረር ያለ!… ኮረዶቹ ሁሉ የሚዋልሉለት ቄንጠኛ ጠምበለል የሚመርጠው ሙያ እንጂ!… እንዲህ እንደዛሬው በስድብና በዘለፋ ተክነህ የምትሞላፈጥበት እንዳይመስልህ… ዶጅህን ፏ!… ፏ!… እያደረግክ በሸገር ጎዳና ስትፈስ የስንቷ የሰከነች ቆንጆ ልብ አብሮ ሲፈስልህ እንደሚውል ባየህ… እስቲ ስማው ዘፈኑን…. ስማው ዘፈኑን…” እያለ ወዳሽከረከራት ዶጅና ወዳበረራት ኮረዳ በትዝታ ሲከንፍ… ዘመንህን አፈር ድሜ ማስጋጡ እያብሰለሰለህ ከነጻነት መለሰ ጋር ትቀጥላለህ . . .

♫… ቤትሽ የት ነው አለኝ አልኩት አራት ኪሎ
በየት በኩል ቢለኝ ትንሽ ወረድ ብሎ
መቼ ልምጣ አለኝ ጧትም ማታ
ምን ለብሼ ቢል ሱፍ ካቦርታ
ምን ይዤልሽ ቢል ቸኮላታ
የምጠጪው ቢል አረንቻታ

አረንቻታ… አረንቻታ
ሿ!.. ሿ!… አረንቻታ
በምሽት ጨረቃ ለብሰህ ውብ ካቦርታ
ከቸርችል ጎዳና ገዝተህ ቸኮላታ
ናልኝ ማታ ማታ …

አረንቻታ…
ትንፋሹ ቸኮላት … ጽጌሬዳ ቃና
ልቤን ይዞት ሄዶ … መች ተመለሰና
ጠይም አሳ መሳይ … ውብ አነጋገሩ
ሙያውና ፀባይ … ዉበቱ ማማሩ …♫

እያለች አራዳዋ ነፂም ይዛህ ጭልጥ ትላለች… ወዳማታውቀው፣ ወዳልኖርከው ዘመን ታከንፍሃለች… ምን ምን እንደሚል ጣዕሙን ሳታውቀው አረንቻታ መጠጣት ያምርሃል… “አረንቻታ!… አረንቻት… ሿ!… ሿ!… አረንቻታ…” እያልክ አብረሃት ትዘፍናለህ… ያልኖርክበት ዘመን ይናፍቅሃል… ዶጅ መንዳት ያምርሃል… ሱፍ ካቦርታ ስትደርብ ይታይሃል… ፏ!… ፏ!… ማለት ይቃጣሃል… ቸኮላት ግዛ ግዛ ይልሃል (የምትሰጣት ኮረዳ ባትኖርም)… ቸኮላት ቸኮላት ያሰኝሃል… ቸርችል ጎዳና ይመጣብሃል… ቸኮላት ለመግዛት ጎዳናውን ትያያዘዋለህ…. ትወጣዋለህ ወደ እምዬ ፒያሳ… ወደ አራዶቹ መንደር…

በጉዞህ ውስጥ ከቸኮላት ይልቅ በመደዳ የተደረደሩትና ለገበያቸው መድራት ሟችን የሚናፍቁት የሬሳ ሳጥን መሸጫ ሱቆች ያዛጉብሃል… ያላዝኑብሃል… ያፋሽኩብሃል… በአበባ እና በቀለማት አሸብረቀው ሟችነትህን ያሳስቡሃል… ሳታስበው ሿ!… ሿ!… ማለትህን ይነጥቁሃል… ሞት ሞት ይሸትሃል… የማሽከርከር ምኞትህ ብን ብሎ ይጠፋብሃል… አሁን ባንተ ዘመን ደግሞ ማሽከርከርና ሞት ያላቸውን ዝምድና ያስታውሱሃል… “እንትን መኪና ተገለበጠ… ይሄን ያህል ሰው ተጎዳ… ይሄን ያህል ሰው ሞተ…. መኪኖች ተጋጩ፣ ገደል ውስጥ ገባ!”… ምናምን የሚል ዜና ያስበረግግሃል…

መቼም አሁን ባለንበት ዘመን የመኪና አደጋን ወሬ መስማት የለት ተዕለት ተግባር ያህል የለመድነው ክስተት እየሆነ ነው… ሁሌም ግን እንደ አዲስ ያስደነግጠናል… ያስጨንቀናል… ያስበረግገናል… አሁን በሰሞኑ የሰማነው ዜና ብቻውን እጅጉን ያሳዝናል!…

በረጅም ርቀት የሩጫ ውድድር (በማራቶን)የሚታወቀውና በናዝሬት ከተማ ተወልዶ ያደገው የ 27 አመቱ አትሌት አለማየሁ ሹምዬ በመኪና አደጋ ህይወቱ እንዳለፈች ሰምተናል… እጅግ ያሳዝናል… አትሌት አለማየሁ በ2008 በጣልያኗ Vercelli ከተማ ዓለም አቀፍ የማራቶን ውድድሩን በቀዳሚነት በማሸነፍ ጀምሮ በፖላንድ፣ በቤይሩት እና በሌሎች አገሮች ከማሸነፉም በላይ በፍራንክፈርት፣ በሮተርዳም እና በሌሎች ከተሞችም ባስመዘገባቸው ጥሩ ሰአቶች ብዙ ተስፋ የነበረው ወጣት ነው… እንደ ግለሰብ ቤተሰቦቹን፣ ጓደኞቹን፣ አጋሮቹንና ዘመዶቹን አጉድሏል… እንደ አገርም ብርቱ ተስፋ የነበረውን አትሌት ማጣት ብዙ ያጎድላል… ለቤተሰቦቹና ለወዳጆቹ መጽናናትን ይስጥልኝ…

ከዚህ በፊትም እንደ አለባቸው ተካ አይነት ውድ ሰዎችን በተመሳሳይ አጥተናል… በየቤቱ የጎደለውን፣ የተጎዳውን ቤቱ ይቁጠረው… በ’ርግጥ የአደጋ መንስዔ የሾፌር ችግር ብቻ አይደለም… ብዙ ለአደጋ የሚያጋልጡ ምክኒያቶች ይኖራሉ… ቢሆንም ግን እላለሁ አሽከርካሪዎች ያለባችሁን ከባድ ሃላፊነት በአግባቡ ተወጡ“ ከመሞት መሰንበት” ደግ ነውና… የሚመለከታችሁ አካላትም በወገን ነፍስ አታላግጡ…

♫… ቤቴ ከመንገድ ዳር … ካውራጎዳናው ነው
በጡሩምባህ ጠርተህ … ነይ ብትለኝ ምነው
በኔ አልተጀመረም … ሰውን ሰው መውደድ
ፏ!… ፏ!… ብለህ ጥራኝ … ልምጣ ከመንገድ… ♫

እያለች መንገድ መንገድ እያየች ቸኮላትህንና አረንቻታህን ለምትጠብቅ ወዳጅህ መኪናህን ፏ!… ፏ!… አረንቻታህን ሿ!… ሿ!… እያደረግክ በሰላም ግባላት!

መልካም መንገድ !
አብዲ ሰዒድ

 
Leave a comment

Posted by on January 14, 2013 in ስብጥርጥር

 

የ’ኔ አምባሳደር . . .


Image

በድሬዳዋ ከተማ ተወልዳ ያደገችው፣ በ17 አመቷ ብሄራዊ ትያትርን የተቀላቀለችው፣ ዘፋኝ፣ ዳንሰኛ፣ የፊልም ተዋናይት፣ የውዝዋዜና የዳንስ አሰልጣኝ የሆነችው… በተለያዩ ሃገራት በተለይም በአውሮፓ ጥንቅቅ አድርጋ ኢትዮጵያዬን በጥበብ ስራዎቿ የምታወድስልኝ ምንይሹ ክፍሌ ለ’ኔ የባሕል አምባሳደሬ ናት!…

“መባ” በተሰኘው የመጀመሪያ አልበሟ (Mosaique Vivant − 2002 ) በኔዘርላንድ፣ በጀርመን፣ በቤልጂየም እና መሰል የአካባቢው አገሮች ዝናን ያተረፈችው፣ በተገኝችባቸው መድረኮች ሁሉ የአገራችንን የተለያዩ ባህሎች፣ ቋንቋዎች እና ሌሎች ገጽታዎች ለማስተዋወቅ የማትደክመው ምንይሹ በ’ርግጥም ለ’ኔ የባህል አምባሳደሬ ናት!…

ከኢትዮጵያ፣ ከማሊ፣ ከሱዳን፣ ከዲሞክራቲክ ኮንጎ፣ ከኔዘርላንድ፣ ከአሜሪካ እና ከሌሎች አውሮፓ አገራት በተውጣጡ ሙዚቀኞች ታጅባ የኢትዮጵያ ሙዚቃ በሌላውም የአለም ክፍል ተደማጭነትን እንዲያገኝ (አለም አቀፋዊ መልክ እንዲኖረው) የበኩሏን ለማበርከት የምትዳክረው ምንይሹ በኔ ልኬት ደርጃ ከምሰጣቸው (ምንም እንኳ የሙዚቃ ባለሙያ በልሆንም − እንደ አድማጭ) የኢትዮጵያም ብቻ ሳይሆን የአፍሪካ የሙዚቃ አምባሳደሮች አንዷ ናት!…

“ድሬዳዋ” በተሰኘው ሁለተኛ አልበሟ (Me and My Record 2008) በ2008 በአውሮፓ የዓለም የሙዚቃ ሰንጠረዥ ከምርጥ አስር አልበሞች አንዱ ለመሆን የበቃችው… በአማርኛ ከሚታተሙ የአገር ውስጥ የህትመት ውጤቶች በተጨማሪ በደች፣ በቱርክ፣ በጀርመን እና በሌሎች ሃገሮች በእንግሊዘኛና በየሃገሮቹ ቋንቋዎች በሚታተሙ ጋዜጦችና መጽሄቶች ስለሙዚቃዋ ዓለም አቀፋዊነት ከፍተኛ ሽፋን ያገኘችው ምንሹ በ’ርግጥም የሁልግዜም የባሕል አምባሳደሬ ናት!…

17 የተለያዩ አለም አቀፍ አርቲስቶች በተሳተፉበት፣ ስለ ዉሃ ብቻ በተቀነቀነውና በአለም ላይ ለሚገኙና በንጹህ ውሃ እጥረት ህይወታቸው በአጭር ለሚቀጭባቸው ህጻናት የንጹህ ዉሃ ያለህ ሁላችንም ያቅማችንን እናበርክትላቸው ዉሃ… ዉሃ… ዉሃ… ስትል ከሌሎች ዓለም አቀፍ አርቲስቶች ጋር ያቀነቀነችው ምንይሹ በግጥሙ መልዕክት ብቻ ሳይሆን በሙዚቃዊ ደረጃዋም ልቤን ታጠፋዋለችና ለኔ ከጥቂት ምርጦቼ አንዷ ናት!…

ሰላም ለህጻናት፣ ሸማኔው ደጉ፣ ዉሃ ዉሃ፣ ወሰንኩ፣ እንዲሁም የዲ የዲ በጉራጊኛ፣ ኤ ሃማማ በሲዳሚኛ፣ በወላይትኛ፣ በኦሮሚኛ እና በሌሎች የአገራችን ቋንቋዎች ስለ ባህሎቻችን ስፋትና ጥልቀት ለማስተዋወቅ የምትለፋው ምንይሹ፣ ቡና ቡና ስትል የቡና መገኛዋን ከፋ ደረጃውን በጠበቀ ሙዚቃ የምታወድስልኝ ምንይሹ፣ ከኢትዮጵያም አልፋ አፍሪካዬ ስትል ለአፍሪካ ያቀነቀነችልኝ ምንይሹ፣ በአፍሪካ ምድር ጦርነት ይቁምልን፣ ሰላም ይስፈንልን ስትል ጮክ ብላ ተምትጣራው ምንይሹ በርግጥም ለ’ኔ የሰላም አምባሳደሬ ናት!…

ከነ Oumou Sangare, Salif Keita, Angelique kidijo, ከነጂጂ እና ከሌሎች ምርጦች ጋር በአንድ መደዳ አስቀምጬ የማደምጣት ምንይሹ ለ’ኔ በርግጥ አምባሳደሬ ናት!… በቅርብ የሚለቀቀው “ጥቁር ቀለም” የተሰኘው አልበሟ እንዴት እንደናፈቀኝ…
ጥቁር ቀለም…

♫ … ዮጵያ… ኢትዮጵያዬ
…. ዮጵያ… ኢትዮጵያዬ…

ጥቁር ቀለም ፈሶ ምድርሽን ሲሞላው
በተራራ ሜዳ በጫካ በዉሃው
ልዩ ታሪክ ያለሽ የራሳችን ድርሻ
ኩራት የዘላለም ቅኔ ነሽ ሐበሻ . . . ♫

Love you Minyeshu …
http://www.minyeshu.nl/

 
Leave a comment

Posted by on December 25, 2012 in ስብጥርጥር