RSS

Monthly Archives: October 2013

ተስፋ ስንት ያወጣል?!

 

ሰው በሰው ጨክኖ ቀን ሲለብስ ጥቀርሻ
ሕልሙ የጨለመበት ያስሳል መሸሻ
እግሩን ተከትሎ
ተስፋን አንጠልሎ
አዲስ ቀንን ስሎ
በሄደበት መንገድ በጀመረው ጉዞ
ወየው ማለት ሆነ እሬሳውን ይዞ።

ወየው!… ወየው!… ወየው!…
ሰዉስ ስንቱን አየው …

ተስፋ ስንት ያወጣል ምንድነው ተመኑ?
በይሆናል ምኞት ስንቶቹ ባከኑ
ስንቱ መንገድ ቀረ… ስንቶቹ ረገፉ?!
ስንቶቹ ሰመጡ… ስንቶች ተቀጠፉ?!

ዋይታ ብቻ ሆነ ዝምምም ብሎ ለቅሶ
ለድጋፍ የሚሆን ጉልበታችን አንሶ
አቅማችን ኮስሶ
በደላችን ብሶ . . .

እንጉርጉሮ ቢወርድ ቢደረደር ሙሾ
በግፍ ለጨቀየው ለዚያ ለቂም ቁርሾ
ላይሆን መተንፈሻ ሃዘን ማስታገሻ
ለከሰሉ ነፍሶች የእምባ ስር ማበሻ

በቃኝ ማለቃቀስ
እምቢኝ ወይኔ ወይኔ
የትም አይቅርብኝ ቸር ይደር ወገኔ።

አጥንቱ አይቆጠር አይለቀም አፅሙ
በቀለም በገፁ አይለይ በስሙ
ለክቡር ሰው ገላ ወፎች አይሻሙ
አይብላው አሞራ
አይከታትፈው አውሬ
ዝም አትበይ ተነሽ!… እሪ በይ አገሬ !!!

ተስፋ ስንት ያወጣል ምንድነው ተመኑ?!
በይሆናል ምኞት ስንቶቹ ባከኑ
ስንቱ መንገድ ቀረ… ስንቶቹ ረገፉ
ስንቶቹ ሰመጡ … ስንቶች ተቀጠፉ?!…
__________________
__________________

በይሆናል ተስፋ…. በይሳካል ተስፋ… በየበረሐው ለሚባክኑና ለባከኑ ነፍሶች!!
ሰላም ፍቅርና ሕብረት ከለሁላችን ጋር ይሁን!!!

አብዲ ሰዒድ
ብጥስጣሽ ሃሳቦች (bT’sT’ash) . . .

Image

 
Leave a comment

Posted by on October 20, 2013 in ግጥም

 

ዘ – ም – ዘ – ም !

 

በዚያ ሐሩር ምድር፣ በዚያ ጠፍ በረሐ
ከደም ተቆራርጠው የሰው ልጅና ውሃ
ሕይወት ልታከትም ተይዛ ገርገራ
በዘምዘም ጠብታ ሕላዌዋ በራ።

ሃጀር ተራወጠች ሰፍዋና መርዋ
ለአንድ ልጇ ጥማት መች ዛለ ገላዋ
እሪ በል እስማኢል አልቅስ ተንዘፍዝፈህ
በእንባህ ዘለላዎች በል ያዛት ቀስፈህ።

እናት ዓለም ልፊ፣ ወዲህ ወዲያ ቃኚ፤
ያንቺን ጥማት ሽረሽ፣
በአሸዋው ዳክረሽ፣
ለአብራክሽ ክፋይ፣ ለእስትንፋስሽ ባክኚ።

በመካከል ሩጪ፣ በላይ ተራመጂ
ከወደዚህ ማትሪ፣ ደግሞም ከዚያ ሂጂ፤
ጠብቂው በዓይንሽ፣
ፈልጊው በእግርሽ፣
ርሃብ ጥማትሽን ለልጅ ፍቅርሽ ማግጂ።

አንድ! ሁለት! ሶስት! አራት!
ጉልበት እያጠራት . . .
አምስት! ስድስት! ሰባት!
ሕልሟ እየራቀባት …
ቀልቧ እየሳሳባት …
እ – ና – ት!
አቤት እናት!

በዚያ ሐሩር ምድር፣ በዚያ ጠፍ በረሐ
ከደም ተቆራርጠው የሰው ልጅና ውሃ
በዘምዘም አገኙት የነፍስን ፍሰኃ።

በል እስማኢል ጠጣ፣ ሃጀር ሆይ ጥገቢ
ላንቺም ለልጅሽም ዘምዘምን መግቢ።
እፈሽው በእጅሽ፣
አዳርሽው በዓይንሽ፣
ርኪበት በነፍስሽ፣
በአሸዋ፣ በኮረት፣ ከልይው በድንጋይ
የ’ናትነትሽ ጥግ ዝንታለም እንዲታይ።

“ዞሚ!” … “ዝሚ!” … “ዞሚ!” …
ድምፅሽን አሰሚ!
ትውልድሽን ካድሚ።

ተጓዥ መንገደኛው ይረፍ ባንቺ መንደር
“ሻባእ” “ሻባእህ” እያለ መርካቱን ይናገር።
ኃይል ብርታት ይሁን ለመኖርሽ ተስፋ
የጤናሽ ምልክት ይኑር እንዳይጠፋ።

“ዞሚ!”… “ዝሚ!”… “ዞሚ!”
ድምፅሽን አሰሚ!
ዓለምሽን ካድሚ።
___________
2006 E.C
አብዲ ሰዒድ
ኡፕሳላ፣ ስውዲን

HAPPY EID TO ALL MUSLIMS
❤ EID MUBAREK ❤

Image

 
2 Comments

Posted by on October 15, 2013 in ግጥም