RSS

Monthly Archives: January 2013

እግር ኳሳችን . . .

እኛና ተሳትፎ . . .  budinachen

ኢትዮጵያችን በአፍሪካ ዋንጫ ውድድር የመጨረሻዋን ተሳትፎ ያደረገቸው በ1982 (እ. አ. አ) በሊቢያ ተካሂዶ በነበረው 13ኛው የአፍሪቃ ዋንጫ ውድድር እንደነበር ሰምተናል… እነሆ ከ31 አመት በኋላም ክብራችንን ለመለሱልን ዋልያዎቹ የላቀ ፍቅርና ምስጋናችንን እያዥጎደጎድን እንገኛለን… ከዚህም በላይ ይገባቸዋል!… የሽንፈት ከራማችንን እንደገፈፋችሁት በክፉ የሚያያችሁ ከራማው ይገፈፍ አቦ!… 

መሃመድ አሊ ሸዳድ . . . 

ኢትዮጵያችን ከተሳተፈች 31 አመታት ይቆጠሩ እንጂ በአፍሪካ ዋንጫ ውድድር ላይ ግብ ካስቆጠረች 37 አመታትን ቆርጥማለች… የመጨረሻ ጎሏን ያስቆጠረችው በ1976 (እ. አ. አ) አዲስ አበባ ላይ በኢትዮጵያ አዘጋጅነት ተካሂዶ በነበረው 10ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ውድድር ላይ ነበር… ይህች የመሃመድ አሊ (ሸዳድ) ጎል በወቅቱ ኢትዮጵያን ከግብጽ ጋር 1 ለ 1 በሆነ አቻ ውጤት እንዲለያዩ ያስቻለች ነበረች… 

አዳነ ግርማ . . . 

አገራችን ለመጨረሻ ጊዜ ባፍሪካ ዋንጫ ጎል ስታስቆጥር አዳነ ግርማ አልተወለደም ነበር… ኧረ ገና አልታሰበም!… እየተሰቃየንበት የከረምንበትን የጎል ረሃብ፣ የጎል ጥማት፣ የጎል ድርቅ ድራሹን ስላጠፋልን… ታሪካችንን ስለቀየረልን… በ’ርግጥ የትኛውም አይነት ሙገሳ ይገባዋል… ከንግዲህ የሸዳድ ጎል ቅርስ ብቻ ተደርጋ መወራቷ አብቅቷል… ከ’ንግዲህ በእግር ኳስ ተስፋ የራቃት ኢትዮጵያ እየጠፋች ነው… ከ’ንግዲህ የኳስ ተስፋዋ እየለመለመ ነው… 

በየሰፈሩ የኳስ ፍቅር ያላቸው ታዳጊ ልጆች በወኔ ኳስ እያንከባለሉ እንደሆነ እናምናለን… እንደ አዳነ፣ እንደ ሰለሃዲን፣ እንደ ጌታነህ፣ ባጠቃላይ እንደ ዋሊያዎቹ ዝናቸው እንዲወራ እየተመኙ እንደሆነ ጥርጥር የለኝም!… እነዚህን ልጆች አቅማቸውን ተረድቶ የሚደግፋቸው… በአግባቡ የሚንከባከባቸው እስካለ ድረስ ገና ብዙ ታሪክ ይሰራል!… 

መሃመድ ኡስማን (ሚግ) . . . 

መሃመድ ኡስማን (ሚግ)… 😦 … ልክ የዛሬ 31 አመት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የጊኒን ብሔራዊ ቡድን አሸንፎ ለአፍሪካ ዋንጫ እንዲያልፍ ያስቻለ ሰው ነበር (ነፍሱን አላህ በጀነት ያኑርልንና)… ይህ ከድሬዳዋ የተገኘ ምርጥ የእግር ኳስ ተጫዋች በጣም ፈጣን ከመሆኑ የተነሳ ሚግ በሚለው ቅጽል ስሙ ይታወቃል… እነሆ ከ’ሱ በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫ ሊያስገባን የሚችል ጎል ማስቆጠር ተስኖን 31 አመታት ጠብቀናል… ስለምን ግን 31 አመታት ፈጀብን?… እውን የጥንቶቹን ያህል ተጫዋቾች ማፍራት አቅቶን ነበርን?!… ብለን ብንጠይቅ የዚህ ሰው ታሪክ በከፊል ጥያቄያችንን ይመልስልናል… 

ይህ ለአገር ታላቅ ውለታ የሰራ ሰው ህይወቱ ያለፈው የመከራን ጽዋ እንደተጋተ ነበር… ለዚህ አኩሪ ታሪኩ ኢትዮጵያችን የከፈለችው እስር… ርሃብ… እርዛት…. መገፋት… እና ጎዳና ላይ ማደርን ነበር… ኢትዮጵያን የምታህል ታላቅ አገር ለአፍሪካ ዋንጫ ውድድር ያበቃ ሰው በረንዳ እያደረ በረንዳ ላይ ሲሞት እያየ የትኛው ትውልድ ይሆን በተነሳሽነት ኳስ ሊጫወት የሚችለው?!…. ከቶም አይታሰብም!… ታሪክ መስራት የፈለገ ታሪክ ሰሪዎቹን ያከብራል!… አይከኖቹን ያልቃል!… 

ከሁለት ወይም ከሦስት አመት በፊት የስፖርት ጋዜጠኛው ሰኢድ ኪያር ለዚህ ድንቅ የኢትዮጵያ ልጅ እናትና ቤተሰቦች የተደረገን የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅት አስቃኝቶን ነበር (በነገራችን ላይ ጋዜጠኛ ሰኢድ ኪያር ታላላቅ ስፖርተኛቻችንን እንድናውቃቸው በምታደርገው ጥርት በበኩሌ እጅግ አድርጌ አመሰግንሃለሁ) እናም የተመለከትነው የቤተሰቦቹ የኑሮ ደረጃ በ’ርግጥም ያማል!…

እስቲ እሰቡት ከወራት በፊት ላፍሪካ ዋንጫ እንድናልፍ ያስቻሉንን ጎሎች ያስቀጠሩትና እንዲያ ያስቦረቁን… ዛሬም ያስፈነደቁን… ሳላሃዲን ሰኢድ ወይም አዳነ ግርማ ወይም ሌላ የቡድኑ ተጫዋች ተጎሳቁለው ጎዳና ወድቀው ቢታዩ በርግጥ ኢትዮጵያችን አትጎሳቆልምን?… ኧረ ክፉ አይንካቸው!…

እናም እላለሁ አሁን ያገኘነው ክብር ይቀጥል ብሎም የተሻለ ስኬት በዘላቂነት እናስመዘግብ ዘንድ ባለታሪኮቻችንን እናክብር … ታላቁን ያወቀ… የታላቁን ስራ ያከበረ… ከታላቁ ስህተት የተማረ… በ’ርግጥም ታላቅ ነገር መስራት ይቻለዋልና!… መሃመድ ኡስማን ከ 8 አመት በፊት እንዳዘነብን፣ እንደተከፋብን፣ በረሃብና በእርዛት አልፏል!… እሱን ማክበር እስከፈለግን ድረስ ግን ዛሬም ልናስበው እንችላለን…

በየተሰማሩበት የሙያ ዘርፍ ብርቱ ስራ የሰሩ ክብር ብሎም የተሻለ ኑሮ የሚገባቸው ብዙ ሰዎች ዛሬም አሉን… እናም አይናችንን ገልጠን እንመልከታቸው… እናመሰግናለን… እናከብራችኋለን… እንወዳችኋለን…. እንበላቸው!… እነሱን ስናከብር ኢትዮጵያችንን ትከብራለችና!… 

“ምን በደስታ ሰዓት ያላዝንብናል?”… የሚለኝ ቢኖር ልክ ነው!… ጊዜው የደስታ እንጂ የማስለቀሻ እና የችግር ወሬ የመዘብዘቢያ አይደለምና!… በደስታው ወቅት ደስታውን እንዴት ማስቀጠልና እንዴት ተደጋጋሚ ደስታን ማጣጣም እንደሚችል የሚያውጠነጥን ግን በ’ርግጥ ነገም ደስተኛ ይሆናል!… 

እንደው ተምሳሌት ስለ ሆኑ ሰዎች ካወራን አይቀር በነካ እጃችን የሙዚቃችንን ባለውለታ የሆነውን Abebe Melesse-አበበ መለሰንም እናስበው እስቲ!… ሁለቱም ኩላሊቶቹ ታመው ድጋፍ ፍለጋ ላይ ነው… ሁለት ብር ለሁለት ኩላሊቶቹ!… ሞባይሎን 832 ላይ ይጫኑ ከዚያም Z የሚል መልዕክት ይጻፉ… አቤን ያድኑ… በሙዚቃው ይዝናኑ… 

ክብር ለዋሊያዎቹ!… 
ዘላቂ እድገት ለእግር ኳሳችን!…. 
ብርቱ ጥንካሬና መልካም ውጤት ካናንተ ጋር ይሆን!

አብዲ ሰዒድ

 
1 Comment

Posted by on January 24, 2013 in ስብጥርጥር

 

ጸሎት ወ ዱዓ . . .

*** . . . አሃዱ ጸሎት . . . *** SA 29

በዕለተ አርብ ቀን፣ በዕለተ ከተራ፣
ለጥምቀት ዋዜማ፣ ወገን ሲጠራራ፣
ባንድ እየዘመረ፣ 
ባንድ እየጨፈረ፣
ሎሚ፣ ከረሜላ እየወረወረ …
በጸሎት ሊያነጋ፣ ውርጭ እየደፈረ፣
ሕዝበ ክርስቲያኑ፣ ጃን ሜዳ ሲያቀና፣
በክብሩ ማረፊያ፣ አዳሩን ሲያፀና፣
ለማለዳው ፀበል፣ ለግፊያው ሲዘጋጅ፣
ዋልያው ተጓዘ፣ ላገር ክብር ግዳጅ፡፡

ባህረ ጸበሉን፣ በፍቅር ተራጭቶ፣
ጽላቱን በክብር፣ ከደብሩ ሸኝቶ፣
ቃና ዘገሊላን፣ በጸሎት ተደፍቶ፣
የውስጠቱን መሻት፣ ላምላክ አስረድቶ፣
ጉዳዩ እንዲሞላ፣ በእምነት ተሞልቶ
ባሳለፈ ማግስት፣ በቀን መጀመሪያ፣
በዕለተ ሰኞ፣ ድል ይሁን ለኢትዮጵያ፡፡

እግዜር ያግዛችሁ፣
እግዜር ያበርታችሁ፣
ስንቱ በየደብሩ፣ ስለት ገባላችሁ፡፡

*** . . . ክልኤቱ ዱዓ . . . *** 

በዕለተ አርብ ቀን፣ በየውመል ጁመዓ፣
መስጂድ ተሰባስቦ፣ ወገን ሲያደርግ ዱዓ፣
ያ ረቢ!… ያ ረቢ!…
አትበለን እምቢ !
ብርቱ ሃጃ አለብን፣ ሕዝብ ፊት አቅራቢ፣
ʻድምፃችን ይሰማ!… ድምፃችን ይሰማ!ʼ…
ጥረት ልፋታችን፣ ከንቱ እንዳይታማ፡፡

የረሱል መከታ፣ መጠጊያና ጋሻ፣
የቢላል የዘር ግንድ፣ የቸር መናገሻ፣
የኡሙ አይመን ምድር፣ ፍቅር መጨረሻ፣
የሶሃቦች ደጀን፣ የክፋት ማርከሻ፣
የነጃሺ ቀዬ፣ የእምባችን ማበሻ፣
ለሆነችው ምድር፣ እናት ኢትዮጵያ
ያ ረቢ አደራህን፣ አግዛት በፍልሚያ፡፡

አላህ ያግዛችሁ፣
አላህ ያበርታችሁ፣
ሸሆች በየመስጂድ፣ ዱዓ ያዙላችሁ፡፡

*** . . . ሰልስቱ ፍቅር . . . ***

ኑሮ አልሞላ ብሎ፣ ድህነት ቢገፋኝ፣
አሊያም ፖለቲካው፣ ሰው አገር ቢደፋኝ፣
ምን ብኖር እርቄ፣ ወገኔን ናፍቄ፣ 
ለአገሬስ ልጆች፣ ወጣለሁ ደምቄ፡፡

ዘር ማንዘር አልቆጥርም፣
ሃረግ አልመትርም፣
ቡትለካውም የለኝ፣ በከንቱ አልዘምርም፤
አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ አርማዬን ይዤ፣
ዘመን የወለደው፣ ተስፋዬን አርግዤ፣

አለሁ ከጎናችሁ፣ 
የአገሬ ልጆች ብርታት አይራቃችሁ
ኧረ እንኳን በደህና በሰላም መጣችሁ፡፡

__________ // _________

አብዲ ሰዒድ
ስኬት ለብሔራዊ ቡድናችን!

ፎቶ ምንጭ: @ Dimitru (Facebooker), www.DireTube.com, EthioTube

 
Leave a comment

Posted by on January 18, 2013 in ግጥም

 

ያ ሆ… ‘ምቦምቤላ! . . .


በማዲባ ምድር፣ በአቦይ ማንዴላ፣africa cup
በፈርጡ ስቴዲየም፣ በዚያ በ’ምቦምቤላ፣
ያ ሆ በል! ያገር ልጅ፣ በል የ’ርግብ አሞራ፣
ለኩራት ለክብርህ፣ ለእትብትህ ባንዲራ፡፡

ጉሮ ወሸባዬ፣ ጉሮ ወሸባዬ፣ 
ቀና በይ ካንገትሽ፣ እናት ኢትዮጵያዬ፣
ዝናሽ ያንሰራራ፣ ክብርሽ ይድነቃቸው፣
የከርሞ ታሪክሽ፣ ሃይል ይሁን ስንቃቸው፡፡

በቼልፊኮ ጫማ፣ እግር እየደማ፣
በእናት አገር ፍቅር፣ ልብ እየተጠማ፣
ስንት ታሪክ ታየ፣ ስንት ጉድ ተሰማ፡፡ 

ኢታሎ ቫሳሎ፣ ሉችያኖ ቫሳሎ፣
መንግስቱና ግርማ፣ ዝናቸው ከፍ ብሎ፣
ለዘመን ያደረ፣ 
ለአፍ የከበረ፣ ታሪክ እንደጻፉ፣
የዛሬም ልጆችሽ፣ ክብርሽን ያትርፉ፡፡

አዳነ፣ ሳላሃዲን፣ ሳላሃዲን፣ አዳነ፣
አገር ከህመሙ፣ በናንተ እግር ዳነ፣
እንግዲህ ይቅናችሁ፣ ብርታት አይራቃችሁ፣
ሴሌሜ ሴሌሜ፣ በቸር ያድርሳችሁ፡፡

“ሴሌሜ ሴሌሜ፣ ሆ ያ ሴሌሜ፣”
በዋልያ ፍቅር፣ አለሁኝ ታምሜ፤
“ሴላ፣ ሴላ፣ ሴላ፣ 
ሴላላላ ላ ሚያ” 
ድል ካንቺ ጋር ይሁን እናት ኢትዮጵያ፡፡

__________ // __________

© አብዲ ሰዒድ 
ጥር፣ 2005 E.C
shegerewa@gmail.com

 
Leave a comment

Posted by on January 17, 2013 in ግጥም

 

ሰውና መኪና . . .

♫… ይላል ዶጁdodg
ይላል ዶጁ
ፏ!… ፏ!… ይላል ዶጁ
ደስ የሚለኝ ሾፌር መልከመልካም ልጁ
እኔስ እህቱ ነኝ ይብላኝ ለወዳጁ
ፏ!… ፏ!… ይላል ዶጁ
ፏ!… ፏ!… ይላል ዶጁ …

ይላል ዶጁ …
ፈገግታውን ጋብዞ … አንዴ ቢያናግረኝ
ይህም አለ ለካ … መውደዱ ጀመረኝ
ልክ እንደመኪናው … እያሽከረከረ
ሹፌር ነው የኔ ፍቅር … ልቤን ያበረረ … ♫

መቼም ይህ የነጻነት መለሰ ዘፈን ቆየት ባለው ጊዜ ሹፌር እና ለፍቅር ተመራጭነት ያላቸውን ዝምድና እንድታብሰለስል ያደርግሃል… አንድ ትንሽ እድሜው ገፋ ያለ ጎልማሳ አግኝተህ “እንደው ግን ሾፌር እንዲህ ተወዳጅ ነበር እንዴ? ነው ወይስ ዶጅ የሚባለው አሜሪካን ሰራሽ መኪና ለኢትዮጵያ አዲስ ስለነበረ ነው?” ብለህ ብትጠይቀው… “እንዴ ምን ነካህ?!… ያኔ’ኮ ሹፍርና ማንም ዘሎ ያልጠገበ ወጠጤ ዘው ብሎ የሚገባበት ሙያ አይደለም!… ረጋ፣ ሰከን!… ኮራ፣ ቀብረር ያለ!… ኮረዶቹ ሁሉ የሚዋልሉለት ቄንጠኛ ጠምበለል የሚመርጠው ሙያ እንጂ!… እንዲህ እንደዛሬው በስድብና በዘለፋ ተክነህ የምትሞላፈጥበት እንዳይመስልህ… ዶጅህን ፏ!… ፏ!… እያደረግክ በሸገር ጎዳና ስትፈስ የስንቷ የሰከነች ቆንጆ ልብ አብሮ ሲፈስልህ እንደሚውል ባየህ… እስቲ ስማው ዘፈኑን…. ስማው ዘፈኑን…” እያለ ወዳሽከረከራት ዶጅና ወዳበረራት ኮረዳ በትዝታ ሲከንፍ… ዘመንህን አፈር ድሜ ማስጋጡ እያብሰለሰለህ ከነጻነት መለሰ ጋር ትቀጥላለህ . . .

♫… ቤትሽ የት ነው አለኝ አልኩት አራት ኪሎ
በየት በኩል ቢለኝ ትንሽ ወረድ ብሎ
መቼ ልምጣ አለኝ ጧትም ማታ
ምን ለብሼ ቢል ሱፍ ካቦርታ
ምን ይዤልሽ ቢል ቸኮላታ
የምጠጪው ቢል አረንቻታ

አረንቻታ… አረንቻታ
ሿ!.. ሿ!… አረንቻታ
በምሽት ጨረቃ ለብሰህ ውብ ካቦርታ
ከቸርችል ጎዳና ገዝተህ ቸኮላታ
ናልኝ ማታ ማታ …

አረንቻታ…
ትንፋሹ ቸኮላት … ጽጌሬዳ ቃና
ልቤን ይዞት ሄዶ … መች ተመለሰና
ጠይም አሳ መሳይ … ውብ አነጋገሩ
ሙያውና ፀባይ … ዉበቱ ማማሩ …♫

እያለች አራዳዋ ነፂም ይዛህ ጭልጥ ትላለች… ወዳማታውቀው፣ ወዳልኖርከው ዘመን ታከንፍሃለች… ምን ምን እንደሚል ጣዕሙን ሳታውቀው አረንቻታ መጠጣት ያምርሃል… “አረንቻታ!… አረንቻት… ሿ!… ሿ!… አረንቻታ…” እያልክ አብረሃት ትዘፍናለህ… ያልኖርክበት ዘመን ይናፍቅሃል… ዶጅ መንዳት ያምርሃል… ሱፍ ካቦርታ ስትደርብ ይታይሃል… ፏ!… ፏ!… ማለት ይቃጣሃል… ቸኮላት ግዛ ግዛ ይልሃል (የምትሰጣት ኮረዳ ባትኖርም)… ቸኮላት ቸኮላት ያሰኝሃል… ቸርችል ጎዳና ይመጣብሃል… ቸኮላት ለመግዛት ጎዳናውን ትያያዘዋለህ…. ትወጣዋለህ ወደ እምዬ ፒያሳ… ወደ አራዶቹ መንደር…

በጉዞህ ውስጥ ከቸኮላት ይልቅ በመደዳ የተደረደሩትና ለገበያቸው መድራት ሟችን የሚናፍቁት የሬሳ ሳጥን መሸጫ ሱቆች ያዛጉብሃል… ያላዝኑብሃል… ያፋሽኩብሃል… በአበባ እና በቀለማት አሸብረቀው ሟችነትህን ያሳስቡሃል… ሳታስበው ሿ!… ሿ!… ማለትህን ይነጥቁሃል… ሞት ሞት ይሸትሃል… የማሽከርከር ምኞትህ ብን ብሎ ይጠፋብሃል… አሁን ባንተ ዘመን ደግሞ ማሽከርከርና ሞት ያላቸውን ዝምድና ያስታውሱሃል… “እንትን መኪና ተገለበጠ… ይሄን ያህል ሰው ተጎዳ… ይሄን ያህል ሰው ሞተ…. መኪኖች ተጋጩ፣ ገደል ውስጥ ገባ!”… ምናምን የሚል ዜና ያስበረግግሃል…

መቼም አሁን ባለንበት ዘመን የመኪና አደጋን ወሬ መስማት የለት ተዕለት ተግባር ያህል የለመድነው ክስተት እየሆነ ነው… ሁሌም ግን እንደ አዲስ ያስደነግጠናል… ያስጨንቀናል… ያስበረግገናል… አሁን በሰሞኑ የሰማነው ዜና ብቻውን እጅጉን ያሳዝናል!…

በረጅም ርቀት የሩጫ ውድድር (በማራቶን)የሚታወቀውና በናዝሬት ከተማ ተወልዶ ያደገው የ 27 አመቱ አትሌት አለማየሁ ሹምዬ በመኪና አደጋ ህይወቱ እንዳለፈች ሰምተናል… እጅግ ያሳዝናል… አትሌት አለማየሁ በ2008 በጣልያኗ Vercelli ከተማ ዓለም አቀፍ የማራቶን ውድድሩን በቀዳሚነት በማሸነፍ ጀምሮ በፖላንድ፣ በቤይሩት እና በሌሎች አገሮች ከማሸነፉም በላይ በፍራንክፈርት፣ በሮተርዳም እና በሌሎች ከተሞችም ባስመዘገባቸው ጥሩ ሰአቶች ብዙ ተስፋ የነበረው ወጣት ነው… እንደ ግለሰብ ቤተሰቦቹን፣ ጓደኞቹን፣ አጋሮቹንና ዘመዶቹን አጉድሏል… እንደ አገርም ብርቱ ተስፋ የነበረውን አትሌት ማጣት ብዙ ያጎድላል… ለቤተሰቦቹና ለወዳጆቹ መጽናናትን ይስጥልኝ…

ከዚህ በፊትም እንደ አለባቸው ተካ አይነት ውድ ሰዎችን በተመሳሳይ አጥተናል… በየቤቱ የጎደለውን፣ የተጎዳውን ቤቱ ይቁጠረው… በ’ርግጥ የአደጋ መንስዔ የሾፌር ችግር ብቻ አይደለም… ብዙ ለአደጋ የሚያጋልጡ ምክኒያቶች ይኖራሉ… ቢሆንም ግን እላለሁ አሽከርካሪዎች ያለባችሁን ከባድ ሃላፊነት በአግባቡ ተወጡ“ ከመሞት መሰንበት” ደግ ነውና… የሚመለከታችሁ አካላትም በወገን ነፍስ አታላግጡ…

♫… ቤቴ ከመንገድ ዳር … ካውራጎዳናው ነው
በጡሩምባህ ጠርተህ … ነይ ብትለኝ ምነው
በኔ አልተጀመረም … ሰውን ሰው መውደድ
ፏ!… ፏ!… ብለህ ጥራኝ … ልምጣ ከመንገድ… ♫

እያለች መንገድ መንገድ እያየች ቸኮላትህንና አረንቻታህን ለምትጠብቅ ወዳጅህ መኪናህን ፏ!… ፏ!… አረንቻታህን ሿ!… ሿ!… እያደረግክ በሰላም ግባላት!

መልካም መንገድ !
አብዲ ሰዒድ

 
Leave a comment

Posted by on January 14, 2013 in ስብጥርጥር

 

ማርዬ . . .

ማርዬ አብሮ አደጌ የልጅነት ፍቅሬ፣maryee22
ማተብ ማንነቴ ነፃነቴ ክብሬ፣
እንዴት ነሽ ባያሌው እንዴት ነሽ አለሜ?!
አንቺ ቅን እመቤት የሌት ተቀን ህልሜ::

እኔ እንደሁ ከድቼሽ እምነትሽን ፍቄ፣
“በማሪያ” ፍቅር ላይ ላዩን ደምቄ፣
አለሁ በነጭ አለም ሰርክ አንቺን ናፍቄ::

ማርዬ … ?!

ድሮ ገና ያኔ ስትወጅኝ ስወድሽ ልባችን ሲጠፋ፣
በፍቅራችን ሰበዝ በዕምነት ስንደዶ ህይወትን ስንሰፋ፣
ጋራ ሸንተረሩ፣ ሜዳና ገደሉ፣ የአበቦቹ ሽታ፥
የመስኩ ላይ ውበት፣
የቀጠፍነው እሸት፣ ያ ውብ ሳቅ ጨዋታ፣
ሁሉም ትዝ እያለኝ እየዞረ ባይኔ
ይደጋግመኛል ባንቺ መብከንከኔ::

ግን እንዴት ነሽ ውዴ? እንዴት ነሽ አለሜ?!
ሰርክ የምትናፍቂኝ የውስጠት ህመሜ::
እኔ እንደሁ ከድቼሽ እምነትሽን ፍቄ
“በማሪያ” ፍቅር ላይ ላዩን ደምቄ
አለሁ በነጭ አለም ሰርክ ተጨንቄ::

ማርዬ … ?!

እኔ ወዲህ ልሸኝ ስትሰናበቺኝ፣
ቅዱስ ቃሉን ይዘሽ መፅሃፍ ስታስመቺኝ፣
ያንገትሽን ማተብ ባንገቴ ስታስሪ፣
የኔን ያንገት ማተብ
ከግማድሽ ጋራ በወግ ስትቋጥሪ፣
በበተስኪያን አፀድ ደውሉ እያስተጋባ፣
ላትከጂኝ ላልከዳሽ ቃል ስንገባባ፣
በአማልክት አጀብ ምዬልሽ ነበረ፣
እርሜን በላሁ እንጂ ቃሌ ተሰበረ::

ማርዬ እመቤቴ የልጅነት ፍቅሬ፣
እንዴት ነሽ ባያሌው ነፃነቴ ክብሬ፣
እኔ እንደሁ ከድቼሽ እምነትሽን ፍቄ፣
“በማሪያ” ፍቅር ላይ ላዩን ደምቄ፣
አለሁ በነጭ አለም ሰርክ ተሳቅቄ::

ማርዬ …?!

የነጃሺ አድባር፣
የሶሃቦቹ አጥንት፣
ጀማ ንጉስ መውሊድ ፣ የሸሆቹ ዱዓ፤
ቡራኬያቸው ደርሶ፣
እምነት ፅናት ለብሶ፣
ለፍቅራችን ፀዳል የሆነን “ሸፈዓ!”፤

የስጋ ወደሙን ምስጢረ አንድምታ፣
አብረን የጎረስነው በፆመ ፍልሰታ፣
ያጠጣሽኝ ፀበል ቀድተሽ በማለዳ፣
ሰርክ እየፈወሰኝ ከሚገጥመኝ ፍዳ፣
ሁሉም በልቤ አለ በደማቅ ተፅፎ፣
ዝንታለም ማይጠፋ አንቺነትሽ ገዝፎ::
ብቻ እንዴት ነሽ ውዴ እንዴት ነሽ አለሜ?!
ሰርክ ያማስታውስሽ የነፍስያ ህመሜ::
እኔ እንደሁ ከድቼሽ እምነትሽን ፍቄ
“በማሪያ” ፍቅር ላይ ላዩን ደምቄ
አለሁ በነጭ አለም ሰርክ ህልሜን ናፍቄ::

ማርዬ …?!

ግን እውነት ከድቼሽ?!
እኔ አንቺን ረስቼ፣ ትቼሽ ይመስልሻል?!
ዳሩ …!? መጥተሽ ካላየሽው …!
እንዴትስ ብነግርሽ እንዴት ይገባሻል!?
ብቻ ትዝ እንዳልሽኝ
ብቻ ት…ዝ…! እንዳልሽኝ 
… ዘመን ነግቶ ይመሻል::

እንኳን አንቺን ቀርቶ …
እንኳን አንቺን ቀርቶ …
የኩበት ጭስ ሽታ፣
የከብቶች ኳኳታ፣
የአህዮች ማናፋት ሁሉ ይናፍቀኛል፤
የእረኞች ፉጨት፣
የወፎች ዝማሬ፣
ቅዳሴና አዛኑ ሁሌም ውል ይለኛል::

ያ …! ደርባባ ፊትሽ፣
ትሁት አንደበትሽ ፣
ሽንሽን፣ መቀነትሽ፣
ነጠላ፣ ዘንቢልሽ፣ ጥላሽ በልቤ አለ፤
ህያው ማንነቴን፣
የፍቅር እመቤቴን፣
ማርዬን፣ ማርዬን፣ ማርዬን እንዳለ::

አንቺ ማለት እኮ!
ባህልና ቅርሴ፣
የዘር ማንዘር ውርሴ፣
ኩራትና ክብሬ፣
እትብት የደም ስሬ፣ እናት አገሬ ነሽ፤
ከውስጤ ነጥዬ፣ ቆርጬ ‘ማልጥልሽ::

ብቻ ግን እንዴት ነሽ እንዴት ነሽ አለሜ
ሰርክ የማስታውስሽ የዘውትር ህመሜ
እኔ እንደሁ ከድቼሽ እምነትሽን ፍቄ
“በማሪያ” ፍቅር ላይ ላዩን ደምቄ
አለሁ በነጭ አለም ሰርክ ተሳቅቄ::

____ / © አብዲ ሰዒድ 2004 E.C / ____
_______ / ኡፕሳላ፤ ስውዲን / _______

 
Leave a comment

Posted by on January 11, 2013 in ግጥም