RSS

Monthly Archives: May 2013

የዓለም ፀሐይ ዓለም . . .

ዓለም ፀሐይ ወዳጆ . . .

alem1
አርቲስት ዓለም ፀሐይ ወዳጆን የማያውቅ የጥበብ ቤተሰብ ይኖራል ብዬ አልገምትም… ከኖረም ከቲያትሩም፣ ከትወናውም፣ ከዘፈኑም፣ ከግጥሙም ዓለም ራሱን ያራቀ… በስሚ ስሚ ወሬ እንኳን በኪነ ጥበብ ዘርፍ ነፍሱን ያላፀደቀ መሆን አለበት… ዓለም ፀሐይ ዘርፈ ብዙ የሆነች የጥበብ ፈርጥ ናት!… የተውኔት ጸሐፊ፣ የቲያትር አዘጋጅ፣ ተዋናይ፣ ገጣሚ ከመሆኗም በተጨማሪ የኢትዮጵያ ሕጻናት ቲያትር መስራች እንዱሁም በውጭው ዓለም በተለይም በአሜሪካ ኢትዮጵያዊ የጥበብ ስራዎች ከኢትዮጵያዊያን ልቦች እንዳይጠፉ በብርቱ የምትንቀሳቀስ የጥበብ አድባር ናት!… ጣይቱ የጥበብ ማእከልን ይጠቅሷል…

የሷን የጥበብ ስራዎች በሙሉ ልዘረዝር አልተነሳሁም!… ሁሉም በየመስኩ እንደመልካቸው ለየብቻ ሊዘርዘሩና ሙያዊ ትንተና ሊሰጥባቸው የሚችሉ ናቸው… ስለ ትያትር ስራዎቿ ለብቻ… በመጽሃፍና በሲዲ ስላሳተመቻቸው ግጥሞቿ ለብቻ… ለበርካታ ዘፋኞች ስለሰጠቻቸው የዘፈን ግጥሞች ለብቻ.. እያልን ከጥበብ ባሕሯ ልንጨልፍ ይቻለናል!… እናም ይህ ጽሁፍ ትኩረት የሚያደርገው የዘፈን ግጥሞቿ ላይ ብቻ መሆኑን መግለጹ ያስፈልገኛል…

አብዛኞቻችን ብዙውን ጊዜ ትኩረት የምንሰጠው ለዘፋኞች እንጂ ለግጥምና ዜማ ደራሲዎችም ሆነ ለአቀናባሪዎች አይደለም… በእርግጥ ዘፈን የድምጽ ስራ በመሆኑ ዘፋኙን ማወደስና ማክበር የተገባ ነው… አንድ ሙዚቃ ሙሉእ ሆኖ ቀልብን እንዲገዛ የሁሉም አስተዋጽኦ የየራሱ ዋጋ እንዳለው መዘንጋቱ ግን የጥበብን ውህደት እንደመዘንጋት ይቆጠራል… ዜማ ያለ ግጥም… ግጥምም ያለ ዜማ… ሁለቱም ያለ ጥሩ ቅንብር ለመንፈስ እርካታን የሚለግስ ዘፈን ሊሰጡን አይቻላቸውም… ሶስትም አንድም እንደማለት ነው… የማይነጣጠሉ!… ዓለም ፀሐይ የምትታወቀው ውስጥ ዘልቀው በሚገቡ ግጥሞቿ ነው… እናም ግጥም ላይ ብቻ ትኩረት አደርጋለሁ…

ከወራት በፊት ስለ ዘፈን ግጥሞቿ አወራኋት… ባጋጣሚ ውይይታችንን የቀረጽኩበት ድምጽ መቅጃ ከጄ ወጣ… በሲዲ አሊያም በሌላ መሰል ነገር አልገለበጥኩትም ነበርና ተበሳጨሁ… በድጋሚ ላውራሽ ማለቱ ደግሞ እሷን ማድከም እንደሆነ ተሰማኝ… እፍረትም ሸንቆጥ አደረገኝ… እናም መልሼ እስካገኘው መጠባበቅ ግድ ሆነብኝና እስካሁን ቆየሁ… መቼም ቅር እንደማትሰኝብኝ እምነቴ ነው… ከራሷ የሰማሁትን ለማጠናቀር ስለፈለግኩ እንጂ በተባራሪ የሰማኋቸውን እንዲሁም ካሴቶች ላይ ያየኋቸውን ለቃቅሞ መጻፍ እንደሚቻለኝ ዘንግቼው አይደለም… ጊዜዋን ሰውታ ስለ ስራዎቿ ስላዋየችኝ እጅግ እያመሰገንኩ ከራሷ አንደበት የሰማሁትን በራሴ መንገድ ለመነካካት እሞክራለሁ…. እጅግ ከባድ ቢሆንም…

ከ400 በላይ የዘፈን ግጥሞች . . .

ስለ ሙሉ የዘፈን ግጥሞቿ በዚህ ጽሁፍ ለመዘርዘር መሞከር የማይታሰብ ነው… ምን ያህል ግጥሞች ለምን ያህል ዘፋኞች እንደሰጠች በእርግጠኝነት ለመናገር ይቸግራታል… “የማታ እንጀራ” የተሰኘው የግጥም መጽሐፏ ሲመረቅ በድምጽ ባለሙያዎችና በጓደኞቿ ትብብር የተዘጋጀ ‘ሰርፕራይዝ’ አይነት ስጦታ ተበረከተላት… ስጦታው ሲታይ እስካሁን የሰራቻቸውን የዘፈን ስራዎች ያሰባሰቡ ሲዲዎች ነበሩ… በደስታና በአግራሞት መሃል ሆና አመስግና ተቀበለቻቸው… በኋላም ከ400 በላይ የዘፈን ግጥሞች ለ47 ዘፋኞች እንደሰጠች ተረዳች… ተገረመችም… ተደሰተችም… አመሰገነችም…

ምንም እንኳ ወዳጆቿ የቻሉትን ያህል ለማሰባሰብ ቢሞክሩም ሙሉ ነው ለማለት ግን አይቻልም… ምክኒያቱም በካሴት የመቀረጽ እድል ያላገኙ በድሮው ጊዜ በቲያትር ቤቱ የባሕል ክፍል ይዘፈኑ የነበሩ ዘፈኖችን ማካተት አልተቻለምና ነው… እንደ ምሳሌም የነ ጠለላ ከበደን፣ የነ ፀሐይ እንዳለን፣ የነ መልካሙ ተበጀን በካሴት ያልታተሙ ዘፈኖች መጠቃቀስ ይቻላል….

የሷን ግጥም ያልዘፈነ ዝነኛ ድምጻዊ ማግኘት ይከብዳል ከክቡር ዶክተር ጥላሁን ገሠሠ ጀምሮ እነ ማሕሙድ አህመድ፣ ሙሉቀን መለሰ፣ ቴዎድሮስ ታደሰ፣ ፀሐዬ ዮሐንስ፣ ሻምበል በላይነህ፣ ዳዊት መለሰ፣ ኅይልዬ ታደሰ፣ ግርማ ተፈራ፣ ብዙአየሁ ደምሴ፣ ሰጠኝ አጣናው እንዲሁም ከሴቶች አስናቀች ወርቁ፣ አስቴር አወቀ፣ ኩኩ ሰብስቤ፣ በዛወርቅ አስፋው፣ አቦነሽ አድነው፣ ሂሩት በቀለ፣ ፋንትሽ በቀለ፣ አሰፉ ደባልቄ እያልን ከብዙ በጥቂቱ መጠቃቀስ ይቻለናል… የቻልኩትን ያህል በቀጣይ ለመነካካት እንደምሞክር ቃል እየገባሁ ላሁኑ ሙሉቀን መለሰ ላይ ብቻ ትኩረት አደርጋለሁ…

ሙሉቀን መለሰና የዓለም ፀሐይ ግጥሞች . . .

muluken
ሙሉቀን በተነሳ ቁጥር የዘፈኖቹን ግጥሞች ውበትና ጥልቀት… የተሸከሙትን መልእክትና ቁምነገር ያለማንሳት አይቻልም!… ዘመናችንን ሙሉ ካጣጣምናቸው ከአብዛኛዎቹ ድንቅ ግጥሞች ጀርባ ደግሞ ዓለም ፀሐይ አለች… ሙሉቀን በአብዛኛው የእሷን ግጥሞች ሲጫወት ነው የኖረው… “ሌቦ ነይ” ከሚለው የመጀመሪያ የካሴት ስራው ጀምሮ ዘፈን እስካቆመበት ጊዜ ድረስ የዓለም ፀሐይን ግጥሞች አዚሟቸዋል… ባጋጣሚ ሙሉቀንን ብታገኘውና “እንትን የሚለው ዘፈንህ ግጥሙን ማን ነው የጻፈው?” ብትለው ድንገት የሰጠውን ገጣሚ ቢዘነጋው አልያም በጊዜያዊነት ግር ቢለው በርግጠኝነት “ያው ዓለም ፀሐይ ትሆናለች” ብሎ ነው የሚመልስልህ….

ሙሉቀን እጅግ ውብ የሆኑ ዘመን ተሻጋሪ ስራዎቹን ለኢትዮጵያ ሙዚቃ አበርክቶ ዓለማዊውን ዘፈን የተሰናበተና መንፈሳዊውን ዓለም የተቀላቀለ ብርቅዬ አርቲስት ነው… የቋንቋው ውበት… የአዘፋፈኑ ለዛ… የሚጫወታቸው ግጥሞችና ዜማዎች… ቅንብሮቹ… ብቻ በሁሉም የተዋጣለትና የተለየ ቦታ መቀመጥ የቻለ ድምጻዊ ነው… ዓለም ፀሐይ ራሷ ምንም እንኳ ስራዎቿን የተጫወቱላትን ዘፋኞች በሙሉ እንደየመልካቸው ብትወዳቸውም… ብታከብራቸውም… ብታደንቃቸውም… ለሙሉቀን ያላት ስሜት ግን ይለያል….

ሙሉቀን ቋንቋ አዋቂ ነው… ቋንቋን የማሳመር ተክኖ አለው… ዜማ መርማሪ ነው… አንድን ዘፈን የሚሰራው ብዙ ተጨንቆና ተጠቦ… ብዙ ዜማዎችን አጥንቶና መርምሮ… ብዙ ጊዜ ወስዶ… ከነፍሲያው ጋር አዋህዶ ነው… ጥድፍ ጥድፍ ያለ ጥናት አይወድም!… የተዋከበ ቀረጻም አይዋጥለትም!… ያልመሰለውን ቅንብር አይቀበለም!… በወቅቱ የነጋዴዎችን ተጽእኖ ተጋፍጦ ለጥበቡና ለስሜቱ ያደረ በሳል አርቲስት ነው!… በዚህም የኢትዮጵያ ሙዚቃ በቅንብር ረገድ እንዲያድግ የበኩሉን አስተዋጽኦ አድርጓል… እነ ሙላቱ አስታጥቄን የመሳሰሉ ሊቅ አቀናባሪዎች ስራዎቹን ተግተው እንዲያቀናብሩለት ድርሻውን ተወጥቷል… በክፍያም ረገድ በዘመኑ ለዘፋኞች የሚከፈለው ክፍያ ከፍ እንዲል ፈር የቀደደ ነው…

ዓለም ፀሐይን የሚያበሳጫት አንድ ችግር ግን ነበረበት… ግጥሞቿ ውስጥ የባህል፣ የህዝብ፣ አሊያም ገጣሚያቸው በውል የማይታወቁ ስንኞችን እያመጣ ይጨምራል… አንዳንድ ዘፈኖቹ ላይ ግማሹ ግጥም የሷ ይሆንና ግማሹ የሌላ ይሆናል… ይህን ስራውን አትወድለትም!… “እንደዚህ አታድርግ ግጥሞቹን እንዳሻሽላቸው ከፈለግክ እራሴው ላሻሽላቸው እንጂ የሌላን አምጥተህ ስራዎቼ ውስጥ አትጨምርብኝ!” ብትለውም እሱ ከወደደና ካመነበት ያደርገዋል… ካሴቱ ከወጣ በኋላ ለተወሰነ ጊዜ ከፊቷ ይሸሻል… “እስቲ ጥይቋት… ምን አለች?… ተቆጣች?…” እያለ ይጠይቃል… በኋላም ስራው ይቀጥላል… እንዲህ አይነቶቹን ዘፈኖች በሙሉ ልብ የኔ ናቸው ለማለት አትደፍርም… ይህ ግን ባንዳንዶቹ ስራዎቿ እንጂ በሁሉም ላይ አይደለም…

በአብዛኛው ሙዚቃ አፍቃሪ እጅግ የሚወደዱት እነ “ገላዬዋ”… “ሰውነቷ”… “ወይ እዳዬ”… “አልዘገየሽም ወይ”… “ቁመትሽ ሎጋ ነው”… “መውደዴን ወደድኩት”… “ቁረጥልኝ ሆዴ” እና ሌሎች በርካታ ስራዎቹ የሷ ግጥሞች ናቸው… ጥቂት ስንኞችን ልቆነጣጥርና ለዛሬ ላብቃ…

1) ♪♪ ገላዬዋ ♪♪

♪♪ ገላዬዋ ነይ ነይ
ገላዬዋ ነይ ነይ
ሰው በገላው ውበት ይናፈቅ የለም ወይ♪♪

♪♪ ያይን ሽፋሽቷን ቅንድቧን አድንቁ
ጣቷን አስተውሉ ስትተዋወቁ
ዓይኗን ተመልከቱት እኔው ፈቅጃለሁ
ከኔው ጋር እያለ ሲዋሽ ይዤዋለሁ ♪♪

♪♪ አንገቷን አድንቁ መቃ ነው ብላችሁ
አካባቢ ሲቃኝ ታገኙታላችሁ
ቁጣ ግልምጫውን እችላለሁ ያለ
ጡቷን ቢመለከት ከልካይ አንድም የለ ♪♪

♪♪ ጥርሷን አሳስቁት ዝምታን አያውቅም
ፈገግታ በሷ ዘንድ ብዙ አያስጨንቅም
ዳሌ አቀማመጡን እዩት ለናሙና
እግሯን አትንኩብኝ መምጫዋ ነውና♪♪

♪♪ ገላዬዋ ነይ ነይ
ገላዬዋ ነይ ነይ ♪♪

2) ♪♪ ቁመትሽ ሎጋ ነው ♪♪

♪♪ ቁመትሽ ሎጋ ነው ሰንደቅ ያሰቅላል
የሰላም የፍቅር ምልክት ያሳያል ♪♪

♪♪ አሸን ክታብ ድሪ አልቦ ለቋ* ቀርቶ
ሽመል ሰውንተሽ ይታያል አብርቶ
ድሪውን ጠልሰሙን ገላሽ ባያደርግም
የፍኝ እኩሌታ ውበትሽን አይነፍግም ♪♪

♪♪ ለምድና ጎፈሬ ምን ይሆነኝ ብለሽ
ጌጤ መድመቂያዬ እራስ ወርቄ አንቺ ነሽ
የኔ በትረ ሙሴ መጥፎሽን አልወድም
ጠምበለል ነሽ ሎጋ ይህንን አልክድም ♪♪

♪♪ ቁመትሽ ሎጋ ነው ሰንደቅ ያሰቅላል
የሰላም የፍቅር ምልክት ያሳያል ♪♪

3) ♪♪ መውደዴን ወደድኩት ♪♪

♪♪ አንቺን መሳይ ቆንጆ ለኔ የሰጠኝን
መውደዴን ወደድኩት ያንቺ ያረገኝን
የኔ ያረገሽን መውደዴን ወደድኩት
ሳስብ ሳሰላስል ቆየሁ ከወሰንኩት ♪♪

♪♪ ሃር ከመሰለው ከጸጉርሽ ጀምሮ
እንከን የሌለብሽ ውብ ነሽ በተፈጥሮ
ትኩስ የፈነዳው ጽጌሬዳ ከንፈር
እስኪ አፍ ያውጣና ውብትሽን ይናገር ♪♪

♪♪ የሐረር መንደሪን የመስከረም አደይ
የሞጆ ብርትኳን የነሐሴ እንጉዳይ
ከንፈርሽ እንጆሪ ቀይ ጽጌሬዳ
ወፍ ጭጭጭ ሳይል ማልዶ የፈነዳ ♪♪

♪♪ አንቺን መሳይ ቆንጆ ለኔ የሰጠኝን
መውደዴን ወደድኩት ያንቺ ያረገኝን
የኔ ያረገሽን መውደዴን ወደድኩት
ሳስብ ሳሰላስል ቆየሁ ከወሰንኩት ♪♪

. . . በመጨረሻም እስቲ እናንተም የምታውቁትን ስራዎቿን ጻፍ ጻፍ አድርጉልኝ… ከዓለም ፀሐይ ጋር ያወጋነው ብዙ ነው… በቀጣይ ደግሞ ከሌላ ብርቅዬ ድምጻዊ ጋር ይዣት እመለሳለሁ… ረጅም እድሜ ላንቺ ዓለም ፀሐይ… ሰላም ለሁላችን!!!

ክብር ለጥበበኞች!
አብዲ ሰዒድ
2005 E.C

 
Leave a comment

Posted by on May 21, 2013 in ስብጥርጥር

 

ወፍዬ በእኔ እይታ

ይህ ጽሁፍ በአበባየሁ መሰለ የተጻፈ ነው… ግጥሙ በገጣሚ ሙሉጌታ ተስፋዬ ስለተጻፈውና ድምጻዊ አበበ ተካ ጥሩ አድርጎ ስለተጫወተው ወፍዬ ዘፈን ይተነትናል… አንብቡትማ!… የምትሉትም ካለ አካፍሉን እስቲ ….

ወፍዬ በእኔ እይታ . . .  
(በአበባየሁ መሰለ (ዶ/ር) )

አብዲ እኔም እንዳንተ በወፍዬ የሰከርኩ የወፍዬ ዘካሪ ነኝ። ወፍዬን ስሰማ አንዲት ጠንካራ ሴት ያለማንም ድጋፍ ራሷን ችላ ኑሮ ቀልሳ ለመኖር የቻለች፤ ደጋፊ እንደሌላት አውቀው፤ ብቸኝነቷን አይተው ጉልበተኞች ያበሳቅሏት፤ በሽታ ላይ የጣሏት፤ ለልጁዋ ኖራ ለልጁዋ ያለፈችን እናት አይበታለሁ። ይህንን እይታዬን ከግጥሙ እየቆነጠርኩ ላስረዳ።

ወፍዬ …

♪♪ ጭራ ጭራ የምታድረው 
ጭራ ለቅማ የምታድረው
እንዲህ አስናቀችኝ 
ቀድማኝ ጎጆ ወጥታ ጎጆ አስተማረችኝ
ጎጆ አቤት ጎጆን ወፍዬ አስቀናችኝ . . .♪♪

እነዚህ ስንኞች የዚህች አናት ቀድማ ጎጆ መውጣቷ፤ ቀድማ ቤት፤ ኑሮ መመስረቷ፤ ለፍታ-ጥራ ግራ መኖሯ ያስቀናው (መልካም ቅናት)፤ የሷን ጥንካሬ ያስመኘው ልጇ የሚለውን ነው የሚነግሩን። ይህች እናት ግጥሙን ገጣሚው ሲጽፈው በሕይወት የለችም የሚል እሳቤ ይዤ ነው የተነሳሁት። ይህ ልጇ “ጎጆ” ብሎ የሚመስለው የምድሩንም የሰማዩንም ቤቷን ነው። ያንቺን ኑሮ በሰጠኝ ብሎ የሚመኘውም አንድም በምድር አንድም በሰማይ መሆኑን በተለያየ መልኩ እንመለከታለን። ይህንን ምኞቱንና ፍልስፍናውን በጥልቀት ከሚቀጥሉት ስንኞች መረዳት ይቻላል።

♪♪ምነው ባደረገኝ የሷ ጋሻ ጃግሬ
እንደምንም ብዬ እኔም ጥሬ ግሬ
ያገዳ ጎጆዬን ባቆምኳት ማግሬ . . . ♪♪

♪♪ አጉል በቃኝ ላይል አይን አይቶ ገምቶ
ወይ ሞልቶ ላይሰላ ጆሮ አይችሉ ሰምቶ
እንዴት ጎጆ ይቅር አርሶና ሸምቶ . . .♪♪

የሚቀጥሉት ስንኞች በተለይ የምድሩንና የሰማይን ኑሮ በሚያምር አገላለጽ ይሉታል።

♪♪ገመና ከታቹ የሳር ቤት ያማረሽ 
ሚስጥረ መለኮት ማነው ያስተማረሽ
ካፈር ክዳን ጎጆ መሬቱን ፈልፍሎ 
ከሰማይ ቤት እጣሽ ማን በሰጠኝ ከፍሎ♪♪

ምልከታዬን በተሻለ መንገድ ለማስረዳት ይረዳኝ ዘንድ በተለይ እነዚህን ስንኞች በቅርበት መመልከት ያስፈልጋል። ብዙዎቻችን እንደምናውቀው በተለይ በገጠር ቤቶች ከሳር ክዳን ነው የሚሰሩት–በተለምዶ “ጎጆ-ቤት”ብለን የምንጠራው ማለት ነው። “ገመና ከታቹን የሳር ቤት ያማረሽ” ሲል የ’ድሃ’ መቃብር አስከሬኑ በኩታና በሰኔል ይጠቀለልና ሳር ተጎዝዩዞበት ይቀበርና አፈር ከተመለሰበት በሃላ ሳር ይጎዘጉዝበታል። የ’ድሃ’ መቃብር ወለሉም ጣራውም ሳር ነው። ስለዚሀ ይህ ስንኝ ቢያንስ ሁለት ተምሳሌቶችን የያዘ ነው ማለት ይቻላል፡ አንደኛው-ምድራዊ ጎጆ ቤትን፤ ሌላኛው ግብአተ መሬትን ማለት ነው። በተለይ የገጣሚው ትኩረት፤ በእነዚህ ስንኞች ማለቴ ነው፤ የሰማዩ ኑሮ ላይ እንደሆነ የሚታየው የቤቷ አሰራር መለኮታዊ ይዘት እንዳለው ይገልጥና “ካፈር ክዳን ጎጆ መሬቱን ፈልፍሎ” “ከሰማይ ቤት እጣሽ ማን በሰጠኝ ከፍሎ” በማለት አንቺ በገባሽበት የአፈር ቤት ውስጥ እኔንም ማን ቢያስገባኝና እሰማይ ብንገናኝ የሚል አይነት አንድምታ ያስይዘዋል። 

እንዲያው ከላይ ብቻ ላነበበው ወፎች አፈር ጭረው ሰማይ ላይ የአፈር ቤት ይሰራሉ ብሎ እሱን ሊነግረን ነው ሊያሰኝ ይችላል። እርግጥ ነው የግጥሙ ተምሳሌት እሱን የተከተለ ነው፤ መዳረሻው ረቂቅ ይሁን እንጂ። የሚከተሉት ስንኞች ውስጥ ደግሞ የበለጠ የሰው ልጅ “ሩቅ ሃሳቢ ቅርብ አዳሪ” እንደሆነ (ብዙ እያሰበ ባጭሩ ሊቀጭ እንደሚችል) ልብ በሚነካ እንጉርጉሮ አይነት ለዛ ይነግሩናል።

♪♪ እኔን እኔን እኔን ይብላኝ
እኔን አይኔን እኔን ይብላኝ
የቀን ሰው ሌት አፈር
ልቤ ሩቅ አሳቢው ቅርብ አድሮ ሲደፈር
ምን ነበር ቢቆጨው ጎጆ አጥቶ ከማፈር . . . ♪♪

የሰውን ልጀ ላፍታ ታይቶ እንደሚጠፋ፤ ይህንንም ሃቅ “የቀን ሰው ሌት አፈር” “ልቤ ሩቅ አሳቢው ቅርብ አድሮ ሲደፈር” ብሎ ባዋቀራቸው ስንኞች እያዋዛ ከታሪኩ ጋር በውበት ይለውሰዋል። 

♪♪ ፈጣሪዋን አምና ያፏን ጥሬ ሰጥታ 
ለጭሮ አዳር ውሎ በዝማሬ ወጥታ
አዳኝ እንዴት ያጥቃት ፍርድና ዳኛ አጥታ . . . ♪♪

♪♪ አጣሁ ነጣሁ ብላ እንደሰው ባይከፋት 
ምፅዋት ባትለምን ተርፎን ባንደግፋት
ጎጆዋ ለቻላት ምን ነበር ባንገፋት . . .♪♪

እነዚህ ስንኞች አሁንም ከላይ ከላይ ላነበባቸው ገጣሚው ወፍ ጭጭጭ እያለች እየዘመረች ሳታርስ ሳታርም በፈጣሪዋ ተማምና ጭራ ልትበላ በጠዋት ወጥታ እረኛ ወይም ሰብል ጠባቂ አጠቃት የሚለን ይመስላል። እርግጥ ነው የግጥሙ አርዕስት “ወፍዬ” ነውና ተምሳሌቱ የወፍ ኑሮ ነው። ነገር ግን ጥቂት ጠለቅ ብለን ብንመለከት፤ ያቺ ከርታታ እናት በጠዋት “ፈጣሪዋን አምና ያፏን ጥሬ ሰጥታ” ይለናል። እሷ በፈጣሪዋ ተማምና ያፏን ጥሬ ሰጥታ–ጾማ–ያላትን ለልጅዋ አጉርሳ..ጭራ ልታድር እያመሰገነች ወጣች። ግና የወደቀ ዛፍ ምሳር ይበዛበታልና ለፍታ ባደረች፤ ጭራ በኖረች ጉልበተኞች አላኖር አሏት፤ ደበደቧት በሽተኛ አደረጓት። 

♪♪ ታማ ትንፋሽ አጥሯት ደክማ ስታጣጥር 
ማን ያቃናት ይሆን ውለታ ሳይቆጥር
ወልዶ ማሳደጉን ብዙ ሰው ቢያውቅበት
ያፉን ማን ይሰጣል የ’ጁ ሲርቅበት . . . ♪♪

ብቸኛ ናትና ደጋፊ የሌላትምና ታማ ስታጣጥር እንኳ ውለታ ሳይቆጥር ውሃ የሚያቀብላት አጣች። እንደዛ እየማቀቀች ወጥታ ጭራ ራሷንና ልጇን መመገብ ተሳናት። እጅ አጠራት፤ አጣች። ቢሆንም ግን እሷ ትራብ እንጂ ልጇን ታጎርሳላች። ይህንን የእናትነትና የመሷዕት ውድነት በመጨረሻዎቹ ሁለት ስንኞች ሙሉጌታ ልብ በሚነካ አይነት ይገልጠዋል። ልብ እንበል አሁንም ስለወፍ አኑኗር ነው የሚነግረን። ወፍ ደግሞ በአፏ ነው የመትበላው በአፏ ነው የምታበላው። “ወልዶ ማሳደጉን ብዙ ሰው ቢያውቅበት” “ያፉን ማን ይሰጣል የ’ጁ ሲርቅበት . . .” ይለናል። ያቺ እናት እጅ አጥሯታል፤ አጥታለች፤ እጇን ዘርግታ መስጠት አልቻለችም፤ የእጇ ራቀባት፤ ከየት ታምጣ? የእጄ ራቀ ብላ ግን ልጇን አላስራበችም። የምትቆርሰው ብታጣ ራሷ ልትጎርሰው ያዘጋጀችውን ካፏ ላይ ወስዳ ልጇን ታበላለች። 

ታዲያ…ማን አለ እንደ ወፍዬ? ይህስ ልጅ አማዬ እዚህ አልተመቸኝም እዚያው ከሰማይቤት እጣሽ ማን በሰጠኝ ከፍሎ ቢል እናቱ ለሱ ምን እንደሆነች ማን ይረዳል? ወፍዬ ድንቅ እናት!

♪♪ ወልዶ ማሳደጉን ብዙ ሰው ቢያውቅበት
ያፉን ማን ይሰጣል የ’ጁ ሲርቅበት . . .???♪♪

ሙሉጌታ ተስፋዬ ተባረክ!

እንግዲህ ይህ የኔ እይታ ነው…እናንተስ ምን ትላላችሁ?

 

Image

 

 
Leave a comment

Posted by on May 18, 2013 in ስብጥርጥር

 

እናት እሙ ገላ !

ደግሞ አንድ ቀን ላንቺ ከቶ ምን ሊረባ?
ዓመት ሙሉ ማሰብ 
ዓመት ሙሉ ማክበር 
ዓመት ሙሉ መውደድ 
ዓመት ሙሉ ማፍቀር
በዘመን ቢመተር ከአንጀት ላይገባ !

ሰማሽ እሙ ገላ …

ተወርቶ ተነግሮ 
በጽሁፍ ተሞንጭሮ
በፎቶ ተሰቅሎ
በቃል ተሸልሎ 
ብዙ ተፎክሮ ያልቅ እንደሆን እንጃ
የተራመድኩበት የፍቅር ስጋጃ..

እማምዬ ውዴ …

አንቺ የኔ ምንጣፍ መረማመጃዬ
የኑሮ ግብግብ መለማመጃዬ 
መውጣቴ መውረዴ
መውደቅ መነሳቴ 
ደስታዬ ኩራቴ 
ሃዘኔ ክሳቴ 
ጉስቁልና ጥጌ
ጌጤና ማረጌ…

ደግሞ አንድ ቀን ላንቺ ከቶ ምን ሊረባ?
ዓመት ሙሉ ማሰብ 
ዓመት ሙሉ ማክበር 
ዓመት ሙሉ መውደድ 
ዓመት ሙሉ ማፍቀር
በዘመን ቢመተር ከአንጀት ላይገባ!

___ // አብዲ ሰዒድ // ___

. . . ዛሬ እለቱ የእናቶች ነው ቢሉ ላስብ ሞከርኩና ድክም አለኝ… እውን ታስቦ ይቻላልን?… 
እንዲያው ዝምምምም እንጂ!…

ለማናቸውም HAPPY MOTHERS DAY !

ፍቅር ለሁሉም እናቶች ❤
ሰላም ለሁሉም እናቶች ❤
ጤና ለሁሉም እናቶች ❤

LOVE YOU ENATEE
LOVE YOU UUMMII
LOVE YOU MOMMM

ONE LOVE !
Image

Picture Source: 
http://anguloart.wordpress.com/2012/01/19/animation-portfolio-motherhood/

 
2 Comments

Posted by on May 12, 2013 in ግጥም

 

የመድረሳ ፍቅር

(ለሐሊማ)

አሊፍ፣ ባ፣ ታ፣ ሣ . . . *
አሊፍ፣ ባ፣ ታ፣ ሣ . . .
ፊደላት ስንለይ ተቀምጠን መድረሳ
ልሳንና ቀለም ስንመጥን በአበሳ. . .

የኡስታዝን ቁጣ ትንሽ ነፍሴ ፈርታ
ለማሃፈዝ ስጣጣር ሳፋቅድ ስፈታ…

ደግሞ ባንቺ ፍቅር ቀልቤ ሩኋን ስታ
ሰርቄ እያየሁሽ በኩርኩም ስመታ
ያደግኩብሽ ውዴ ናፍቆቴ ሐሊማ
የልጅነት ገዴ ነይ ድምጽሽን ልስማ…

አሊፍ፣ ባ፣ ታ፣ ሣ . . .
አሊፍ፣ ባ፣ ታ፣ ሣ . . .
ኹሩፍ ስንለያይ ተቀምጠን መድረሳ
ልሳንና ቀለም ስንመጥን በአበሳ…

ቁርአኑን ወጣሁት ጨረስኩት ሃፍዤ
አንቺን ለማስደሰት በፍቅርሽ ተይዤ

ታዲያ አሁን ዛሬ ትልቅ ሰው ተብዬ
በትልቆች መሃል በክብር ቁጭ ብዬ
ቁርአኑን ልቀራው በገለጽኩት ቁጥር
ጀነትን ያሳየኝ ቀናው የልጅ ፍቅር
ድቅን እያለብኝ ተቸገርኩ ሐሊማ
ለበይክ አለሁ በይኝ በይ ድምጽሽን ልስማ…

አሊፍ፣ ባ፣ ታ፣ ሣ . . .
አሊፍ፣ ባ፣ ታ፣ ሣ . . .
ፊደላት ስንለይ ተቀምጠን መድረሳ
ልሳንና ቀለም ስንመጥን በአበሳ…

ትዝ ይልሽ እንደሆን ያኔ ልጆች ሳለን
ሐራም ሐላል ሳንል በቅን አብረን ዘለን
አንቺም እጄን ይዘሽ እኔም አንቺን ይዤ
ቁርአኑን ስትወጭው እኔም ባንዴ ሃፍዤ
ቦርቀን ነበረ ለዱንያም ላኼራ
ዛሬ ድምጽሽ ጠፋ በይ ስሚኝ ስጣራ
የኒካው ቀለበት ተቀምጧል በአደራ …

አሊፍ፣ ባ፣ ታ፣ ሣ . . .
አሊፍ፣ ባ፣ ታ፣ ሣ . . .
ፊደላት ስንለይ ተቀምጠን መድረሳ
ልሳንና ቀለም ስንመጥን በአበሳ…

__ // © አብዲ ሰዒድ // __
ተጻፈ: 2004 E.C
ኡፕሳላ፣ ስውዲን።

ማስታወሻ:

ከአረብኛ የተወሰዱና ምናልባት መድረሳ ላልተማረ ሰው ግር ይሉ እንደሁ ብዬ ያሰብኳቸውን ቃላት እንደሚከተለው ትርጓሜያቸውን አስቀምጫለሁ… የተሻለ የአረብኛም ሆነ የመድረሳ ትምህርት እውቀት ያለው ሰው ፍቺዎቹን ቢያሻሽላቸው ደስታዬ ነው…

መድረሳ: የቁርአን ትምህርት ቤት
አሊፍ፣ ባ፣ ታ፣ ሳ፣ . . . የአረብኛ ፍደል ቆጠራ
ኡስታዝ… የቁርአን ወይም የሃይማኖታዊ ትምህርት አስተማሪ
ማሃፈዝ… በቃል ሸምድዶ መያዝ… ወይም በቃል ብቻ መውጣት…
ኹሩፍ… የአረብኛ ፊደል ወይም ፊደል ቆጠራ
ለበይክ … አቤት.. አለሁ እንደማለት
ሐራም… የተከለለ… በሃይማኖት አስተምህሮት የማይፈቀድ
ሐላል… የተፈቀደ… ሊደረግ የሚቻል

 Image

 
3 Comments

Posted by on May 9, 2013 in ግጥም

 

. . . / የግራ ገቡ ደብዳቤ / . . .

ይህ ጽሁፍ አንድ ግራ-ገብ ግለሰብ የጻፈው ነው… ብዙ ነገሮች ግራ ግብት ቢሉት ግራ በተጋባች መጣፊያው ግራ ገብ ጥያቄዎችን ሊያነሳ ወደደ!…

እናንት የገባችሁ ተመራማሪዎች!… እናንት ያልገባችሁ ተደናቋሪዎች!… እናንት ግራ የገባችሁ ተደናባሪዎች ሆይ!…. በየትኛውም አቅጣጫ ቀፍድዶ ከያዘን ጽንፍ አሳብ ነጻ ሁናችሁ የግራ ገቡን አሳብ በመልካምነት ትመለከቱ ዘንድ… ጥያቄዎቹንም በቀናነት ለመመለስ ትሞክሩ ዘንድ ትለመናላችሁ… መመለስ ፈቃዳችሁ ባይሆን እንኳ ለራሳችሁ ብታብሰለስሉት ግራ ገብነትን እንደመጋራት ይቆጠራል….

ልብ በሉ!… ይህ ግለሰብ ግራ የተጋባው የሚያስበው አጥቶ አይደለም!…. የሚጸናበት አቋም የሌለው ዋዣቂ ስለሆነም አይደለም!… ነገሮች የሚደባለለቁበት ቀዥባራ ሆኖም አይደለም!…. ይልቁኑስ ከዚህምም ከዚያም የሚወራወሩትን ቅጥ የለሽ ዘለፋዎችና ውል የለሽ መናቆሮችን አጥርቶ ማወቅ ስለፈለገ እንጂ!… ከመደናቆር መመካከር በሚል መንፈስ ስለተነሳሳ እንጂ!…

ይህን ግራ ገብ ግለሰብ ሃይማኖቱን አትጠይቁት!…. ማንን እንደሚያመልክ አትመርምሩት!…. ከየት እንደመጣ ለማወቅም አትጣሩ!… ዘር ማንዘሩንም ለመቁጠር አትድከሙ!… “እንዲህ የሚያስበው የእንትን ፓርቲ አባል ስለሆነ ነው!… የነእንትና ደጋፊ ስለሆነ ነው!…. እነ እንትናን ስለሚጠላ ነው!”… ምናምን ብላችሁ በራሳችሁ መነጽር ለማየትም አትልፉ!… በመላ ምት ለመደምደምም አትጣደፉ!…

ይህ ሁሉ ኮተት አሳቡን ለመረዳትም ሆነ ጥያቄዎቹን ለመመለስ አያስፈልግም!… ግራ ገብነቱን ቢያባብሱት እንጂ አይቀንሱትምና!…. እናም ዝምምምም ብላችሁ ብቻ ግራ መጋባቱን ተረዱለት!… በቀናነት ሰው የመሆን መንፈስ ብቻ ተሞልታችሁ ጥያቄዎቹን መልሱለት… ልትመልሱ ካልቻላችሁም በባዶ ከመዘባረቅ ዝምታ ወርቅ ነው።

ጥያቄዎቹም ሆነ አሳቦቹ በሰሞኑ ከተነሳው የአቡነ ጴጥሮስ ሐውልት እና ከባቡር መንገድ ዝርጋታው ጋር ይያያዛሉ . . .

ከሐውልቱ መነሳት ጋር ተያይዘው ለተፈጠሩት መነታረኮች… መበጣበጦች… እና ግራ መጋባቶች ዋናው ተጠያቂ መንግስት እንደሆነ ግራ ገቡ ያምናል። ጥርት ያለ መረጃ ቀድሞውኑ በአግባቡ ተዳርሶ ቢሆን… አስፈላጊው ውይይት ከሕብረተሰቡ ጋር ተደርጎ ቢሆን… ቀደም ብሎ ባሳለፈው ታሪክ መንግስት ለታሪክና ለቅርስ ተቆርቋሪነቱን በጽናት አስመስክሮ ቢሆን… ይህ ሁሉ ያለመተማመን… ይህ ሁሉ መደበላለቅ… ይህ ሁሉ መቀበዣዠር ላይኖር ይችላል… በዚያ በኩል ብዙ ነገሮች እያጠፋ እያየን በዚህ በኩል ብዙ ነገሮች ሲያለማ ስናይ አናምንህም ብንለው አይፈረድብንም።

የምንግስት ችግሮች ዘርፈ ብዙ ናቸው… የመንግስት መልካም ስራዎችንም በብዛት እያየን ነው… እነዚህ ሁሉም በየመልካቸው ራሳቸውን የቻሉ መወያያ ጉዳዮች ናቸውና እዚህ አናደበላልቃቸውም።

ይሄ ጉዳይ ሐውልቱን ብቻ ስለሚመለከት እንጂ ሽሽት አይደለም!… አንዱን ችግር ከሌላው መልካም ስራ ጋር ማደባለቁ ግራ ከማጋባት የዘለለ ፋይዳ አይኖረውም!… እዚህ ላይ ግራ ገቡ የሚፈልገው ሙያ ነክ መልሶችን… የጋራ ጥቅምን የተመለከቱ ውይይቶችን እንጂ ከንቱ መደናቆርን አይደለም።

* * *
አቡነ ጴጥሮስ ጳጳስ ነበሩ!… ብጹዕ አቡን ነበሩ!… ሐይማኖታዊ አባት ነበሩ!… ከነዚህም ጋር ተያይዞ የሚኖራቸው ሃይማኖታዊ ስልጣን ወይም ታላቅ የሆነ መለኮታዊ ቦታ ሊኖር ይችላል… ያ!… ሃይማኖታዊ ስለሆነ እዚህ ጋር አናመጣውም። ያ!… እምነቱ ለሚመለከታቸው ሰዎች ብቻ የሚያገለግል እንጂ የመላው ሕዝብ እውነታ አይደለምና ለዚህ ጉዳይ አያስፈልገንም።

አቡነ ጴጥሮስ የነጻነት ታጋይ ነበሩ!… አርበኛ ነበሩ!… ላመኑበት ሕይወታቸውን የገበሩ ባለውለታ ነበሩ!… የኢትዮጵያችን የቁርጥ ቀን ሰው ነበሩ!… የትግል አርማ ነበሩ!… ስንቱ ባንዳ አገሩን ሲሸጥ በአላማቸው ጸንተው ለበርካታ ታጋዮች አርአያ መሆን የቻሉ ታላቅ ሰው ነበሩ!…

“እምቢኝ አልገዛም!… እኔን እንደ አባት አምነው ለሚከተሉኝ ሕዝቦቼ የውድቀት ምሳሌ አልሆንም!” በማለታቸው ነው በግፍ የተገደሉት… ይህ ታሪካቸው ነው ሐውልት እንዲቆምላቸው ያደረገው…. በዚህ አኩሪ ታሪካቸው ማንም ነጻ ኢትዮጵያዊ እንዲያከብራቸው ይገደዳል!…. እዚህ ላይ ብቻ ነው ማተኮር የሚገባን… ለምንሰጠው ማንኛውም አስተያየት ከዚህ እይታ መውጣት ያለብን አይመስለኝም…. ሃይማኖትንና ታሪክን ማደበላለቅ እውነትን ከማጨመላለቅ የዘለለ ፋይዳ አይኖረውምና።

የኚህን ታላቅ ሰው መታሰቢያ ሐውልት እንደማንም ተራ እቃ አንስቶ መጣል ይገባል… መንገድ እንጂ በመንገዱ ላይ በነጻነት እንድንራመድ ያደረጉን ባለታሪኮች ዋጋ የላቸውም…. ብሎ የሚከራከር ቢኖር አሳቡን ይመርምር!… ምልከታውን ይፈትሽ!….

በሌላም በኩል ደግሞ ጉዳዩን ከጽድቅ ጋር አያይዞ የእምነቱ ማራመጃ… የሃይማኖቱ ማካሄጃ… ከፈጣሪው ጋር መማለጃ… የሚያደርግ ስለ ሐውልቱ በተነሳ ቁጥር የማምለክ ያህል የሚጠበብ ቢኖር!…. እርሱም አሳቡን ይፈትሽ…. ምልከታውን ይመርምር….

እንዲሁም መንግስትን እንቃወማለንና…. አስተዳደሩን አንደግፍምና…. በዚህ ታሪካዊም ሐይማኖታዊም መልክ ባለው ሐውልት ተመርኩዘን ተቋውሟችንን እናራግብ… ብለው የሚንቀሳቀሱ ቢኖሩ አገርንና መንግስትን…. ወይም ፓርቲንና እድገትን ይለዩ!…. ራሳቸውንም ይፈትሹ!…. አሳባቸውንም ይመርምሩ!….

. . . ለእኛ ታሪኩም የሃዲድ ዝርጋታውም ያስፈልጉናል . . .

ታሪክ ብቻውን ዳቦ ሆኖ አይበላም!… የጦር ጀብደኝነት ብቻውን ርሃብና እርዛት ላይ ጀብደኛ ለመሆን አያስችልም!… ሃይማኖታዊ አምልኮ ብቻውን የእድገትና የስልጣኔን መና ከሰማይ አያወርድም!… ከጠኔ ለመውጣት ዋናው ጀብዱ ስራ መስራት ነው!…. ከጨለማ አስተሳሰብ ራስን አላቆ ዝም ብሎ መትጋት!… የተስፋ ብርሃን ተሞልቶ… ከጎጠኝነትን ተፋቶ… በጋራ መልፋት!…. ተግቶ የሰራ… በሕብረት የጣረ ሕዝብ የልፋቱን… የጥረቱን ዋጋ እንደሚያገኝ ግራ ገቡ ልቤ ያምናል።

የዛሬ መንገድና ህንጻ ብቻቸውን ቢገነቡ የድሮ ማንነታችንን እየናዱ ታሪክን እያጠፉ ሲሆንም ማደግ አይባልም!…. ማንነቱን የማያውቅ… ታሪኩን የዘነጋ… ባለውላታዎቹ ላይ የተኛ ትውልድ ለታናናሾቹ የሚያወርሰው ማንነት አይኖረውም…. ቢኖረውም የተበጫጨቀ እንጂ ሙሉ አይሆንምና!…. የአገር ማንነት ከትውልድ ትውልድ እየተቀጣጠለ የሚሰራ ብርቱ ሰንሰለት እንጂ በአንድ ቦታ ተወስኖ የሚኖር ግኡዝ የአደራ እቃ አይደለም። እናም ሁላችንም የመቀጣጠል ሃላፊነት አለብን!….

ነገር ግን ታሪክን እንዴት ነው የምናቆየው?…. በምን መልኩ ነው ከትውልድ ትውልድ የሚተላለፍ ህያው የምናደርገው?… ብሎ መጠየቁና መመካከሩ የሚያስፈልግ ይመስለኛል…

ጥንት አያቶቻችን ወይም አባቶቻችን ታሪክን የሚያቆዩበት መንገድና እኛ የምናቆይበት መንገድ ይለያያል… ነገ የሚመጣው ትውልድ ደግሞ በሌላ መንገድ ሊያቆያቸው ይችላል…. ዘመን ሲለዋወጥ ከዘመን ጋር የሚለወጥ… ከትውልድ አስተሳሰብ ጋር አብሮ የሚዘምን ታሪክን የምናቆይበት መንገድ ከሌለን ወይም እንዲኖረን ካልተጋን እንዲሁ እንደተጯጯህን ብዙ ነገሮች እናጣለን… ብዙ ታሪኮችም ይባክናሉ።

“በበኩሌ የሃዲድ ዝርጋታውን አልቃወምም!… ከተማችን ባቡር ቢኖራት አልጠላም!… እድገትን ማን ይጣላል?… ግን ለምን ሐውልቱን እንዳይነካ አልተደረገም?… ካልጠፋ መንገድ በሐውልቱ ላይ ማስኬድ ምን ይባላል?!… ታሪክን ማጥፋት እንጂ!…”

የሚሉና መሰል ጥያቄዎች በተደጋጋሚ ይጠየቃሉ… ምንም አይነት ድምዳሜ ላይ ባልደርስም ጥያቄዎቹን እጋራቸዋለሁ… ለምን በዚያ መንገድ አለፈ?… ወይም ለምን እንዳይነካው አልሆነም?… ለሚለው ጥያቄ ግን ሙያዊ ምላሽ ያስፈልጋል…

በበኩሌ ለመንገድ ዝርጋታም ሆነ ለባቡር መስመር ዝርጋታ ሙያ መሃይም ነኝ። ቅንጣት የሆነች የዲዛይኒንግ ወይም መሰል እውቀትም የለኝም!… ግን ሙያው እጅግ ጥንቃቄ የሚፈልግ እንደሆነ ይሰማኛል!… እናም “ይቻላል!… አይቻልም!” ማለት አይቻለኝም። በዚህ አጋጣሚ ይህችን ጥሁፍ ድንገት የሚያነባት የዘርፉ ባለሙያ ቢኖርና ከየትኛውም ጽንፍ ነጻ ሆኖ ወይም ሆና ሙያዊ ማብራሪያ መስጠት ቢቻል ግራ ገብነትን መታደግ ብቻ ሳይሆን ለከተማችን እድገትም አስተዋጽኦ ማድረግም ነው. . .

ለመሆኑ መንገድ እንዴት ነው የሚቀየሰው?… የባቡር ሃዲድስ እንዴት ነው የሚዘረጋው?… የከተማ ፕላንስ እንዴት ነው የሚሰራው?… ለዘመናት የኖረች ከተማ ስትታደስስስ እንዴት ነው መታደስ ያለባት?… እኚህ ሁሉ የባለሙያን መልስ የሚሹ ጥያቄዎች እንጂ እንዲሁ በዘፈቀደ የሚዘባረቅባቸው ጉዳዮች አይመስሉኝም….

እስከዚያው ግን የሚመላለሱብኝን ጥያቄዎች እጠይቃለሁ…. የማያውቁትን መጠየቅ እውቀትን ከማስጨበጡም በላይ ከንቱ መደናቆርን ይቀንሳል…. እናም ጥያቄዎቹን ብቻ ትመልሱ ዘንድ በድጋሚ ትለመናላችሁ…

. . . 1 . . . ሐውልቱን እንዳይነካው ስንል እንዲቀየስ የምንፈልገው መንገድ የሌላውን መስመር ዝርጋታም የሚያጣምመው ቢሆንስ?

. . . 2 . . . ሐውልቱን እንዳይነካና በሌላ መስመር እንዲዘረጋ ስንፈልግ ፒያሳ የባቡር ሲሳይ እንዳታገኝ የሚያደርጋት ቢሆንስ?

. . . 3 . . . ሐውልቱን እንዳይነካ ስንል የምንከልሰው ፕላን የአዲስ አበባን ከተማ ማስተር ፕላን የሚረብሸው ቢሆንስ?

. . . 4 . . . የአቡነ ጴጥሮስ ሐውልት የቆመበት ቦታ እዛች ቦታ ላይ በግፈኛው የጣልያን ጦር መሪ ትእዛዝ እንዲረሸኑ ስለተደረገ እንጂ ከአዲስ አበባ ከተማ ማስተር ፕላን አንጻር ሲታይ ቦታው የመንገድ እንጂ የሐውልት ማቆሚያ ባይሆንስ?… መንገዱ ይቅርብን ሐውልቱ ይኑልን ልንል ነው?…

. . . 5. ሐውልቱ ለዝርጋታው ተነሳ እንጂ አልፈረሰም አይደል?… አያስፈልግም ተብሎ አልተጣለም አይደል?… እና ምንድነው ችግሩ?… ከዝርጋታው በኋላ መልሶ መትከል እንደማይቻል የሚገልጽ መረጃ አለ?… በመሃል ለተነሳበት ጊዜ ከሆነ መልሶ ሲተከል ለምን ተነስቶ እንደነበረ መጻፍ አይቻልም?….

ደግሞስ ለምንድነው ተመልሶ አይተከልም ብለን ገና ሳይደርስ የምንደመድመው?… በመንግስት ላይ ያለን እምነት በመውረዱ ከሆነ አንድ ነገር ነው… አይ የለም “አይቻልም!” ተብሎ ታስቦ ከሆነ ግን አልስማማም… የተባለው ዝርጋታ በትክክል የሚከወን ከሆነ ምንም የሚከብድ አይመስለኝም!… ምንም እንኳ የዘርፉ ባለሙያ ባልሆን ባጋጣሚ ያየኋቸው ከተሞች ከአንድም ሁለት ሦስት ደረጃ የወረደ የምድር ለምድር ባቡር ከስራቸው እየተምዘገዘገ ላያቸው የደራ ከተማ ነው… አይደለም አንድ መታሰቢያ ሃውልት መመለስ ቀርቶ ከስር ባቡር እየሄደ ከላይ ሕንጻ መገንባት ይቻላል… ያ ስልጣኔ ብርቃችን ቢሆንም!… ስናሳዝን!… 😦 …

እነዚህን ጥያቄዎች የምጠይቀው ግራ ገብነቴን ለማጥራት እንጂ ለሌላ አይደለም.!… እስካሁን ባጋጣሚ የምጠይቀው ሁላ “ይቻላል ለምን አይቻልም!… ክፋት እንጂ!” እያለ ከመፎከር የዘለለ ሙያዊ ማብራሪያ የሰጠኝ አልገጠመኝም…

በቻይና የሆነ መንገድ መሃል አስፓልት ላይ በካሳ ክፍያ አለመስማማት ምክኒያት የተደነቀረ የአረጋዊያንን ቤት… የሆነ በረሃ መሃል ያለች ዛፍን እንዳይነካ የተጣመመን መንገድ…. እና መሰል ምስሎችን ከማሳየት በዘለለ “ይሄ እንደዚህ ነው… መንገድ ሲሰራ እንዲህ ነው!… የባቡር ሃዲድ ሲዘረጋ እንዲህ ነው!…. የአዲስ አበባ ፕላን እንዲህ ነው!… ስለዚህ በዚህ በኩል ቢያልፍ ጥሩ አማራጭ ነበር…” የሚል እውቀትን መሰረት ያደረገ… ማደግን መበልጸግን ከመመኘትና አብሮም ታሪክን ከማቆየት ጋር ያለውን ፋይዳ የሚገልጽ ሰው አልገጠመኝም… እንዲህ ያለ ጽሁፍም አላየሁም!…. ያጋጣምችሁ ካላችሁ ብታካፍሉኝ እጅጉን አመሰግናለሁ . . .

በበኩሌ ይህንን ጉዳይ አበክሬ የማነሳው ከሃይማኖትም ከፖለቲካም አንጻር አይደለም!… ይልቁንም አዲስ አበባዬን ከአንድም ሁለት ሦስቴ ከላይ ወደታች ቁልቁል ሳያት የተሰማኝን የተደበላለቀ ስሜት እያስታወስኩ እንጂ…

ብዙ ነገሯ የተዘበራረቀ!… መንገዷ የተጣመመና የተሽሎከለከ… ህንጻዎቿ አንድ አካባቢ በስርአት ሌላ አካባቢ ደግሞ ያለ ስርአት እዚም እዛም የተተከሉባት… ያን ተከትለው ለዛ የሌላቸው መብራቶች አንድ ቦታ እንደ ችቦ የሚደምቁባት… ሌላ ቦታ እንደ ኩራዝ ጭል ጭል ጭል የሚሉባት… የመኪናውና የእግረኛው መንገድ የማይታወቅባት… የአታክልቱ ስፍራና መኖሪያ ቤቱ የማይለይባት… የልጆች መጫወቻውና የኳስ ሜዳው የማይታወቅባት… ዝም ብላ በዘፈቀደ የምትወናበድ… ዝም ብላ በዘፈቀደ የምትወላገድ ከተማ ሆና ስላገኘኋት ነው።

… የምር ታስጠላለች!… ማስጠላት ብቻ ሳይሆን የከተማ መልክ ስለሌላት ትጨንቃለች!… ለካ ከከፍታ ነው መልክ የሚታይ!… ለካ ከሰማይ ነው ውበት የሚለይ!… ውይይይ አዲስ አበባዬ…

ከሌሎች ከተሞች የሰማይ መልክ ጋር ለማነጻጸር የሚቃጣው የኔ ቢጤ ጀዝባ ካለ ደግሞ ይታመማል!…. በበኩሌ ባጋጣሚ ካየኋቸው ከስቶክሆልም… ከሮም… ከአምስተስተርዳም… ከለንደን ጋር ላመሳስላት ሲቃጣኝ በጅልነቴ እስቃለሁ!… የምር ሰው ብቻ ሳይሆን ከተማም መልክ ያስፈልጋታል…. ታሪኳን ብቻ ሳይሆን… እድገቷን ብቻ ሳይሆን… ዉበቷንም ታሳቢ ያደረገ ውይይት… ውበቷንም ታሳቢ ያደረገ ግንባታ ሊደረግ ይገባል….

አዲስ አበባችን እንዲህ ለዛ ያጣችው… እንደዚህ መልከ ቢስ የሆነችው…. መንገዶችና ህንጻዎች “እንትንን እንዳይነኩ” እየተባለ ሲዘለሉና ተለዋጭ ሲሰራላቸው ስለኖረ እንጂ የከተማዋ ማስተር ፕላን ለዛ ቢስ ሆኖ አይመስለኝም!…. እና እዚህ ጋርም የምንለውጠው የበለጠ የሚያበላሻት ቢሆንስ?… ይህ ሁሉ እንግዲህ የማላውቃቸው ጥያቄዎች ናቸው… በባለሙያ የሚመለሱ!…

በመጨረሻም ታሪክን ለትውልድ ማቆየት የሚቻለው ዘላቂ መፍትሔ የሚያመጣና የዘመን ስልጣኔን መሰረት ያደረገ ውይይት በጋራ ሲካሄድ እንጂ አንድ ጽንፍ ላይ ተንጠልጥሎ ደሞ ከኔ ወዲያ ላገር አሳቢ ብሎ በመፎከር አይደለም እናም ጽንፋችሁን ተዉትና ኑ ስለጋራ ጥቅማችን በጋራ እንነጋገር . . .

ሰላም !
One Love !
_______ // አብዲ ሰዒድ // ________

 

Image

 
Leave a comment

Posted by on May 4, 2013 in ስብጥርጥር

 

ትንሽ ማስታወሻ . . .

ቀደም ብሎ ኃይለ ማርያም ይሰኙ የነበሩት በኋላም ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ የተባሉትና በኢትዮጵያ የሰላሌና የዎሎ ጳጳስ የነበሩት የነጻነት ታጋይ አባት ላመኑበትና ለቆረጡበት አላማቸው ሕይወታቸውን የሰዉበትን የጀብዱ ታሪክ ለመዘከር ብሎም በነዚያ አምስት ዓመታት (በኢትዮጵያ አቆጣጠር ከ1928-1933) የጣልያን ቆይታ ኢትዮጵያችን ያለፈችበትን ውጥንቅጥ… የባንዳና ያገር ወዳድ ምጥ… የሻጭና ያሻሻጭ እሽቅብጥብጥ… የሃቀኛና የእውነተኛን መንጓጠጥ… ከ5 ዓመት የግዞት ኑሮ መልስ በኃላ የነበረውን የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መልመጥመጥና መቁረጥረጥ… ብሎም ብዙ መሰል ታሪኮችን ሲያስታውሰን የኖረው የአቡነ ጴጥሮስ መታሰቢያ ሐውልት ተነሳ… (ፈረሰ አላልኩም!… መነሳትና መፍረስ በጣም የተለያዩ ናቸው።)

እናም ትንሽ ምልልስ ከጸጋዬ ገብረ መድህኅን “ጴጥሮስ ያቺን ሰዓት” ከተሰኘ ተውኔት ላይ ብንቆነጣጥርስ… ይህ ምልልስ በእስር ላይ የሚገኙት አቡነ ጴጥሮስና ለጣሊያን አድሮ እጃቸውን እንዲሰጡ የሚያግባባቸው ግርሻ የሚያደርጉት ነው።

ልብ በሉ እኔ እንደመሰጠኝ ቆነጣጠርኩት እንጂ ምልልሱ ሙሉ አይደለም… እናም ሙሉ ታሪኩን ትረዱት ዘንድ ”ጴጥሮስ ያቺን” ሰዓት የተሰኘውን ተውኔት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ በኢትዮጵያ አቆጣጠር በ2003 ከታተመው የጸጋዬ ገብረ መድኅን ታሪካዊ ተውኔቶች መጽሐፍ ላይ እንድታነቡ ይመከራል።

ኃይሉ:
. . . ስለዚህ ልጄ ካንተም ሆነ ያገር አዛውንት ካልካቸው ጋር ያው እንደግራዚያኒ መቸጋገር እንጂ መመካከር አይኖረንምና ፍቃድህ ሆኖ የመጨረሻ ሰዓቴን በግል እንዳሳልፋት ለጊዜው ብቻዬን ተወኝ።

ግርሻ:
አባቲላ ለምን ቸኰሉ? ገና ለዘለዓለሙ ዓለም ብቻዎን ይሆኑ የለም?

ኃይሉ:
እሱንም ቢሆን እናንተ ወስናችሁልኝ ሳይሆን እኔ መርጨ ነው ልጄ።

ግርሻ:
ለርስዎ እንጂ ለሌላውማ እንዳይመርጡ አቅም የለዎትም።

ኃይሉ:
ለራሱ ለመምረጥ አቅም ያጣ እንኳን ተስፋ የተስፋ ጭላንጭል አይኖረውም። መሳሪያነቱ እንኳን ጭለማ እንጂ ብርሃንነት የማይኖረው፣ ጨዋ ወገኑን እንስሳ በማስደረግና፣ የተስፋቸው ጮራ ፍንጣቂ መሆኑ ቀርቶ፣ የተስፋቸው አሽቃባጭ ጥንብ-አንሳነት ብቻ ነው እሚተርፈው።

ግርሻ:
እኔስ በጄ፣ ለኔስ በጄ እንደምንም፣ እንደማናቸውም ለራሴ ልኑርለት፣ ከሞት ማዶ ያለ ተሥፋ የራዕይ ወይም የባለመለኰት ጠባይ ነውና ራሴን አላመጻድቅም።

ኃይሉ:
ትህትናህ ከግብዝነት እንጂ ከመንፈሣዊነት እንዳልፈለቀ ላንተ እንደሚታወቅህ እኔንም ያጠራጥረኛል። ይሁንና ከሞት ማዶ ያለ ተስፋ የራዕይነት ብቻ ሳይሆን የህይወትነትም፣ የሥጋዊነትም ጠባይ አለው ልጄ፣ ድፍን በድፍን እንቁላል ካልተፈረከሰ በዉስጡ ያለው አዲስ ህይወት ብር ትር ብሎ አይበርም። የስንዴ ፍሬ ወድቃ ካልበሰበሰች በቀር አታፈራም፣ አትበዛም። መውደቅና መሞት የሚያስተላልፈውን፣ የሚያፈራውን የተሥፋ አይነት መች አጣኸው?
የንፍገትና የስስት ኑሮህን እምታባብልበት ዘዴ፣ የምታሸንፍበት ልቦና አጥሮብህ ነው እንጂ።

ግርሻ:
ሞትማ ተሥፋ ከሆነ፣ ስንቱ ሽፍታ ሞቶ የለ፤
ተሥፋ ያለ በመግባባት ነው፣ በሕይወት ነው ተሥፋ ያለ።

ኃይሉ:
ያንተ ብጤው ሕይወት ለሕዝብ ተሥፋ የሞትነት መሣሪያ ነው።
የነሱ ብጤው ሞት ለሕዝቡ ተሥፋ የሕይወትነት መሣሪያ ነው።
ባላንጣን በተሥፋና በጦር መሣሪያነት እንጂ በልምምጥ፣ በእምባ ያሸነፈ የለም።

ግርሻ:
አቅም ያጣ ቢለማመጥ ተግባባ፣ ተመካከረ ነው እንጂ ባነባ ተለማመጠ አይደለም እሚባል። መግባባት የደከመ ወገን ውል ነው።

ኃይሉ:
ባሪያን በፈንጋዩ መሃል ደፍቶ መግዛትና መገዛት እንጂ ሌላ ምን ውል ሊኖር?

ግርሻ:
ትርጉም ሁሉ እንየአስተያየቱ ነው እሚራባ አባቴ። በቃል ኪዳንና በውል የሠፈረ ፊርማ ግን በሕግ የጸደቀ የተረጋገጠ የእውነት ፍሬ ነው።

ኃይሉ:
የተረጋገጠ የእውነት ፍሬ ቃል-ኪዳን? የማን እውነት? የማን ቃል-ኪዳን? ያንተ እውነት? ወይስ የኔ እውነት?

ግርሻ:
የጋራችን እውነት። የውላችን እውነት።

ኃይሉ:
ጠፊ ካጥፊው ከተዋዋለ መጥፊያውን አፀደቀ እንጂ ተዋዋለ አይባልም።

.
.
.

/ጥሩምባ/

. . . አቡነ ጴጥሮስ የተባሉት፣ በገናናው የኢጣሊያ መንግሥት ላይ ስለሸፈቱ፣ በሞት ይቀጣሉና ነገ ጠዋት ባምስት ሰዓት፣ አራዳ ጊዮርጊስ ቤተስኪያን አጠገብ እንትሰበሰቡ ተብላችኋል። . . .

.
.
.
/ጥሩምባ/
. . . አቡነ ጴጥሮስ የተባሉት፣ . . .
.
.
.

ምንጭ:
ታሪካዊ ተውኔቶች፣ ጸጋዬ ገብረ መድኅን
አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬስ፣ 2003 E.C

Image

 
Leave a comment

Posted by on May 3, 2013 in ስብጥርጥር

 

. . . የኔታና ሚስ . . .

abdi2

ሀ – ሁ . . . አ – ቡ – ጊ – ዳ
ሀ – ሁ . . . አ – ቡ – ጊ – ዳ
ገና ከማለዳ ልጅነቴን ለምዳ
ከስትንፋስ ከደሜ ከነፍሴ ተዋህዳ . . .

ሀ – ግእዝ . . . ሁ – ካእብ
ሂ – ሳልስ . . . ሃ – ራብእ
ሄ – ኻምስ . . . ህ – ሳድስ
ሆ – ሳብእ . . . ስክልስ . . .

በዜማ ስለቅም፣ በህብር ሳወድስ
መልእክተ ዮሐንስ፣ መልክተ ዮሐንስ
ስከልስ ስከልስ፣ ለነፍሴ ሳሰልስ . . .

በአገራዊ ቃና
ሕይወቴ እንዲቃና
የኔነት፣ እኔነት፣ በደሜ እንዲዘራ
የኔታ በኩርኩም፣ አባም በከዘራ
የለፉልኝ እኔ፣ ያደድኩት ልጃቸው
ዛሬ ወጉ ደርሶኝ አባት ሆኜላቸው . . .

ልጄን ከቀለም ቤት በኩራት ሰድጄ
አቡጊዳም እዳ፣
እኔነትም ባዳ፥
ሆኖበት ሲቸገር አይቼ ነድጄ! . . .

እ – ን – ደ – ተ – ብ – ከ – ነ – ከ – ን – ኩ
እ – ን – ደ – ተ – ብ – ሰ – ለ – ሰ – ል – ኩ

“ኤ ፎር አፕል” ብሎ ልጄ አፉን ፈታ
“ኤን ብቻ!” የምትሰብክ ከፊደል ገበታ
ግእዝ የማታዜም፣ ቅኔ የማትፈታ
ማንነት ‘ማይገዳት፣ ለ’ሱ የሌላት ቦታ
ሚስ ናት የሱ የኔታ
ሚስ ናት የሱ ጌታ::
_____ // _____

___ // © አብዲ ሰዒድ // ___
ተጻፈ: 2000 E.C
ሐዋሳ፣ ኢትዮጵያ።

 
Leave a comment

Posted by on May 2, 2013 in ግጥም

 

ከ – ን – ቱ . . . !

እስቲ ዝም በል አፌ!
__ አንዲትም ቃል አታውጣ
ከንቱ ነገር እያራገብክ
__ ከንቱነቴን አታሳጣ::

*
አይኔም ተው አትቆጥቁጠኝ
__ እባክህ አትፍሰስ እምባዬ
አለ ሲሉት የለም ነው
__ ሰው የመሆን እጣዬ::

*
ጆሮዬም ተወው ይቅርብህ
__ እስቲ አትለቃቅም ወሬ
ደግሞ ጨርሳ እንዳትጠልቅ
__ ያዘቀዘቀች ጀምበሬ . . .

*
ልቤም ተው አተክዝብኝ
__ ግድ የለም ሃዘን አታብዛ
አገር እንደሆን ሰው ነው
__ ፍቅር ነው ህዝብን ‘ሚገዛ . . .

*
ነፍሴ ሆይ ተሰብሰቢ
__ በይ ተነሽ ግቢ ሱባኤ
ጥሞና ነው የሚበጅሽ
__ ከራስሽ ጋር ጉባኤ . . .

*
መሄድ መምጣት ነው ዓለም
__ እንደዚህ ነው ተፈጥሮ
ቀናውን መሻት ነው ደጉ
__ የነፍስን ፅናት መርምሮ . . .

___ // © አብዲ ሰዒድ // ___
ተጻፈ: ነሐሴ፣ 2004 E.C
ኡፕሳላ፣ ስውዲን።

Image

 
Leave a comment

Posted by on May 1, 2013 in ግጥም