RSS

Category Archives: ግጥም

እቴ አንቺን ሳስብሽ . . .

 

እቴ አንቺን ሳስብሽ ልቤን የሚደክመኝ
ዐይንሽ ላይ ሳተኩር እኔ ዐይኔን የሚያመኝ . . .

አይደለም ለፊትሽ፣ ለገጽሽ ከራማ
አይደለም ለድምጽሽ፣ ላንደበትሽ ዜማ
አይደለም ለጸጉርሽ፣ ለዚያ የሃር ነዶ
አይደለም ለጥርስሽ፣ ለሃጫው በረዶ . . .

አይደለም አይደለም፣ ውዴ አበባዬ . . .
ነገሩ ወዲያ ነው፣ ሌላ ነው ጉዳዬ . . .

አየሽ . . .
በኔና አንቺ መንደር፣ በሁለታችን አገር
ወንድ ነው የበላይ፣ ወንድ ነው ‘ሚከበር
ወንድ ነው ‘ሚያነሳ፣ ወንድ ነው የሚጥል
ወንድ ነው በግብሩ ሴትን የሚያጣጥል
አዳፍኖ ‘ሚያቃጥል . . .

(በርግጥ ሴትም ሆነው ሴትን የሚያረክሱ
አይጠፉም ይሆናል በስምሽ የሚያርሱ)

ግን ግን ለምን ሆነ ?!
ልቤ ገነገነ . . .

አዋቂ ታዋቂው፣ አድናቂ አዳማቂው
መሪና ተመሪ፣ ተጨመላላቂው
መንገድ የጀመረ፣ ተረኛ ጠባቂው
ሁሉም እንዳቅሙ፣ ስምሽን አንስቶ
እንደፈቀደለት፣ ድክመትሽን አውስቶ
ውበትሽን አጉልቶ፣ ገላሽን አቡክቶ
ነፍስሽን ዘንግቶ፣ ህልምሽ ላይ ተኝቶ
ሲጽፍ ሲቸከችክ፣ ስንቱን እንቶፈልቶ
ኃይልሽ በየት በኩል፣ በነማን ተሰምቶ
ኧረ እንደምን ታይቶ …

(ይኸው እኔ ራሴ፣ እየጻፍኩ አይደለ
ብዙ ያልጨመረ፣ ብዙም ያልጎደለ)

ጥንባዣም ደራሲ፣
ኮተታም ሃያሲ፣
እንቅልፋም ገጣሚ፣
ሆዳም አሳታሚ . . .
ባንድ አገር፣ ባንድነት ዐይኑ እየፈዘዘ
በንዋይ በዝና፣ ነፍሱ እየነፈዘ
በሆዱ፣ በራቡ፣ እየደነዘዘ፤
የቃላት ቡትቶ እየበዋወዘ
ስንት ቀን ገደለሽ፣ ስንት አንቺን ገነዘ …

አየነው፣ ሰማነው …
ገዝተን አነበብነው …

‘ወሲብ፣ ገድል፣ ሚስጥር
የአዲስ አባ ‘ቂንጥር’
የጭኖች ንቅሳት
የዳሌ ትኩሳት’
መዋደቅ መነሳት የሚል ዝባዝንኪ
ስንት ሰዎች ጻፉ በይ ንገሪንኝ እስኪ ?!

ለምቦጭሽን አትጣዪ፣ ጠበቅ አርገሽ ስሚኝ
ካጠፋሁም ላጥፋ፣ ተይኝ አታርሚኝ
ይልቅ ተማሪና ስታመም አክሚኝ።

አሁን ያ ደራሲ . . .
‘ጭኗ ሲተራመስ፣ ዳሌዋ ሲቆጣ
ጡቷ ሲወጣጠር፣ ቅንዝሯ ሲመጣ
ሲሰራት፣ ሲቆላት፣
እንደ ጉድ ሲያምሳት፣
አብርድላትና ከንቱ ነፍሷን ንሳት፤
መቼም ከዚህ በቀር ሁሉም ነው የሚያንሳት።’

ብሎ እየጻፈ በገላ ችርቸራ
በሴትነትሽ ጥግ ዝሙት እየዘራ
ከመጣ ከሄደው አንቺን እያዳራ
‘ታላቅ ሰው’ ተብሎ ባገሩ ሲጠራ
ማን ተከላከለ?
ማን ሰው ሃቅ አወራ?

ደግሞ የገረመኝ …
ከሁሉም ከሁሉም ይብሱን ያመመኝ …

‘በጭኖችሽ ሰማይ
ወጥታ ብርቱ ፀሐይ
አቃጥላ ፈጀችሽ አንቺኑ መልሳ
የቁሌት አዝመራ በነፍስሽ ነስንሳ።’

ብሎ የጻፈውን ያንኑ ደራሲ
ሲያንቆለጳጵሰው ያ ብኩን ሃያሲ

“እውነት ነው፣ ሃቅ ነው
እሱማ ታላቅ ነው።”
ብለሽ ስታወሪ፣ ላገር ስትለፍፊ
ስሰማና ሳይሽ ዘውትር ስታናፊ
አ – ቤ – ት… ስታስከፊ !

በእውነት ገረመኝ …
በእውነት አመመኝ …

ጡት ብቻ ነሽ አንቺ ?!
ጭን ብቻ ነሽ አንቺ ?!
ወሲብ ነው ገድልሽ ?!
በቃ እሱ ነው ድልሽ ?!
ህልም የለሽም እንዴ ?!
ኧረግ ወየው ጉዴ . . .

(አትመልሽው ይቅር፣ አታውሪልኝ ለኔ
ኑሪና አሳይው ለብኩን ወገኔ።)

አየሽ አንቺ ለሱ . . .
(ብታምኚም ባታምኚም)
‘አንብበሽ ማይገባሽ፣ ገብቶሽ ማትረጂ
ካገኘሽው ጋራ፣ የትም ‘ምትበ-ጂ’
ትሰሪው ትሆኚው፣ ታልሚው የሌለሽ
በቂጥሽ ከመኩራት ፥
ቁጭ ብሎ ከማውራት ፥
ወንድ ልጅ ከማርካት ፥
የዘለለ ሚና ባለም የጎደለሽ
ሸሌ ነሽ፣ ሸርሙጣ፤
ቀን እየጠበቀ ግብርሽ የሚወጣ።’

ደሞ ይሄን ያልኩሽ፣ እኔ እንዳልመስልሽ
ለስድብ ለቁጣ ፥
ለተቃውሞ ጣጣ ፥
መንገድ አደባባይ፣ ጎዳና እንዳይጠብሽ
ገላልጠሽ መርምሪው፣ ያለውን በቅርብሽ…

አውቃለሁ።

የሚያብብ ቡቃያን ብዙ ነው ረጋጩ
የደረሰ ፍሬን እልፍ ነው አፍራጩ
ብዙ ነው ገናዡ፣ ብዙ ነው በዝባዡ
ብዙ ነው በዋዡ፣ ብዙ ነው አፍዛዡ
ብዙ ነው ቀጣፊው፣ ብዙ ነው በራዡ …

መሪዎቹ ገናዥ፣ ካድሬዎቹ ገናዥ
አምራቾቹ ገናዥ፣ ነጋዴውም ገናዥ
ዘፋኞቹ ገናዥ፣ ጸሐፊዎች ገናዥ
በቀልዶች ጋጋታ፣ በፌዞች አደንዛዥ
እኔና አንቺ ደግሞ ባካኝ ተንጠራዋዥ …

“እምቢኝ አልገንዝም !
የሚያብብ ቡቃያን አላደነዝዝም !
የነገዋን ብርሃን አላደበዝዝም !”
ያለው ብርቱ ታጋይ
በነዚያኞች ሃካይ
ተጠልፎ ተጥሎ ተጋድሞበት ሃኔ
አሸልቧል ወዲያ ማንም ሳይል ወይኔ።

አንዳንዱም እስር ቤት
አንዳንዱም መጠጥ ቤት
ገሚሱም ሰው አገር
ገሚሱም ጎዳና ወደናንተ ሰፈር
ወድቋል፣ ይታዘባል
የወጪ ወራጁን ሳቅ ይመዘግባል።

ይገርማል . . . !
“ትውልድን ለማነፅጽ
ወገንን ለመቅረጽ
በሚል አጉል ቅዠት እኔ አልተነሳሁም
ጥበቤን ለማውረድ በርግጥ አልሳሳሁም
እንደመጣ ጻፍኩት
ከዚያም አሳተምኩት
በቃ ተደነቀ
ባገሩ ታወቀ።”

ይሉት መቀባጠር፣ አጉል ፍልስፍና
በአፍሪካ ምድር፣ ተስፋን ላያቀና
የተደፈርሽ አንቺን ክብር ላያፀና
አይገባኝም እኔ አታስረጂኝ እቴ
ይልቅ ነቅተሽ አንቂኝ፣ አድኚኝ ከሞቴ።

አየሽ ባገራችን . . .
ትንሽ ገንዘብና የበዛ ቲፎዞ
በግራና በቀኝ፣ ለጋሻ ተይዞ
ላውሪ ጋዜጠኛ፣ ለጣፊ መናኛ
ኪሱን ሸጉጦለት፣ ነፍቶት እንደፊኛ
ካልሆነ አይጻፍም፣ አይታተም ከቶ
ቢታተምም እንኳ አለልሽ ተረስቶ
በቁም ተዘንግቶ ።

(ይህ ሁሉ መለፍለፍ አሁን ለምንድነው
ዝብዘባ የሚያበዛ ጅላንፎ ሞኝ ነው።)

ብቻ አንቺን ሳስብሽ፣ ለዚህ ነው ‘ሚደክመኝ
እራሴን፣ ወገቤን፣ አይኖቼን የሚያመኝ …

ቢሆንም አምናለሁ!
ከጡቶችሽ ሰማይ
ከጭኖች ሰማይ
ከዳሌ ከባትሽ፣ ከሽንጦችሽ ሰማይ
የራቀ የላቀው የነፍስያሽ ሰማይ
ኃይሉን የተፋ ቀን፣ ወጥተሽ ካደባባይ
ያኔ ነው ያገሬ፣ ብርሃኗ የሚታይ
ያኔ ነው ሚነቀል፣ የሕቦቼ ብካይ።

________
አብዲ ሰዒድ
2006 E.C

Image

 
7 Comments

Posted by on March 8, 2014 in ግጥም

 

“እናቴ ትሙት አንላቀቅም!”


“ሰማህ የኔ ውድ . . .
ሳፈቅርህ ከልቤ ባንተ ተረትቼ
ስላንተው ስባክን አቅሌን ነፍሴን ስቼ
በክንድህ እያሟሟህ ባፍህ እያቀለጥከኝ
ከማያውቁት ዓለም ወስደህ እየከተትከኝ
ነፍሴን አስክረሃት በሀሴት ዳንኪራ
እንዳልቆም እንዳልሄድ ያላንተ እንዳልሰራ
አድርገህ ጠፍረህ እንዲህ አሳስረኸኝ
እሄዳለሁ ብትል ከመንገድ ጥለኸኝ
እናቴ ትሙት አንላቀቅም
እኔ በፍቅር ቀልድ አላውቅም!”

ስትይኝ ፈራለሁ
አንዳንዴም ኮራለሁ
አንዴ ደስ ይለኛል
አንዳንዴ ይጨንቀኛል።


“እየውልህ ውዴ . . .
እኔማ ስወድህ ሁኚ ያልከኝን ሆኜ
የኔን ዓለም ትቼ ባንተ ዓለም መንኜ
ጠቅልዬ ግብቼ ከገዳምህ ዋሻ
በስምህ ፀልዬ ሃጢያቴን ማስረሻ
እንደሆነ መቼም አንተም ታውቀዋለህ
ከቶ ያልሰጠውህ ኧረ እንደው ምን አለህ
ታዲያ ሁሉን ወስደህ ባዶዬን ቀርቼ
ኑሮዬን በሞላ አንተው ላይ ገንብቼ
ስታውቀው እንዳልኖር አንተን ተለይቼ
እሄዳለሁ ብትል ድንገት አንቺን ትቼ
እናቴ ትሙት አንላቀቅም
እኔ በህወት ቀልድ አላውቅም!”

ስትይኝ ፈራለሁ
አንዳንዴም ኮራለሁ
አንዴ ደስ ይለኛል
አንዳንዴ ይጨንቀኛል።


ሰማሽ የኔ እመቤት . . .
እውነት አንቺን ርቄ
እምነትሽን ፍቄ
በፍቅርሽ ቀልጄ
ሌላ ሴት ለምጄ
ምኖር ይመስልሻል ?!
እውነት እውነት እውነት
በእውነት ተሳስተሻል !
ደግሞ ፉከራሽን ዛቻሽን ፈርቼ
እንዳይመስልሽ ውዴ እኔስ ተረትቼ!

ይልቅ እኔም አልኩሽ . . .
እናቴ ትሙት አንላቀቅም
ካንቺስ ወዲያ ሴት አላውቅም።
_______
አብዲ ሰዒድ
2004 E.C

Image

 
Leave a comment

Posted by on December 31, 2013 in ግጥም

 

ጌሾና ፍቅር

ቃሌን ተቀበይኝ በብቅል በጌሾ
ተጠርጎ እንዲወጣ የቂማችን ቁርሾ
ሰክረው ያስቀየሙት ማግስቱን ይረሳል 
በጨብሲ የገነቡት አይዘልቅም ይፈርሳል
ቢሆንም ዛሬን ነይ ነገ እንደሁ ይደርሳል።

ውዴ ሆይ ነይልኝ 
በይ ጠጪ እንጠጣ
ሰላምና ፍቅር ባገር እንዲመጣ !

ደግሞ ይሄን ጡትሽን እስቲ ሸፈን አርጊው
የባላገር ነፍሴን ሰው ፊት አታባልጊው። 

እናልሽ ዓለሜ . . . 
አፈር የሚገፋው ያ ሚስኪን ገበሬ 
ተስፋው እየፈጀው ልክ እንደ በርበሬ
አንጀቱን አጥብቆ ወኔውን ሰንቆ 
ለዓላማው ፅናት እግሩን ሰነጣጥቆ
በደደረው መዳፍ ላቦቱን ሞዥቆ …

“አንተ ስትደርስልኝ አደርጋለሁ ጫማ
ለክብርህ ለግብሬ ለስምህ ሚስማማ 
በል በርታልኝ ልጄ ዝመት ወደ አስኳላ
ቀለም የለየ ነው ደህነኛ ‘ሚበላ!” 
ብሎ የሸኘኝን ከዚያ ከገብስ እርሻ 
የጀግናው አባቴን ድህነት ማስረሻ 

እንዲሆነኝ ፍጠኝ 
ነይ ጠጪ እንጠጣ
ችጋር ድንቁርና ካገር እንዲወጣ !

ኧረ ተይ ጭንሽን አንሺው ከፊቴ ላይ
አልታይ ይለኛል ካንቺ ወዲያ ሰማይ። 

ደግሞም ብትፈልጊ ግብርና ማጥናቴ
በሰብል ምርምር ጥበብ መገብየቴ 
ያባቴን ገብስ እርሻ ላዘምን ላስፋፋ
በጉልበት ሳይደክም በእውቀት ላፋፋ
አልሜ ወጥኜ ግቤን አሰልፌ
ነበር የተማርኩት ከሰው ተጣድፌ
ቀረሁኝ ፒያሳ ቢራዬን ታቅፌ።

ኦሆሆይ ፒያሳ …
አሃይ ቼቺኒያ …
የደፈረሽ ይውደም እናት ኢትዮጵያ!
ዘራፍ ብሎ ገዳይ የጀግና ልጅ ጀግና
ድህነቱን ታቅፎ፣
እውቀቱን ጨንግፎ፣
ሽል ተስፋውም ረግፎ፣ ይጠጣል ያውና!

እኔ ምልሽ ውዴ . . . 
ባለፈው ከኮሌጅ የተመረቅሽ ለታ
መንደርተኛው ሁሉ ሲጨፍር በሆታ
እናትሽ በኩራት ኮንጎዋን ተጫምታ
ዘመኗን በዚያች ለት ሹሩባ ተሰርታ
በበለዘ መልኳ በቅን ልቧ ፈክታ …

“ብሞትም አይቆጨኝ አልቀረሁ ለፍቼ
አንቺን መሳይ ሃኪም ለቀበሌ አፍርቼ
የትልቋ እህትሽ የገነት መካሻ 
የከሰለ ልቤን ሃዘኔን ማስረሻ
እሷ እንደው ተቀጨች አዋላጅ ነርስ አጥታ
አምላክ ባንቺ ካሰኝ ለወገን መከታ”
ብላ እንደሳመችሽ ባስታወስኩት ጊዜ
ያንዘፍዝፈኛል የያዘኝ አባዜ። 

የቀዬው ሰው ሁሉ ዶክተር መጣች ሲሉ
ካዛንችስ ተገኘች ልጅት በመሃሉ 
ምነው በሌሊቱ?!
ምነው በውድቅቱ?! 
አይሻልሽም ወይ ቀን መርፌ መውጋቱ?! 

እያለ እንዳይዝሽ ይህ ነዝናዥ ህሊና
በይ ጨለጥ አርጊበት ደብል አስቀጂና
ውዴ ሆይ በይ ጠጪ
አይዞሽ እንጠጣ
እድገት ብልፅግና ባገር እንዲመጣ !

ኧረ ተይ አንቺ ልጅ …
ባጭር ቀሚስሽ ላይ ፍም ጭንሽ ተጋልጦ
እንደ እናትሽ ቅቤ ጨረሰኝ አቅልጦ።

ኦሆሆይ ካዛንቺስ …
አሃይ ቼቺኒያ …
ደህና ቀን ይውጣልሽ እናት ኢትዮጵያ።
________
አብዲ ሰዒድ 
2006 E.C

Image

 
Leave a comment

Posted by on December 28, 2013 in ግጥም

 

ተስፋ ስንት ያወጣል?!

 

ሰው በሰው ጨክኖ ቀን ሲለብስ ጥቀርሻ
ሕልሙ የጨለመበት ያስሳል መሸሻ
እግሩን ተከትሎ
ተስፋን አንጠልሎ
አዲስ ቀንን ስሎ
በሄደበት መንገድ በጀመረው ጉዞ
ወየው ማለት ሆነ እሬሳውን ይዞ።

ወየው!… ወየው!… ወየው!…
ሰዉስ ስንቱን አየው …

ተስፋ ስንት ያወጣል ምንድነው ተመኑ?
በይሆናል ምኞት ስንቶቹ ባከኑ
ስንቱ መንገድ ቀረ… ስንቶቹ ረገፉ?!
ስንቶቹ ሰመጡ… ስንቶች ተቀጠፉ?!

ዋይታ ብቻ ሆነ ዝምምም ብሎ ለቅሶ
ለድጋፍ የሚሆን ጉልበታችን አንሶ
አቅማችን ኮስሶ
በደላችን ብሶ . . .

እንጉርጉሮ ቢወርድ ቢደረደር ሙሾ
በግፍ ለጨቀየው ለዚያ ለቂም ቁርሾ
ላይሆን መተንፈሻ ሃዘን ማስታገሻ
ለከሰሉ ነፍሶች የእምባ ስር ማበሻ

በቃኝ ማለቃቀስ
እምቢኝ ወይኔ ወይኔ
የትም አይቅርብኝ ቸር ይደር ወገኔ።

አጥንቱ አይቆጠር አይለቀም አፅሙ
በቀለም በገፁ አይለይ በስሙ
ለክቡር ሰው ገላ ወፎች አይሻሙ
አይብላው አሞራ
አይከታትፈው አውሬ
ዝም አትበይ ተነሽ!… እሪ በይ አገሬ !!!

ተስፋ ስንት ያወጣል ምንድነው ተመኑ?!
በይሆናል ምኞት ስንቶቹ ባከኑ
ስንቱ መንገድ ቀረ… ስንቶቹ ረገፉ
ስንቶቹ ሰመጡ … ስንቶች ተቀጠፉ?!…
__________________
__________________

በይሆናል ተስፋ…. በይሳካል ተስፋ… በየበረሐው ለሚባክኑና ለባከኑ ነፍሶች!!
ሰላም ፍቅርና ሕብረት ከለሁላችን ጋር ይሁን!!!

አብዲ ሰዒድ
ብጥስጣሽ ሃሳቦች (bT’sT’ash) . . .

Image

 
Leave a comment

Posted by on October 20, 2013 in ግጥም

 

ዘ – ም – ዘ – ም !

 

በዚያ ሐሩር ምድር፣ በዚያ ጠፍ በረሐ
ከደም ተቆራርጠው የሰው ልጅና ውሃ
ሕይወት ልታከትም ተይዛ ገርገራ
በዘምዘም ጠብታ ሕላዌዋ በራ።

ሃጀር ተራወጠች ሰፍዋና መርዋ
ለአንድ ልጇ ጥማት መች ዛለ ገላዋ
እሪ በል እስማኢል አልቅስ ተንዘፍዝፈህ
በእንባህ ዘለላዎች በል ያዛት ቀስፈህ።

እናት ዓለም ልፊ፣ ወዲህ ወዲያ ቃኚ፤
ያንቺን ጥማት ሽረሽ፣
በአሸዋው ዳክረሽ፣
ለአብራክሽ ክፋይ፣ ለእስትንፋስሽ ባክኚ።

በመካከል ሩጪ፣ በላይ ተራመጂ
ከወደዚህ ማትሪ፣ ደግሞም ከዚያ ሂጂ፤
ጠብቂው በዓይንሽ፣
ፈልጊው በእግርሽ፣
ርሃብ ጥማትሽን ለልጅ ፍቅርሽ ማግጂ።

አንድ! ሁለት! ሶስት! አራት!
ጉልበት እያጠራት . . .
አምስት! ስድስት! ሰባት!
ሕልሟ እየራቀባት …
ቀልቧ እየሳሳባት …
እ – ና – ት!
አቤት እናት!

በዚያ ሐሩር ምድር፣ በዚያ ጠፍ በረሐ
ከደም ተቆራርጠው የሰው ልጅና ውሃ
በዘምዘም አገኙት የነፍስን ፍሰኃ።

በል እስማኢል ጠጣ፣ ሃጀር ሆይ ጥገቢ
ላንቺም ለልጅሽም ዘምዘምን መግቢ።
እፈሽው በእጅሽ፣
አዳርሽው በዓይንሽ፣
ርኪበት በነፍስሽ፣
በአሸዋ፣ በኮረት፣ ከልይው በድንጋይ
የ’ናትነትሽ ጥግ ዝንታለም እንዲታይ።

“ዞሚ!” … “ዝሚ!” … “ዞሚ!” …
ድምፅሽን አሰሚ!
ትውልድሽን ካድሚ።

ተጓዥ መንገደኛው ይረፍ ባንቺ መንደር
“ሻባእ” “ሻባእህ” እያለ መርካቱን ይናገር።
ኃይል ብርታት ይሁን ለመኖርሽ ተስፋ
የጤናሽ ምልክት ይኑር እንዳይጠፋ።

“ዞሚ!”… “ዝሚ!”… “ዞሚ!”
ድምፅሽን አሰሚ!
ዓለምሽን ካድሚ።
___________
2006 E.C
አብዲ ሰዒድ
ኡፕሳላ፣ ስውዲን

HAPPY EID TO ALL MUSLIMS
❤ EID MUBAREK ❤

Image

 
2 Comments

Posted by on October 15, 2013 in ግጥም

 

ጀ – ሚ – ላ !

የዓይንን አሰራር ጥበብ ያላወቀ፣
የጥርስን ተፈጥሮ ልክ ያላደነቀ፣
የቁመናን ልኬት ሚዛን ያልጠበቀ፣
ጀሚላን ቢያገኛት አወቀም ፀደቀ።

ቁም ነገር ወዴት ነው በማን ተወሰነ?
መልካምነት የታል እንዴት ተከወነ?
እውቀትስ ምንድን ነው የት ተተነተነ?
ከጀሚላ ወዲያስ ይህ ሁሉ ባከነ።

አልሐምዱሊላሂ ደርሶናል በረካ
በጀሚላ ፍቅር ቀልባችን ተነካ።

የቀሚሷ ፀዳል፣ የሂጃቧ ግርማ
የእርምጃዋ ስክነት፣ የገጿ ከራማ
የአንደበቷ ለዛ፣ የቃሏ ጥፍጥና
ማር ተምር ቢሏትስ መች ይበቃትና።

በዚህ ቁንጅና ላይ የአምላክ ፍራቻ
ተጣጥባ ተጣጥና ወደ መስጅድ ብቻ
ባያት አልሰለቻት አይነቀል ዓይኔ
የፍቅር ዓለም ሱሴ የነፍስ ኹረልዓይኔ።

አልሐምዱሊላሂ ደርሶናል በረካ
በጀሚላ ፍቅር ልባችን ተነካ።

እይዋት ስትመጣ . . .

ሽውው አለ ነፋሱ ሞገዱም ረገበ፣
ቀሚሷም ለአመል ያው ተርገበገበ፣
(ሸርተት አለ ሻሿ መልሰችው በእጇ
አምባሯን አየሁት ሲገለጥ ግዳጇ)
አትሞቅም አትበርድም ፀሐይዋም ልከኛ፣
ዛፎች ቅጠሎቹ ሆነዋት ምርኮኛ።

አበባውም ፈካ፣ ችግኙም ፀደቀ፣
ያገር ሽማግሌው በስሟ አስታረቀ፣
እናቶች ለክብሯ አወጡላት ዜማ፣
የጓዳ እድርተኛው ለቅሶውን ተቀማ።

ጀሚላ መኣረይ፣ ጀሚላ በሬዱ
ጀሚል ሸኮሪና፣ ጀሚል የውዱዱ
ጀሙ ጀሚላዬ፣ የሰው መጨረሻ
በፍቅር የሰራሽ፣ የውብ መዳረሻ።

አልሐምዱሊላሂ ደርሶናል በረካ
በጀሚላ ፍቅር ልባችን ተነካ።

እዪዋት ብቅ ስትል

’ሚያላዝነው ውሻ ብሶቱን አቆመ
ጭራውን ቆላና ፊቷ ተጋደመ።
ድመት ተንጠራራች ስስ እግሯ ረዘመ
‘አጃኢበ ረቢ’ ፍጥረት ተደመመ።

እርግቦች በዜማ እርግብኛ አወሩ
ጎጆአቸውን ረስተው በሽቶ ሰከሩ
ደነሱ ዘመሩ፣
ጨፈሩ ፎከሩ፣
ክንፋቸው ተማታ፣ ወደ ላይ በረሩ
”ምን አይነት ውበት ነው?!”
”ምን አይነት ሽታ ነው?!” እያሉ እያወሩ።

ጀሚላ መኣረይ፣ ጀሚላ በሬዱ
ጀሚል ሸኮሪና፣ ጀሚል የውዱዱ
ጀሙ ጀሚላዬ፣ የሰው መጨረሻ
በፍቅር የሰራሽ፣ የውብ መዳረሻ።

አልሐምዱሊላሂ ደርሶናል በረካ
በጀሚላ ፍቅር ስስ ልባችን ተነካ።

ምነው ባደረገኘ ቁርአን ማስቀመጫ
በስስ እጇ ዳብሳኝ ባገኝ መተጫጫ
ኧረ ምነው በሆንኩ ምንጣፍ ወይ ስጋጃ
ግንባሯ እንዲነካኝ ስታስገባ ምልጃ።

እንደመታጠቢያሽ እንደ ውዱእ ውኃ
ልቤ ፈሰሰልሽ በፍቅርሽ በረሃ
እስቲ በይ ቁጠሪኝ ልክ እንደ ሙስበሃ
በሚፈትለኝ ጣትሽ እንዳገኝ ፍሠሐ።

ጀሙ ጀሚላዬ፣ የሰው መጨረሻ
በፍቅር የሰራሽ፣ የውብ መዳረሻ።
ስለፍቅር ብለሽ፣ በአላህ በነቢ
የኒካውን ቀልቤን፣ ከቀልብሽ አስገቢ፤
አቤት ያንቺስ ውበት …
አቤት ያንቺስ ፍቅር …
. . . አ
. . . . . . ጃ
. . . . . . . . . ኢ
. . . . . . . . . . . . በ
. . . . . . . . . . . . . . . ረቢ።

/አብዲ ሰዒድ/
ተፃፈ 2005 E.C
ስቶክሆልም፣ ስውዲን

 Image

 
Leave a comment

Posted by on September 21, 2013 in ግጥም

 

እዚህ እና እዚያ

እዚህ ᎐ ᎐ ᎐

ነጋሪት፣ ከበሮ ፡ ሲጎሰም ሲመታ
ጋሻ ጦር ተሰብቆ ፡ ሲነፋ በእምቢልታ
መለከት፣ ጸናጽል፣ አታሞ ሻኩራ
በሕብረ ዝማሬ ፡ በመድፍ እያጓራ …
ሽለላ እየደራ
ሻማም እየበራ
ፉከራ ቀረርቶ ፡ ያፈኞች ቱማታ
እዩልኝ ስሙልኝ ፡ ያድር ባይ ድንፋታ
ያደነቁረናል ፡ ያለ ቅንጣት ፋታ !

ስሟቸው !…
“የምልጃ ታቦቴ
አድባር ጉልላቴ
ምልክቴ ጌጤ
ማተቤ ነህ ፈርጤ…”
ሲሉ ሲባባሉ
በስም ሲማማሉ
ሲ – ሸ – ነ – ጋ – ገ – ሉ !


. . . ያ
. . . . . . ስ
. . . . . . . . . ጠ
. . . . . . . . . . . . ሉ !!!

እዚያ ᎐ ᎐ ᎐

እዬዬና መርዶ፣ የእድር ጡሩንባ
ያስለቃሾች ዋሽንት፣ ያላቃሽ አዞ እምባ
ለዛ የለሽ ዜማ፣ ጣዕም የለሽ ንፍሮ
ቅጥ የለሽ ንፍረቃ፣ ገጽ አልባ እንጉርጉሮ …

ዝርጠጣ፣ ፍርጠጣ
የስሜት ሽምጠጣ
ልዝቡን ከግልቡ ብረዛ ቅየጣ . . .

ደራሽና ገስጋሽ ፡ ላይሆኑ ዘላቂ
በጅምላ ሲነዱ ፡ ሕዝቤን አሳቃቂ
ደግሞም አስጨናቂ
“ስስ ብርሃን ፈንጣቂ”
ግርዶሽ አሟሟቂ
ውዥንብር ናፋቂ . . .

ስሟቸው !…
“ተፋጀ ተጣላ
እርስ በርስ ተባላ
ሞተ ተሰደደ
ተቃጠለ አበደ …

አትነሳም ወይ አትለውም ጎኑን
ደምህን ታቅፈህ ከምትድህ ዘመኑን”
እያሉ እያስባሉ እሳት እየጫሩ
በስም ላይ ስም ጭነው እየተሞሸሩ…

“አዋቂው … ልሒቁ
ረቂቁ … ምጡቁ
ታጋዩ … አርበኛው
የፍትህ እረኛው
አንተ ብቻ ዳኛው “

“ከኛስ ወዲያ ላሳር – ለሕዝባችን ግርማ
እጃችን ያልነካው – ሁሉም ነው ጨለማ።”
ሲሉ ሲፈርጁ በመንጋ ሲያስቡ
ጽድቅና ኩነኔን ባንድ ገጽ ሲከትቡ
ሲያረቁ ሲያፀድቁ
በቃል ሲያስመርቁ
ሲ – ያ – ጨ – መ – ላ – ል – ቁ !


. . . ያ
. . . . . . በ
. . . . . . . . . ሽ
. . . . . . . . . . . . ቁ !!!

እዚያና እዚህ ሆኖ የህልማችን ጫፉ
ስንፋተግ አለን ቀኖች ሲቀጠፉ
እስኪ እንጠጋጋ ወፎቹ እንዳይረግፉ።

/ አብዲ ሰዒድ – 2005 E.C /

Image

 
Leave a comment

Posted by on August 26, 2013 in ግጥም

 

የራስ ጨዋታ !

ዛፍ ተጥሏል አሉኝ ማዶ ከዚያ መንደር 
ጉዞ ጀምሬያለሁ ማገዶ ልበደር። 
መንደርተኛው ሁሉ መጥረቢያውን ታጥቆ 
ግንድ ይሸነሽናል ሥሩን ሰነጣጥቆ። 

ፍልጡስ ይጠቅመናል ግዴለም ፍለጡ
ግን አደራችሁን ችግኝ አትርገጡ። 
ቡቃያውም ይዟል አምሮበታል ሰብሉ
ምነው ባያረግፉት ወፎች እየበሉ። 
*
ወፍዬ ወፊቱ 
ወፍዬ ወፊቱ
የታደልሽ ፍጥረት ባለጸጋይቱ።

አታርሺ አትዘሪ
ፍቅር ነሽ ስትዞሪ
ማንስ ይከስሻል አገዳ ብትሰብሪ።
*
እኔስ አልዘረጋም፣ ወንጭፌን ጨክኜ
የደም ጎጆ አልሰራም፣ ጠጠር አባክኜ።
ይድላት ትፈንጭበት፣ ያውላት እርሻዬ
የተረፈው ይበቃል፣ አይጠፋም ድርሻዬ
ወፍዬን አትንካት፣ በል ተዋት ባሻዬ።

አንዳንዴ ደግ ነው፣ አንዳንዴም ይከፋል 
የቀበሌው ባሻ፣ ያለማል ያጠፋል። 
ዝንጉርጉር ነው ሆዱ፣ አይለይም መልኩ
ይጠባል ይሰፋል፣ አይታወቅ ልኩ 
ለወፍ ይታጠቃል፣ ጀግና ነው ምትኩ። 
*
ወፍዬ ወፊቷ 
ወፍዬ ወፊቷ
አልጠረጠርሽም ወይ ልበ መልካሚቷ።

ባታርሺ ባትዘሪ 
ፍቅር ብትዘምሪ 
አይተዉሽም እኮ ተይ አትዳፈሪ።

/አብዲ ሰዒድ/
Image

 
Leave a comment

Posted by on August 2, 2013 in ግጥም

 

/ ማስታወቂያ ! /

ታላቅ ብለን ያልነው የሰቀልነው ከላይ
ይፈርጥ ጀምሯል እንደበሰለ እንቧይ
ይወርዳል፣ ይዘቅጣል ይሰራል አምቡላ
ማር ጠጅ እንዳልነበር ይሆናል አተላ።

እንደጥሬ እንቁላል ከእጅ እንደወደቀ
አያነሱት ነገር ተጨመላለቀ 
ቦካ ተለወሰ … አካሉ ረከሰ
ገማ በሰበሰ … ሃሳቡ ኮሰሰ።

አድንቀን … አድንቀን 
መርቀን … አፅድቀን 
ሳይቸግር አርቅቀን 
ድንገት አሳቀቀን! 
ኧረ አሸማቀቀን!

ህልማችን መከነ፣ ተስፋችን ተነነ 
ትክን አለ አረረ፣ ውስጣችን በገነ
“ሀ”ብለን ተነሳን፣ ያለፈው ባከነ 
ወየው ታናሽነት !
ወየው ርካሽነት !
‘ወየው… ወየው… ወየው 
እኔስ ስንቱን አየው’ 
ወየው ብለን ቀረን፣ ፀጉራችን በነነ!


… ቃ
….. ጠ
……… ል
……….. ን !

ከንግዲህስ ወዲያ አቋም አውጥተናል!
ላልተወሰነ ቀን፣ 
… ላልተወሰነ ማታ፣
…… ላልተወሰነ ዘመን 

ማድነቅ አቁመናል!
…… ማክበር አቁመናል!
……… አጉል ማሞጋገስ መስቀል አብቅተናል!

መ፟ሸ፟ንገል፣ መ፟ደለል
መ፟ገ፟ፈተር፣ መ፟በደል 
መታሸት፣ መ፟ቀ፟ሸር
መ፟ፈ፟ተግ፣ መበጠር 
መሰጣት፣ መ፟ከካት 
መታመስ፣ መቆላት
መ፟ሰልቀጥ፣ መበላት 
ከንግዲህ በቅቶናል!
ይኸው በአቋምችን ላንዋዥቅ ጸንተናል!

ላልተወሰነ ቀን፣ 
… ላልተወሰነ ማታ፣
…… ላልተወሰነ ዘመን 

ማድነቅ አቁመናል!
…… ማክበር አቁመናል!
……… አጉል ማሞጋገስ ማሽቋለጥ ትተናል!
ይልቅ ለጎጇችን ለራስ በርትተናል!!!

//©አብዲ ሰዒድ //

Image

 
Leave a comment

Posted by on August 2, 2013 in ግጥም

 

“ተው ስማኝ ሃገሬ!”

እኔ እዚህ እየጮህኩኝ፣ እሱ እዚያ እየተኛ
በምን በኩል ይሆን የኛስ መገናኛ ?!
መጠየቄን አልተው፣ ዛሬም እጮሃለሁ
መልካም ቀን ይመጣል፣ አይቀርም አምናለሁ።

‘ባካችሁ ቀስቅሱት ያንን ባለ ተራ
የተሸከመው ቃል አለበት አደራ።
ምነው ለገመሳ ምነው ደነቆረ ?!
በገደል ማሚቱው ድምፄ ውሎ አደረ። 

ተሰማ አስተጋባ ይኸው ዳር እስከዳር 
አውቆ ተኝቶበት ሲያመቻቸው ለአዳር 
ዛሬም አልረፈደም ቀን አለን ወዳጄ
በል ስማኝ ጩኸቴን ብያለሁ ማልጄ።

አማን ሰላም ይሁን፣ ቸር ይዋል መንደሩ 
በፍቅር ይሻላል፣ ተሳስቦ ማደሩ።
ሃገርህ ሃገሬ፣ ርስትህም ናት ርስቴ
አብረን እንገንባት ተው ስማኝ በሞቴ።

ተው ስማኝ ሃገሬ 
ተው ስማኝ ሃገሬ 
ምነው መጨነቄ፣ ምነው መቸገሬ።

የተቀመጥክበት ዙፋንህ ቢደረጅ 
አያልፍ እንዳይመስልህ ተው አታስጠናኝ ደጅ
ይልቅ ፅደቅበት መልካም አድርግና
ለዘመንህ ክብር ለስምህ ልዕቅና።

የከርቸሌውን በር ከፈት አርገው ባሻ
ህብረት ነው ‘ሚበጀን እስከመጨረሻ !
ፍቅር ነው ጥረቴ፣ ሳላም ነው ብርታቴ 
እታገልሃለሁ፣ አይደክምም ጉልበቴ።

የነጃሺን አድባር፣ የቢላልን ምድር 
የሙአይመንን ጡት፣ የረሱልን ፍቅር
በሳላም ልጠብቅ ላልደፍር ላልነካ
እኔስ ቃል አለብኝ በጡት የተነካ።

ዝምታህ ይከብዳል፣ እኔስ ሰግቻለሁ
አስረግጠህ ስማኝ፣ ተው ጓዴ ብያለሁ
ቃሌን ተቀበላት፣ ያው አስረክቤያለሁ።

ተው ስማኝ አገሬ 
ተው ስማኝ አገሬ 
በዛ መጨነቄ፣ በዛ መቸገሬ።
_________
(አብዲ ሰዒድ)

Image

 

 
Leave a comment

Posted by on August 2, 2013 in ግጥም