RSS

Monthly Archives: January 2014

ዘ – መ – ቻ !

አያቴ ኮርያ ዘማች ነበር። እናቴ ቡና አፍልታ መንደርተኛው በተሰበሰበ ቁጥር ምክኒያት እየፈለገ ስለ ኮሪያ ማውራት ይወዳል።

<< እኛኮ ለዓለም ኩራት ለሃገርም ክብር ነን!… እዚህ ተጥለን ብንታይ ዝናችን የተረሳ እንዳይመስላችሁ… በሄድንበት ያገራችንን ስም ከፍ አድርገን ኒሻን በኒሻን ተምነሽንሸን… በሊጎፍኔሽን አርማ ደምቀን… ባገራችን ባንዲራ አሸብርቀን… የተመለስን ጀግኖች ነን!… አታዩትም ግርማ ሞገሴን!>>… እያለ ያቺን ለዘመናት ያየናትን ጥቁር ፎቶ ያሰየናል… አያቴ ሙሉ የጦር ልብሱን ገጭ አድርጎ የለበሰባትን ፎቶ…

እውነቱን ነው!… አያቴ ያምራል… ግርማ ሞገሱ ያስፈራል… ቆራጥ አመለካከቱ ያስደነብራል… እንዲህ አርጅቶ እንኳ አትንኩኝ ባይ ነው… እማዬ ለምን ይሄን ፎት ፊት ለፊት እንደሰቀለችው ግልፅ ነው…. አያቴ ምንም ከምታደርግለት የጥንት ፎቶውን እያየህ ስለ ኮሪያ ብትጠይቀው እንደወደድከውና እንዳከበርከው ይረዳሃል… “አረጀህ፣ ደከምክ፣ አረፍ በል፣ ተኛ ፣ተነስ…” ምናምን ልትለው ብትሞክር ግን ይጣላሃል.. “ወግድልኝ!… የኮሪያ ዘማች እኮ ነኝ”… እያለ ይሸልልብሃል… ከቶም እጅ አይሰጥም!… ቆራጥ… በራሱ ብቻ መቆም የሚሻ ደፋር ሰው ነው… ብልጧ እናቴም ይህን ባህሪውን ጠንቅቃ ስላወቀች ተጠቅማበታለች… ባይሆንማ አያቴ እንደሞተ ፎቶውን አታነሳውም ነበር… እሺ ከዚያ በኋላ ፎቶው የት ገባ?!… ያያቴ ፎቶ የት ደረሰ?!… ያን ምርጥ ታሪካዊ ፎቶ ምን ወሰደው?…

<< እንደው ማማሩስ ጥርጥር የለው… መቼም ያላዩት አገር የለ… ይሄ መቼ መሆኑ ነው ታዲያ?>> ይጠይቃሉ የጦቢዬ እናት… አያቴም ፊቱ በደስታ እየፈካ… ቡናውን በፍቅር እያጣጣመ… ኮሌታውን እያስተካከለ… አፉን በእጁ እየሞዠቀ ይመልሳል…

<<ይሄማ ከዘመቻው ቀደም ብሎ ነው… በግርማዊነታቸው ቆራጥ ንግግር “ቃኘው ሻለቃ” አርማውን ከዣንሆይ እጅ ተቀበሎ በተሸኘ ጊዜ… አይ ዣንሆይ!… ያደረጓት ንጥር ያለች ንግግር!… የዋዛ ንግግር እንዳይመስላችሁ… ዣንሆይ እንዲሁ በከንቱ ቃል አያባክኑም… ሁሏም ቃላቸው ፍሬ አላት… እስታሁን እንኳ መልክታቸው አይዛነፈኝም>>

ሬዲዮኑን አስተካክሎ እያስቀመጠ ይቀጥላል… አያቴና ሬዲዮ ተለያይተው አይቼ አላውቅም… የዜና ፍቅሩ ሁሌም እንደገረመኝ ነው… በሄደበት ሁሉ በካኪ ጨርቅ የተሸፈነችው ሬዲዮ ከእጁ አትጠፋም…

<< እናላችሁ በተጠንቀቅ ለተዘጋጀነው የቃኘው ሻለቃ አባላት በሙሉ የጦር አርማውን እያበረከቱ ዣንሆይ እንዲህ አሉ… ‘ይህንን የጦር መለዮ ዓላማ በምታደርጉበት ጦርነት ሁሉ በጀግንነት ከፍ አድርጋችሁ ትይዙታላችሁ።… ለኢትዮጵያ ነፃነት ከብዙ ሺህ ዓመት ጀምሮ የተጋደሉት ጀግና አባቶቻችሁ መንፈስ ይከተላችኋል፤ በጦር ሜዳ ክንዳችሁን ያፀናል፤ ልባችሁንም ያበረታል!’…>>

<< እውነት ነው ጀግንነት ከደማችን ነው ሐበሻ ተደፍሮም አስደፍሮም አያውቅም>> ጣልቃ ይገባሉ እትዬ ሸጌ…

<<ታዲያሳ!… መይሳው ካሳም ቢሆን ያን የንግሊዝ ጭባ ሁላ እያዳፋ መድፍ ሲያስቀጠቅጠውና ወባ እንደያዘው ቆለኛ ሲያንቀጠቅጠው ነው የኖረ… ምኒሊክም ቢሆን ያን ሶላቶ ጣልያን በዱር በገደሉ ሲያርበደብደው ነው የከረመ… ጥበበኛዋ ጣይቱም ብትሆን ለአርበኛው ጠጇን እያስጣለች ሶላቶውንና ባንዳውን ውሃ ውሃ እያሰኘች በእንፉቅቅ ያስኬደች ጀግና ናት… አባቴ ራሱ በሚኒሊክ ጊዜ አርበኛ ነበር… ስንቱን ያርበኛ ጀብዱ እንዳጫወተኝ ባወጋችሁ ዘበኑም አይበቃን>> …

አያቴ ላፍታ በዝምታ ትንፋሽ እየወሰደ ይተክዛል… በትዝታ አባቱን እያሰባቸው ይሆናል… የቡና እድምተኛም በጉጉት ይጠባበቃል… አያቴ የሚነግረን ታሪክ ተመሳሳይ ቢሆንም አይሰለችም… እሱ ሲያወራው የሆነ እንዳይሰለች የሚያደርግ ነገር አለው… ሁላችንም በጉጉት እንዲቀጥል እንጠብቃለን… አያቴም ቤቱን ገርመም ገርመም አድርጎ ጨዋታውን ይቀጥላል …

<< እኛም ታዲያ ጀግኖች አባቶቻችንንም ሆነ ዣንሆይን አላሳፈርንም!… ሃገራችንንም በሽንፈት አላስጠራንም!… በተሰለፍንበት ውጊያ ሁሉ አልተበገርንም… አንድም የቃኘው ወታደር እጁን አልሰጠም!… ከ16 ሃገራት የተሰበሰበው ተዋጊና አዋጊ ሁላ እኛን እንደ ተአምር ነበር የሚያየን… ‘ኢትዮጵያውያን ከሰው ፍጡር በላይ ናቸው’ እስከመባል ድረስ ተደርሶ ነበር… በዚያ መሳይ ከባድ ውጊያ ባጠቃላይ በክብር የተሰዋው የቃኘው ወታደር 120 አይበልጥም… ቁስለኛውም ቢሆም ከሌላው አንፃር ሲታይ እምብዛም ነው!>>

የአያቴን በወኔ የተሞላ ንግግር በገብረ ክርስቶስ ግጥም እያወራረድኩ… እኔም አብሬው ዘምቼ እመለሳለሁ…

“… ደስታና ሐዘን በቦታው ጨፈሩ
ሣቅ ለቅሶ እየሆነ እምባ ሄደ በግሩ
በያይነቱ ኒሻን ጠመንጃ ሸክሙ
ወቴ ከነደሙ
እዚህ ይዞ መጥቷል ከሩቅ ከኮሪያ
ተቃጥሎ ይጋያል የባቡሩ ጣቢያ
. . . . . . . . . ብቻ እዚህ አይደለም…”

ከዘመቻ ሲመለስ ባቡር ጣቢያ ሄጄ የተቀበልኩት ያህል ይሰማኛል… ሁሌም ትረካው እንደተዋሃደኝ ነው…

<<አንቱ እንደሁ እድለኛ ኖት… በደጉ ዘመን ሁሉን አሳልፈዋል… ጥጋቡንም ዓለሙንም እስኪበቃዎት አይተውታል… ምን ቀሮት እቴ!>> እማማ ዘኔ ናቸው…

<<ይመስገን… ይመስገን… ደግሞ አንቺስ ብትሆኚ ምን ቀረሽና ነው… ኮሪያ ባትዘምቺም መቼም ከኮሪያ ዘማች ጋር ሳትኮምሪ አልቀረሽም… እሱም ቢሆን ዝና ነው እኮ… እኛ እንደሁ ብርቅ ነበርን… አሃሃ… ጥጋቡንማ ተይኝ!… ዣንሆይ እኮ በችጋር ለተጎዱትና ይልሱት ይቀምሱት ለቸገራቸው የፓኪስታን ዜጎች አይዟችሁ እግዜር እንደሰጠን እንሰጣችኋለን ብለው ረብጣ ዶላር ለሩዝ መግዣ ይሰዱላቸው ነበር!>>

<<እንዴ አባ ኢትዮጵያ እርዳታ ትሰጥ ነበር እንዴ?!>> እጠይቃለሁ እኔ

<<ኋላስ!… ስንቱን ረሃብተኛ ከረሃቡ ታድጋው የለ እንዴ!… ስንቱን ችጋራም አርጥባው የለም እንዴ!… ምድራቸው እህል አላበቅል ሰማያቸውም ውሃ አላፈስ ብሎ በረሃብና በቸነፈር ሲቀጣቸው አይዟችሁ ብላ የለም እንዴ!… ስማ ልጄ! ይህች ለምለም ሃገር እኮ ታላቅ ናት!… ዛሬ ተራቁታ ብታያት የዋዛ እንዳትመስልህ… በወስላቶች ዝርፊያ የደኸየች ቢሆንም ሃብታም ነበረች…. ደግሞም ዳግም ማበቧ አይቀርም!>>

የአያቴን በተስፋ የተሞላ ንግግር እያዳመጥኩ… እርዳታ አድራጊዋን ኢትዮጵያ እየታዘብኩ… እማዬ ከሱንከሞ ሱቅ ለቡና ቁርስ እንዲሆናት (በአቋራጭ ምሳም ይሆናል) በብድር ያስመጣችውን ሽንብራ እየቆረጠምኩ… (ግን መቼ ልትከፍለው ነው? ከየት አምጥታ ልትከፍለው ነው? – እሱን አላህ ነው የሚያውቀው)… ለአያቴ ይልሰው ይቀምሰው ያላተረፉለትን ዣንሆይና አያቴ ለሳቸው ያለውን ክብር እያሰላሰልኩ… አንድ የመርቲ ጣሳ የጉድጓድ ውሃዬን ጭልጥ አድርጌ ጠጥቼ (ሆዴ እየተንቦጫቦጨ) ወጣሁ… እኔም ወደ ዘመቻዬ በምንጋ ተመምኩ…

እነሆኝ አደግኩ!
እነሆኝ የኔ ዘመቻ!

… የበደሌ ዘመቻ!
… … የኮካ ኮላ ዘመቻ!
… … … የቀ እና ቐ ዘመቻ!
… … … … የለ እና ሌ ዘመቻ!

ቻ! ቻ! ቻ!
ከንቱ ብቻ!

አጁዛ አለ አዳም ረታ!
እውነትም አጁዛ!

Image

 
1 Comment

Posted by on January 9, 2014 in ስብጥርጥር

 

የዞረው ጎዳና

በጠማማ መንገድ ጉዞ የጀመረ
ሲወድቅ ሲነሳ ባለበት አደረ።
መንገዱስ ከራቀ የህልሜ መድረሻ
አንቺንና መጠጥ ሃዘኔን ማስረሻ።
________

ይህ ፅሁፍ የአልኮል መጥጥ ማስታወቂያዎችን የሚነካካ ነው። ማንኛውንም ግለሰብ ወይም የትኛውምንም አይነት አምራች ድርጅት አይመለከትም። በአንዲት ነፍስ የሚብሰከሰክ ግለሰባዊ ትዝብት ነው። ሃሳቡ ቢስማማህ አንተም ውስጥ የሚብሰለሰል ነገር ስለነበረ ቢሆን እንጂ አዲስ ተዓምር ፈጥሬልህ አይደለም፤ ሃሳቡ ቢጎረብጥህ አላማዬ አንተን ማስደሰት አይደለምና ሃሳቤን አክብረህ ማስታወቂያህንም፣ ጨብሲህንም የመቀጠልና የማስቀጠል ምርጫው ያንተ ነው።

“ሸገር ላይ አብቦ ሸገር ላይ ያፈራ
የጥንት የማለዳው ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ
አብሮ እየዘመነ ከዘመኑ ጋራ
አራዳን ያሞቀ አራዳን ያደራ

ዘላለም ጥም ቆራጭ ዘላለም ፍሰሀ
ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ የነፍስ እህል ውሃ
ወዳጅነት ጠብቆ ጨዋታ እንዲደራ
ይንቆርቆር ይቀዳ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ!”

ይህ የማንቆለጳጰሻ ግጥም በጥላሁን ገሠሠ “የጥንቱ ትዝ አለኝ” ዜማ ታጅቦና በአንባቢው አስገምጋሚ ድምፅ ግርማ ሞገስ ተላብሶ በሸገር ኤፍ ኤም ሲቀርብ ለጆሮ ደስ ይላል። ደስ ማሰኘትና ለመጠጥ ማነሳሳት የማስታወቂያው አላማ በመሆኑ በዚህ በኩል ተሳክቶለታል። ፋብሪካው ለዚህ ሙገሳ የተጠየቀውን ቢከፍልም አይቆጨው፤ ለአርቲስቱም ለድርጅቱም የገቢ ምንጭ ሆኗልና ይቅናቸው።

በግጥሙ ውስጥ ከተካተቱት የማስዋቢዋ ቃላት ጋር ግን በግሌ ፀበኛ ነኝ። ‘ዘላለም ጥም ቆራጭ’… ‘ዘላለም ፍሰሃ’… ‘የነፍስ እህል ውሃ’… ‘ወዳጅነት አጥባቂ’… ምናምን የሚሏቸውን የውዳሴ ቃላት በሰማኋቸው ቁጥር ግርም ይሉኛል። ገንዘብ ስለተከፈለና እድሉ ስለተገኘ ብቻ የሚንፎለፎል ቅጥፈት አይጥመኝም። ቢራ በየትኛው ስሌት ዘላለማዊ ጥም ሊቆርጥ እንደቻለ አልገባኝም። ዝንታለም ፍሰሃ ሊለግስ ይቅርና በብዙ መከራዎች ተቀነጣጥሳ ያጠረች እድሜን የባሰ የሚያሳጥርም ይሄው ልኩ የማይታወቀው አልኮል ነው። የነፍስ እህል ውሃነቱም ጠግቦ ላላደረ አንጀት የሰማይ ያህል ሩቅ ነው፤ ጠግቦ ላደረው ግን ምን እንደሆነ አላውቅም።

“ስማ ይሄ እኮ ማስታወቂያ ነው!… ማሻሻጫ እንጂ ሃቅ አይደለም!… ጅል ነህ እንዴ?!… ምን ታካብዳለህ?… ክባዳም!” አይነት ሰልጠን ያለ ቡጢ ከሰለጠኑት አካባቢ የሚሰነዘር ከሆነም ይህችን ጣል አድርገን እንቀጥላለን …

ዘላለም ጥም ቆራጭ ከሆነማ አርኪ
ለዝንታለም ሃሴት ከተሰኘ ምልኪ
የነፍስ እህል ውሃው በወግ ተበጥብጦ
በብልቃጥ በሲኒ ተደርጎ በጡጦ
ልልጆች ለህፃናት ይመረት አደራ
ታላቋን ኢትዮጵያ በቶሎ እንድንሰራ።

ቺርስ
በጊዮርጊስ

በርግጥ የአልኮል መጠጦችን በሬዲዮ፣ በቴሌቪዥን፣ በተለያዩ የህትመት ውጤቶች እንዲሁም በእስፖንሰር መልክ ማስተዋወቅ በጭራሽ አይገባም የሚል ደረቅ አቋም የለኝም። መንግሥትስ ለምን በህግ ‘ፈፅሞ እንዲከለከል’ አያደርግም?! የምል ወገኛም አይደለሁም፤ አይተዋወቅ ብዬም እየተነሳሁ አይደለም። በህግ የተከለለ የማስተዋወቅ ስርዓት ይኑረው (ወይም ህጉ ካለ በብርቱ ይተግበር) ነው መነሻዬ። አዎ በነጋ በጠባ ቢራ ቢራ አይበሉብን!.. ጎዳናዎቻችንን ሁሉ በቢራ አይሙሉብን!… ኧረ በዛ!… ኧረ ለከት ይኑረው!… ነው የኔ ሃሳብ። እኛ’ኮ ባይተዋወቅም በመጠጣት አንታማም!… ኑሯችን ለስካር ሩቅ አይደለም!… እንኳን አይዞህ ጠጣ ተብለን እንዲሁም ጠጪዎች ነን… ለዚህ እንኳን ብቁ ነን!…

የኛ አርቲስቶች፣ የኛ አስተዋዋቂዎች፣ የኛ ጋዜጠኞች፣ እና ሌሎች የሚመለከታቸው ባለሙያዎች አልኮልን የሚያስተዋውቁበትን መንገድ ልብ ብሎ ላስተዋለው ያስተዛዝባል ብቻ ሳይሆን ያሳስባልም። በተለይ ይሄን ማስታወቂያ እየሰሙ የሚያድጉ ልጆችስ ብሎ ማሰብ ለሞከረ የኔ ብጤ ክባዳም አንገት ያስደፋል።

‘የነፍስ እህል ውሃ ነው’… ‘የዘላለም ፍሰሃ ይሰጥሃል’… ‘ጨዋታህ ያለ ቢራ አይደራም’… ‘ወዳጅነትህ ያለ መጠጥ አይቀጥልም!’… እያልክ ላሳደግከው ልጅህ ኋላ ላይ ደግሞ ‘መጠጥ ይጎዳሃል’… ‘ጤናህን ያዛባብሃል’… ‘ከወዳጅ ያጣላሃል’… ምናምን ብትለው “አባዬ ደግሞ ታሾፋለህ እንዴ?!… አንተ አይደለህ እንዴ ለህዝቡ ስታውጅ የነበረው?!” ብሎ እንደሚያፌዝብህ ለማሰብ ጥልቅ ተመራማሪ መሆን የሚሻ አይመስለኝም። ያው እንዳላገጥን እንለቅ ካልሆነ በቀር…

አብዛኞቹ አርቲስቶች በግጥም፣ በዜማና በሙዚቃ ቅንብር ሲያንቆለጳጵሱት፤ በተለያየ የምስል ዲዛይን ሲያስሽሞነሙኑትና ሲያሞጋግሱት ስራዬ ብሎ ላያቸው አስካሪ መጠጥ የሚያስተዋውቁ ሳይሆን ብርቱ የነፍስ አድን መድሃኒት ሊያድሉ የሚሰናዱ ነው የሚመስሉት። አብዛኞቹ ነገረ ስራቸው ቅጥ ያጣ፣ የሚከፈላቸውን ገንዘብ እንጂ የሚሉትን ነገር ለሽራፊ ሰከንድ እንኳ ያሰቡበት የማይመስሉ ናቸው። በርግጥ ሁሉም ብሎ በአንድ ላይ መጨፍለቅ አግባብ አይደለም (እዚህ ውስጥ ያልተካተቱ አርቲስቶች ይቅር ይበሉኝ) በአብዛኛው ለአይናችን አሊያም ለጆሯችን የከበዱት አርቲስቶቻችን (ትልልቆቹም መጤዎቹም) ግን ቢያንስ የአንድ ቢራ አስተዋዋቂ መሆናቸው የአደባባይ ሃቅ ነው።

በነጠላ ዜማም ይሁን በነጠላ ፊልም ትንሽ ዝና ከተፍ ካለች ጥቁር መነፅርና ቢራ መለያቸው እየሆነች ነው። ኧረ ጎበዝ እየተሳሰብን እንጂ!… በጥቁሩ መነፅር ስታዩት ሌላ ነገር ወይም ሌላ ሃገር እየመሰላችሁ ይሆን እንዴ?!… እስቲ ከጥቁሩ መነፅር ውጡና ጎዳናዎቻችሁን… ህዝባችሁን እዩት… በሃላፊነት ጠጡ ከማለታችሁ በፊት በሃላፊነት ታስተዋውቁ ዘንድ ትለመናላችሁ።

“አውዳመት ሲደገስ ጎረቤት ሲጠራ
ወዳጅ ለመጋበዝ ገበታ ሲሰራ
እንዲሞቅ እንዲደምቅ ጨዋታ እንዲደራ
ይንቆርቆር ይቀዳ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ

ደስ ብሎ እንዲውል ያውዳመቱ ቆሌ
ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ አብሮ ይኑር ሁሌ
ወዳጅነት ጠብቆ ፍቅር እንዲደራ
ቅዱ ቅዱስ ጊዮርጊስ
ያዘቦት ያውዳመት የሁል ጊዜ ቢራ።”

ያዝ እንግዲህ!… ቢራ ከሌለህ አውዳመት የለም!… ወዳጅነት የለም!… ጎረቤት የለም!… መሰባሰብ የለም!… መተሳሰብ የለም!… ፍቅር ብሎ ነገር የለም!… ይልሃል!… በል እንግዲህ ጠጣና አውዳመትህን አድምቅ!… ወዳጅነትህንም ቀጥል… ቢራህም ሁሌም አብሮህ ይኑር ይልሃል!…

እኔም ልጨምርልህ… ከቢራህ የተለየህ እለት ድህነትህና ድንቁርናህ ፍንትው ብሎ ይታይሃልና በድህነትህ እንዳታፍር በኋላቀርነትህም እንዳታዝን ለከት የሌለው አጠጣጥ ጠጣ!… ጠጥተህ ድህነትህን እርሳ!… ይሄንንማ መፅሐፉም ብሎኛል ካልክም መብትህ ነው… መፅሐፉንም… ማስታወቂያውንም… እኔንም “እምቢኝ!” ያልክ ቀን ግን ወዳጅነት እንዴት እንደሚጠብቅና ድህነት እንዴት እንደሚፋቅ ሊከሰትልህ ጀምሯል ማለት ነው። ያኔ እናወጋለን!… ላሁኑ ግን ይህችን ሚጢጢዬ ግጥም እያላመጥክ ቀጥል …

‘አባቱ ደንዳና ብርቱ ጌሾ ወቃጭ፤
እናቱ ታታሪ ብቅል አብቃይ ቀያጭ፤
ኮበሌ ልጃቸው ሆነላቸው በጥባጭ፤
በል ዝም ብለህ ጨልጥ ያገር ሰው ተቀማጭ።’

ላሁኑ ሰላም
ትዝብቱ ግን ይቀጥላል

አብዲ ሰዒድ

Image

 
Leave a comment

Posted by on January 6, 2014 in ስብጥርጥር