RSS

ብቃት!

03 Nov

 

ከመውለድ ከመክበድ ከ’ናትነት በላይ
ከእልፍኝ ከማጀት ከኩሽናም በላይ
ይልቃል ይርቃል የተሰጠሽ ፀሐይ
ተ – ነ – ሽ !
አ – ት – ል – ፈ – ስ – ፈ – ሽ
ን – ቂ !
አ – ት – ው – ደ – ቂ
የትም አታርክሽው የውስጥሽን ሲሳይ!
____________________

ከዚህ ፅሁፍ ጋር የተያያዘው ምስል J. Howard Miller በተባለ አሜሪካዊ ግራፊክ አርቲስት የዛሬ 70 አመት ገደማ የተሰናዳ ነው። ይህ ግለሰብ በሁለተኛው የአለም ጦርነት ወቅት ለጦርነቱ ማነሳሻነት የሚውሉ የፕሮፓጋንዳ ምስሎችን በማዘጋጀት ይታወቃል። “We Can Do It!” የሚል ርዕስ የተሰጠው ይህ ምስልም ከስራዎቹ አንዱ ነው።

በምስሉ ላይ የምትመለከቷት ሴት Geraldine Hoff Doyle ትባላለች። በ1942 በአሜሪካ ሚቺጋን በሚገኝ የማሽነሪ ፋብሪካ ውስጥ የብረታ ብረት ሰራተኛ ነበረች። በወቅቱ የ18 ዓመት ወጣት የነበረችውን ይህችን የብረት ሰራተኛ አንድ የዩናይትድ ፕሬስ ኢንተርናሽናል ፎቶ አንሺ በስራዋ ላይ ሳለች ፎቶ አነሳት… ይህን ፎቶ ደግሞ ሚለር በዚህ መልኩ አሰናዳው… ከዚያም ይህ ፎቶ ሴቶችን ለፋብሪካ ስራና ለጦርነቱ እገዛ እንዲያደርጉ በማነሳሳት በኩል ብርቱ አስተዋጽኦ እንዳደረገ ይገመታል።

በዘመኑ የፋብሪካ ስራዎች በአብዛኛው የሚከወኑት በወንዶች ነበር… የወንዶች ስራ ብቻ ተደርገው ይቆጠሩም ነበር… በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ምክኒያት በርካታ ወንዶች ወደ ውትድርናው በመሰማራታቸው ሴቶችን ማበርታት ግድ ሆነ… በዚህም በርካታ ሴቶች የብረታ ብረትና የተለያዩ የፋብሪካ ስራዎች ላይ በመሳተፍ ጦርነቱን እንዲያግዙ ሆነዋል። አግዘዋልም!

ምንም እንኳን በ1943 ገደማ ለተካሄዱ ጥቂት የጦርነት ቅስቀሳዎች ያገለገለ ቢሆንም ያን ያህል ለማላው ጦርነት ጥቅም ሰጥቷል ማለት ግን አይቻልም… ጦርነቱም አበቃ… ፎቶውም ተረሳ!…

በ1980ዎቹ መጀመሪያ አካባቢ ግን ምስሉ ከተመሸገበት ስርቻ ተጎተተ… ከ40 አመታት በኋላ ዳግም ነፍስ ዘርቶ ተነሳ… የምስሉ ትንሳኤም ሆነ!… ያሁኑ አነሳስ ግን ለጦርነት ቅስቀሳ አልነበረም… ይልቁንም ለሴቶች መብት ተሟጋቾች ልሳን ሆኖ ለማገልገል እንጂ!

ምስሉ በብዙ ሺህ ኮፒዎች ተባዛ… በርካቶች አደባባይ ይዘውት ወጡ… መጽሐፎች፣ መፅሄቶች፣ ቴምብሮች፣ እና በርካታ የጥናት ስራዋችም ይህን ምስል ተጠቅመዋል… በቤት ውስጥ… በትምህርት ቤት… በስራ ቦታ እና በተለያዩ አካባቢዎች የሚካሄዱ ቅስቀሳዎች ተጧጧፈውበታል…

“ሴቶችን ማሳነሱ ይቁም!”…
“አትችይም የሚል አስተሳሰባችሁን ዋጡት!”…
“እችላለሁ!”
“እንችላለን!”
“ትችላለች!”
ለሚሉ ዘመቻዎች በሚገባ አገለገለ… አሁንም ድረስ እያገለገለ ይገኛል… የተጠቀሙበት ተጠቀሙ!… በርግጥም ሁሉም ሴቶች ይችላሉ… እመኚኝ ትችያለሽ!

ይህን ማራኪና አነቃቂ ምስል እንዳስታውሰው ያደረገኝ World Economic Forum በሰሞኑ ያወጣው የ2013 Global Gender Gap Report ነው… ይህ ሪፖርት አገሮች በሴቶች ተሳትፎ ዙሪያ ያለቸውን ደረጃ ያስቀምጣል…

በኢኮኖሚው፣ በፖለቲካው፣ በትምህርቱ እና በጤናው ዘርፍ የሴቶች እኩልነት የት ድረስ እንደደረሰ በተለያዩ መመዘኛዎቹ መዝኖ ደረጃውን ይሰጣል… በዚህ አመት በወጣው ሪፖርት መሠረት ኢትዮጵያችን ከ136 ሃገሮች 118ኛ ደረጃን ይዛለች… ይህ ማለት ሴቶች ከላይ በተዘረዘሩት መስኮች ያላቸው ተሳትፎ እንዲያው ዝም የሚያሰኝ መሆኑን የሚያሳይ ነው!!…

በዚህ ሪፖርት አይስላንድ 1ኛ ስትሆን… የመን የመጨረሻ ደረጃን ይዛለች… የኖርዲክ ሃገሮቹ እነ ፊንላንድ፣ ኖርዌይ እና ስውዲን አይስላንድን ሲከተሉ እነ ደቡብ አፍሪካ ሌሴቶ እና ፊሊፒንስ ደህና ተስፋ ያላቸው በሚል ተፈርጀዋል… ጎረቤታችን ኬንያ እንኳ ኢትዮጵያን ታስከነዳታለች (ያው የሷም ገና ቢሆንም)…

አዎ ኢትዮጵያ ዛሬም ለሴቶች የምትመች አይደለችም!… ብትመችም እጅግ ጥቂት ለሆኑና ከቁጥር ለማይገቡ የከተማ ሴቶች ነው (እሱም ምቾት ከተባለ ማለቴ ነው)… የሴቶችን ምቾት ሳትጠብቅ መሰልጠንና ማደግ ደግሞ ከቶም የማይታሰብ ቅዠት ነው… ሴቶችን የዘነጋህበት ጉዞህ አንተም የተዘነጋህ ያደርግሃል… ሴትን ስታቀና መንገድህ ይቀናል… ሴትን ስትንቅ በርግጥም ትናቃለህ!… ይህን ደግሞ ባይናችን እያየን ነው… ያከበሩት ሃገራት ከብረዋልና!

እናም ፈረንጆቹ ከ60ና 70 አመት በፊት የተጠቀሙት አይነት ዘመቻ ሳያስፈልገን አይቀርም… ከ20ና 30 አመት በፊት ጀምረው የተጓዙበት ጎዳና ሳይጠቅመን አይቀርም… “አትችይም!”… “አይሆንም!”… ምናምን የሚሉሽን አትስሚያቸው… እመኚ አሳምረሽ ትችያለሽ!…

ምናልባት ይህን የምታነብ ነቃ ያለች ከተሜ ሴት ብትገኝ…

“ምን ትችያለሽ ትሽያለሽ ይለኛል?… ይህ አባባል በራሱ የበታች ነሽ አይነት ነው!… እናም ይህ አይነት ቅስቀሳ አይመቸኝም!”… ምናምን የሚል ፍልስፍና ይቃጣት ይሆናል…
ለዚህች አይነቷ ነቄ… አየሽ ነፍሴ… ይኸው መልሴ እንላታለን… “ትችያለሽ!” የሚል ቃል እንደውሃ የጠማት… ህልሟን አጉል ልማድ የጨፈለቀባት… ውጥኗን ከንቱ ቃል ያጨነገፈባት… ትችያለሽ… ተነሽ የሚለው ቃል ብቻውን የሚያለመልማት በሚሊዮን የምትቆጠር ኢትዮጵያዊት ሴት አለች ነው …

እናም ተነሽ… አንቺ ስትነሽ ሃገር ትነሳለችና!
YES YOU CAN DO IT !!!

Image

 
Leave a comment

Posted by on November 3, 2013 in ስብጥርጥር

 

Leave a comment